Monday, February 25, 2019

ጸሎት በኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ትርጓሜ

በመ/ር ሽመልስ መርጊያ
18/06/2011 ዓ.ም  
ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት እኔስ ቅዱሳን ብላቸው እመርጣለሁ በአንድነት የተስማሙባት አንዲት ደግ ትርጉም አለች እርሷንም በሕሊናዬ ሳደንቃት ሳወጣ ሳወርድ አረፈድኩ፡፡ እርሷም ጸሎት ማለት ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር ናት የምትለዋ ትርጓሜ ናት፡፡ እሊህ ሊቃውንት በአንድ ድምፅ ጸሎት ማለት ልመና፣ ምልጃ ወይም ምስጋና ማለት ነው ብለው አልተረጎሙልንም ነገር ግን ጻድቁ አብርሃም አምላኩን ሥላሴን በእንግድነት ተቀብሎ ያነጋገረውን ንግግር ዓይነት፣ ሎጥ ወንድሙንና ቤተሰቡን እንዲያድንለት ከአምላኩ ጋር የተነጋገረውን መነጋገር ዓይነት፣ ያዕቆብ በጵንኤል ከአምላኩ ጋር ታግሎ ካልባረከኝ አልለቅህም ያለውን ዓይነት መነጋገር፣ ሙሴ በደብረ ሲና ተራራ ላይ ዐራባ ቀንና ሌሊት ከፈጣሪው ጋር የተነጋገረበትን ዓይነት እና ክብርህን አሳየኝና እርሱ ይበቃኛል ብሎ የተነጋገረውን መነጋገር ዓይነት፣ ኤልያስ እና ኤልሳዕ ከአምላካቸው ጋር የተነጋገሩበትን መነጋገር ዓይነት፣ ነቢያት ሁሉ ከአምላክ ጋር የተነጋገሩትን መነጋገር ዓይነት ናት አሉን ወዳጆቼ፡፡