Sunday, February 10, 2019

እግዚአብሔርን ማወቅ ራስን ለማወቅ


በመ/ር ሽመልስ መርጊያ

ቀን 03/06/2011 ዓ.ም

እውነቱን እንናገር ካልን ሰው ራሱን ወደ ማወቅ የሚደርሰው እግዚአብሔርን ወደ ማወቅ ሲደርስ ብቻ ነው፡፡ ሰው እግዚአብሔርን ሳያውቅ የሚኖረው ኑሮ ከእንስሳት በእጅጉ በተዋረደና ባለማስተዋል እንደ ሰይጣን ፈቃድና ሐሳብ በሆነ አኗኗር ውስጥ  ነው፡፡ ሰው ንጹሕ የሆነውን ባሕርይውን ተረድቶ ክፉ ፈቃዱን ገቶ በመልካም ሰብእና መመላለስ የሚችለው አስቀድሞ እግዚብአብሔርን ሲያውቅ ነው፡፡ አንድ ሰው ስለ እግዚአብሔር እየተማረ ሲያድግ ራሱን ወደ ማወቅ ይደርሳል፡፡ እግዚአብሔርን ሳያወቁ ራስን ማወቅ አይቻልም፡፡ ምክንያቱም ሰው በተፈጥሮው እግዚአብሔርን እንዲመስል ሆኖ የተፈጠረ ፍጥረት ነውና፡፡ ስለዚህ ሰው እግዚአብሔርን ሲያውቅ ንጹሕ የሆነውን እግዚአብሔርን የሚመስልበትን ባሕርይውን ወደ ማወቅ በእርሱም ወደ መመላለስ ይመጣል፡፡ እግዚአብሔርን በማወቅ ውስጥ ሆነን ራሳችንን ወደ ማወቅ ስንመጣ በውስጥም በውጪም ሥራ የሚሠራውን እግዚአብሔርንና ፈቃዱን እንረዳለን፡፡ እግዚአብሔርን ለማወቅ አለመሻት ራስን ለማወቅ ፈቃዱ እንደሌለን ማሳያ ነው፡፡  በራስ ጥረት ራስን ለማወቅ የሚደረግ ድካም  እንደው ደንዝዞ በስሜት መንሆለል፤ በሐሳብ መጋለብ፤ በምናብ መንጎድ ቢሆን እንጂ የትም አያደርሰንም፡፡ ይህም በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ እንደመዳከር ነው፡፡