Monday, April 20, 2020

የልቡና ትንሣኤ - ወደ ነፍስ ትንሣኤ - የነፍስ ትንሣኤ - ወደ ሥጋና ለነፍስ ትንሣኤ

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
12/08/2012
የልቡና ትንሣኤ ስለ እርሱ ማወቅን፣ መረዳትን፣ ማመንንና መቀበልን ይጠይቃል፡፡ ይህም ማለት ከውኃና ከመንፈስ ተወልጄ የእግዚአብሔር ልጅነትን አግኝቻለሁ፤ አሁን የምኖረው ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣው ከክርስቶስ ጋር በተዋሕዶ ነው፤ አሁን ከሰማያውያን ጋር ኅብረትን ፈጥሬአለሁ፤ ከአእላፍት ቅዱሳን መላእክት፣ ከቅዱሳት ነፍሳት ጋር አንድ ጉባኤ  ሆኜአለሁ፤ ምንም እንኳ በምድር ብኖር በሰማያዊ ሥፍራ ነኝ ብሎ ማወቅ፣ መረዳት፣ ማመን፣ መቀበል ማለት ነው፡፡ ይህን ማወቁ፣ መረዳቱ፣ ማመኑና መቀበሉ ከሌለን ባልታደሰው በቀበርነው በአሮጌው ማንነታችን ዕውር ድንብራችንን መጓዛችን እንቀጥላለን፡፡ ያኔ የሥጋ ሞት ያስፈራናል፣ ዕለታዊው ነገር ያስጨንቀናል፣ ዘለዓለም የምኖር ይመስለናል፣ በመብል በመጠጥ ደስታን ለማግኘት እንተጋለን፣ የእግዚአብሔርን ሕልውና ትርክት ይመስለናል እንጂ አናምንበትም፡፡ እነዚህ የልቡናን ትንሣኤ በማጣታችን በእኛ ላይ የሚሰለጥኑብን ናቸው፡፡ ነገር ግን የልቡናን ትንሣኤ ገንዘብ ስናደርግ ያለፈው የጨለማ ጉዞ፣ ያለማወቅ ጉዞ፣ የሥጋ ባርነት ጉዞአችን ሁሉ ትዝ እያሉን ይቆጩናል፡፡ ከፊት ለፊታችን ብዙ ሥራ እንደሚጠብቀን እንረዳለን፡፡ ገና መድረስ ካለብን ከፍታና መረዳት እንዳልደረስን፣ ሥጋችን የክርስቶስ ሥጋ ሆኖ በጥምቀት መለወጡን እንዳልተረዳነው ወደዚህም መረዳት ለመድረስ መትጋት እንዳለብን፣ ሕሊናችን ሁሌም ይህን  አሮጌውን ሰዋችንን ማለትም እንደ ሥጋ ፈቃድ መመላለሳችንን ገፍፈን እንደ መንፈስ ቅዱስ ፈቃድ እንድንመላለስ እንዲያተጋን ማሳሰብን ገንዘብ እናደርጋለን፣ የክርስቶስ አካል የሆነውን ሥጋችንን ባሕርይ ለማወቅ እንተጋለን፡፡ በአጠቃላይ ወደ ነፍስ ትንሣኤ እንመጣለን፡፡