Sunday, June 11, 2017

የነፍስ ወግ (በእንተ ደናግላን)


እንደ ጢሞቴዎስ ከልጅነት ጀምሮ ከቅዱሳን መጻሕፍትና ከመንፈስ ቅዱስ እንዲሁም ከትርምት ሕይወት ስለእግዚአብሔር የተማረ፤ የልቡናውን ደጅ በመዝጋት ከሕግ መምህር ትምህርቱን የቀዳ ክርስቲያን ለእርሱ ከትዳር ሕይወት ይልቅ የድንግልና ሕይወት እንዴት የተመረጠ ሕይወት አይሆነው? ይህ ሰው ማዕረጉ ከመላእክት ወገን ነውና የሥጋ ፍትወት የራቀለት በትንሣኤ ሕይወት የሚኖር እግዚአብሔር ሳይመርጥ ኃጥኡንም ጻድቁንም እንዲወድ ሁሉን የሚወድ በአንዲት ብላቴና ፍቅር ታሥሮ እርሱዋን አስቀድሞ ሌላውን አስከትሎ መውደድ የማይቻለው፣ እንደ አምላኩ ሁሉን አስተካክሎ የሚወድ በትዳር ውስጥ ያሉቱ ጥንዶች በትንሣኤ የሚያገኙት ሙሉዕ የሆነ ፍቅር አግኝቶ የሚኖር ሰው ነው፡፡