Monday, February 13, 2012

ለእኛስ የፍቅረኞች ቀን ይኖረን ይሆንን?(ቀጣይ ጽሑፍ)


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/06/2004
... ከእዚህ መንደርደሪያ አሳብ ተነሥተን ጾታዊ ፍቅር የተገለጠው መቼ ነው ብለን ብንጠይቅ ሔዋን ከአዳም የግራ ጎን ከተገኘች በኋላ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ በዚያን ጊዜ አባታችን አዳም እግዚአብሔር ከጎኑ አጥንት የፈጠራትን ሴት በተመለከተ ጊዜ “ይህች አጥንት ከአጥንቴ ናት ሥጋዋም ከሥጋዬ ናት” በማለት ለእርሱዋ ያለውን ፍቅር ለአምላኩ ገለጠ፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር በገነት በአዳምና በሔዋን መካከል ትዳርን መሠረተ፡፡እግዚአብሔርም "ሰው አባትና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይጣበቃል(ይተባበራል)" አለ፡፡ ስለዚህም ለአዳምና ለሔዋን እቺ ዕለት የደስታቸው ቀን ናትና መቼም ቢሆን የሚረሱዋት ቀን አይደለችም፡፡
ይህ በሰማያት የተሠራው ሰማያዊ ሥርዐት ከውድቀትም በኋላም ቀጥሎአል፡፡ ስለዚህም በዚህ ፍቅር እርስ በእርሳችን እንሳሳባለን በትዳርም እንታሰራለን፡፡ ሥርዐቱም ሰማያዊ ነውና ፍቺ ፈጽሞ አይፈቅድም፡፡ ፍቺ ተፈጸመ ማለት ትዳሩ ከሰማያዊው ሥርዐት ወጣ እንስሳዊ ሆነ  ቅድስናውን አጣ ማለት ነው፡፡ ያም ማለት ምን ማለት መሰላችሁ በሥላሴ ውስጥ ያለው አንድነትና ሦስትነት መልኩን አጣ ከተፈጠርንበት ዓላማ ወጣን ማለት ነው፡፡