Monday, September 24, 2012

መስቀል ለእኛ ኦርቶዶክሳውያን



በዲ/ን ሽመልስ መርጊ
14/01/2005
ከዚህ በፊት በማኅበረ ቅዱሳን መካነ ድር የተለቀቀ
መስቀል ለእኛ ኦርቶዶክሳውያን ልዩ የሆነ መንፈሳዊ አንድምታ አለው፡፡ በመስቀሉ እነሆ አሮጌው ሰዋችንን ሰቅለን ከጐኑ በፈሰሰው ውኃ በጥምቀት በመቅበር አዲሱን ሰው ክርስቶስን ለብሰን ተነሥተናል(ኤፌ.422-24)፡፡ 
 በመስቀሉ እርግማናችን ተወግዶ የኃጢአት ስርየትን አግኝተናል፡፡ በመስቀሉ ላይ ከተሰዋው ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ በመመገብ ከሚያፈቅረን ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ፍጹም የሆነ ተዋሕዶን መሥርተናል(ማቴ.2626) እርሱ በእኛ እኛም በእርሱ የሆንበት ሰማያዊ ማዕዳችን በመስቀሉ ላይ የተሠዋው መሥዋዕት ነው፡፡ (ዮሐ.656) 
በመስቀሉ በአዳምና በሔዋን መተላለፍ ምክንያት በእኛ ላይ ጸንቶ የነበረው የፍርድ ትእዛዝ ተሽሯል፡፡(ቆላ.214) በብሉይ ለሙሴና ለእስራኤል ዘሥጋ እግዚአብሔር አምላክ በምስክሩ ድንኳን ውስጥ ባለችው የቃል ኪዳኑ ታቦት ላይ  ሆኖ በደመና አምድ ይገለጥላቸው ነበር፡፡(ዘጸአ.339) ቢሆንም ወደ ቅድስተ ቅዱሳን የምታገባዋ ጎዳና ተዘግታ ነበር፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ጳውሎስካህናት አገልግሎታቸውን እየፈጸሙ ዘወትር በፊተኛይቱ ድንኳን ይገቡባታል፤ በሁለተኛይቱ ግን ሊቀ ካህናት ብቻውን በዓመት አንድ ጊዜ ይገባባታል፤ እርሱም ስለ ራሱና ስለሕዝቡ ኃጢአት የሚያቀርበውን ደም ሳይዝ አይገባም ፊተኛይቱም ድንኳን በዚህ ገና ቆማ ሳለች ወደ ቅድስት የሚወስደው መንገድ ገና እንዳልተገለጠ መንፈስ ቅዱስ ያሳየናል”(ዕብ.96-) ብሎ ተናገረ፡፡