Saturday, January 28, 2012

ስምንተኛዋ ቀን



ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
20/05/2004
ለስሙ ክብር ይግባውና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከልደቱ እስከ ስቅለቱ ተፈጥሮአዊ ሥርዐታትን ሁሉ በመሻር እኛም እንደርሱ ከፍጥረታዊ ሕግ በላይ እንድንሆን አበቃን፡፡ አስቀድሞ ከተፈጥሮአዊ ሕግ ውጪ ከቅድስት ድንግል ማርያም ያለወንድ ዘር ተፀነሰ፤ በኅቱም ድንግልናም ተወለደ፤ እንደንግሥናው ማረፊያውን ከንጉሥ እልፍኝ ያደርግ ዘንድ የሚገባው ጌታ ከከብቶች በረት እንስሳት እስትንፋሳቸውን እያሟሟቁት ተገኘ፡፡ ድንግል ከሆነችም ክብርት ብላቴና ጡት ጠብቶም እንደ ሕፃናት አደገ፡፡ በአይሁድ ሥርዐት ሙሉ ሰው እስከሚባልበት እስከ ሠላሳ እድሜው ድረስ ሁሉን በቃሉ የፈጠረ አምላክ ዝምታን መረጠ፡፡
 እርሱ ሁሉን ማድረግ ሲቻለው በቅናት ተነሣስተው በእርሱ ላይ የስድብን ቃል በተናገሩት ላይ ስለክፋታቸው በብድራት ክፋትን አልመለሰላቸውም፡፡ ይልቁኑ “…አባቴን አከብረዋለሁ እናንተ ግን ታዋርዱኛላችሁ” ብሎ በትሕትና ቃል መለሰላቸው፡፡(ዮሐ.8፡49) ከፍጥረታዊው ሕግ ውጪ በጭቃ የዕውሩን ዐይኖች አበራ፡፡ እርሱ ራሱ እግዚአብሔር ሆኖ እግዚአብሔርን ይሳደባል ብለው ከሰሱት፡፡ ወንጀለኞችን በሲኦል የሚቀጣ እንደ ወንጀለኛ ተቆጠረ፡፡ አሕዛብ ለእግዚአብሔር የቀኑ መስሎአቸው ሊቀኑለት በሚገባው አምላካቸው ላይ ተዘባበቱበት፡፡ በጥፊ መቱት የረከሰ ምራቃቸውንም ተፉበት እርሱ ግን በምራቁ እርሱን ሰምተው መንጎቹ ይሆኑ ዘንድ ጆሮአቸውን ኤፍታህ ብሎ ከፈተላቸው፤(ማር.7፡35) አርዓያቸውንም ይለዩበት ዘንድ ዐይኖቻቸውን በምራቁ አበራላቸው፡፡(ዮሐ.9፡8) አይሁድ በወንጀለኛው ምትክ ቅዱስ የሆነውን ክርስቶስን ይሰቅሉት ዘንድ ተማከሩበት፡፡

የእውነተኛ ጸሎት ባሕርያትና ውጤቱ (ከስምዖን ሶርያዊ)


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
19/05/2004
መግቢያ
ይክበር ይመስገንና የጥንት ክርስቲያኖች ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ማዕከል ያደረገ ሕይወት ይኖራቸው ዘንድ ራሳቸውን የሚያስተካክሉበት የጽሙና ጊዜና ቦታ ነበራቸው፡፡ ቤታችውንም ሲያንጹ የጸሎት ቤትንም ታሳቢ በማድረግ ነው፡፡ ይህች የጸሎት ቤት ጸሎት የሚያደርሱባት ብቻ ሳትሆን ቤተመጻሕታቸውም ናት፡፡ ለእነርሱ ሰገነታቸው እርሱዋ ናት እግዚአብሔር በዚያ ያስተማራቸውን ለማኅበራዊ ሕይወታቸው ማጣፈጫ አድርገው ይጠቀሙበታል፡፡ ይህ ሕይወት የትህርምት ሕይወት ተብሎ ይታወቃል፡፡
 ይህ ሕይወት ከምንኩስና ሕይወት ፈጽሞ የተለየና ማንም ክርስቲያን ሊተገብረው የሚችል ምናልባትም ከምንኩስና ሕይወት የሚልቅ ሕይወት ነው፡፡ ክርስቶስ ቀን ቀን ሕዝቡን ካስተማረ በኋላ ማታ ማታ ወደ ደብረዘይት ተራራ በመሄድ በጸሎት ይተጋ ነበር፡፡ ይህ ግን እርሱ ተገብቶት ሳይሆን ለእኛ አብነት ሊሆነን በመሻት ነው፡፡ በትህርምት ሕይወትም ጸሎትን የምንጸልይበትና መንፈሳዊ መጻሕፍትን የምንመረምርበት ጊዜና ቦታ ሊኖረን ግድ ነው፡፡ በጨለማ ከአምላክ የተማርነው በተግባራዊ ሕይወታችን ለዓለሙ ሰባኬያነ ወንጌል በመሆን ሕዝቡን ወደ እግዚአብሔር እናቀርባለን፡፡ በዚህ ሕይወታችን በጥምቀት ያገኘነው የክህነት ሥልጣን ተግባራዊ ይሆናል(royal priesthood ይህን ለመረዳት “እናንተ የመንግሥቱ ካህናት ናችሁ የሚለውን ጽሑፌን ይመልከቱ) በዚህ ሕይወቱ እጅግ የሚታወቀው ቅዱስ ኤፍሬም ነው፡፡ እርሱ ጌታውን በመሰለ ሕይወት ይኖር ነበር፡፡ ማታ ማታ በጸሎትና መንፈሳዊ መጻሕፍት በመመርመር ሲተጋ ቀን ቀን ደግሞ ሕዝቡን በማስተማር ይተጋ ነበር፡፡ ወደፊት ይህን አስመልክቶ መጽሐፍ ይኖረኛል፡፡ በዚህ ጽሑፍ ላይ የትህርምት ሕይወት ሲባል ይህን ሕይወት እንደሆነ አንባብያን እንዲያስተውሉልን በትሕትና እጠይቃለሁ፡፡   

ሥራ ፈትነት ለብዙ ኃጢአቶች መወለድ በር ይከፍታል” ተብሎ ተጽፎአል፡፡ በትህርምት ሕይወት የሚኖር ክርስቲያን ጸሎት የማያደርስ ከሆነ እርሱ ሥራ ፈት ነው ፡፡ ቅዱሳን አባቶች ከሌሎች አግኝተው ለእኛ እንዳስተማሩን በእግዚአብሔር አገልግሎት የተጠመደ ሰው እርሱ በጸሎት እየተጋ  ነው ፡፡እኔ እንደማምነው “ሕጉንም በቀንና በሌሊት ያስባል”(መዝ.፩፥፪) እንዲል ነቢዩ ዳዊት በመልካም ሥራ በመትጋት ሕጉን ለመፈጸም የሚታትር ከሆነ እርሱ በእውነት ያለማቋረጥ እየጸለየ ነው፡፡ ይህ ክርስቲያን ወደ ተሟላ መንፈሳዊ ከፍታ ሲደረስ፣ አመለካከቱም በመንፈስ ቅዱስ ሲታደስና ፍጹም ሰላምን ሲያገኝ፣ አንዲሁም አእምሮው በእግዚአብሔር ፍቅር ሲያዝ  እግዚአብሔር የዚህን ታራሚ ልቡና መገለጫው አድርጎታል ማለት ነው፡፡