Wednesday, March 7, 2012

በዓለ እግዚእ በቅዱስ ኤፍሬም




ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
29/06/2004 
ይህቺ ቀን ለቅዱሳን ነቢያት ነገሥታትና ካህናት የደስታቸው ቀን ናት፡፡ በዚህች ቀን በይሁዳ አውራጃ በቤተልሔም እንደ ተስፋ ቃሉ የሰው ልጆችን ከኃጢአት ሊያድናቸው ከቅድስት ንጽሕት ድንግል ማርያም አማኑኤል ተወለደ፡፡ እነሆ ድንግል አስቀድሞ በነቢዩ ኢሳይያስ “እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች”(ኢሳ.7፡14)ብሎ የተነገረው የትንቢት ቃል እውን ሆነ፡፡ አሕዛብን ወደ እርሱ የሚያቀርባቸው በዚች ቀን ተወለደ፡፡ ነቢዩ ዳዊት ስለእርሱ የተናገረው ትንቢት ዛሬ ተፈጸመ፡፡(መዝ.130፡1-7) ሚክያስ የተናገረው የትንቢት ቃልም እንዲሁ፡፡(ሚክ.5፡2) ጌታችን በኤፍራታ እረኛ የሆነው ክርስቶስ ተወለደ፡፡(ማቴ.2፡1-2) በበትሩም(በመስቀሉም) በእርሱ የታመኑትን ይጠብቃቸዋል፡፡ ከያዕቆብ ኮከብ ወጣ ከእስራኤልም ራስ የሆነው ተነሣ፡፡ በልዓም አስቀድሞ “አያለሁ አሁን ግን አይደለም እመለከታለሁ በቅርብ ግን አይደለም ከያዕቆብ ኮከብ ይወጣል ከእስራኤልም በትር ይነሣል”ብሎ የተናገረው የትንቢት ቃል በዛሬዋ ቀን ተፈጸመ፡፡(ዘኁል.24፡17) በሕቡዕ የነበረው ብርሃን በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ መገለጥ ታየ፡፡ በነቢዩ ዘካርያስ የተነገረው ብርሃን ዛሬ በቤተልሔም አበራ!(ዘካ.4፡1-3)

ጌታችን ሆይ!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
28/06/2004
ጌታችን ሆይ! ዛሬ ወደ ኋላ ተመልሼ የአዳምና የሔዋን ቅድስናና ንጽሕና ምን ይመስል እንደነበረ ለማስተዋል ሞከርኩ፡፡ ጌታ ሆይ! የኃጢአታችንን ታላቅነት እኛ በአንተ ላይ ባደረስነው መከራ ስንመለከተው፣ የጥንት ቅድስናችንንና ንጽሕናችንን በአንተ ሰው መሆን ውስጥ ተመለከትነው፡፡ አዎ ጌታችን ሆይ! በአንተ የቀደመው የቅድስና ሕይወታችን ምን ያህል ማራኪ እንደነበረ አስተዋልነው፡፡ አንተ በልብህ ትሑትና የዋህ እንደሆንክ ነገር ግን የዋህነትህ ከእውቀት ጉድለት እንዳልሆነ እንዲሁ ከውድቀት በፊት የአዳም አባታችንና የሔዋን እናታችን ትሕትናና የዋህነት በእውቀት የተሞላ ነበር፡፡
አንተ ፍጥረትህን ነፍስህን እስከ መስጠት ደርሰህ እንድትወድ እንዲሁ አዳምና ሔዋንም ራሳቸውን እስከመስጠት ድረስ ደርሰው አንተንና ከሥራቸው ያስገዛህላቸውን ፍጥረታት ይወዱ እንደ ነበር አሳየኸን፡፡ ጌታ ሆይ! አዳምና ሔዋን እርስ እርሳቸውም ያላቸው ፍቅር በአንተና በአባትህ መካከል እንዳለው ዓይነት ፍቅር ይመስል ነበር፡፡ ቅድስናቸውም አንተ “የሰማዩ አባቴ ቅዱስ እንደሆነ እናንተም ቅዱሳን ሁኑ” ብለህ እንዳስተማረከን ዓይነት ሥላሴን አብነት ያደረገ ቅድስና ነበር፡፡ ይህ እንደ ሕፃን ቅዱስና ንጹሕ የሆነ የአዳምና የሔዋን ተፈጥሮ በአንተ ዘንድ እጅግ ተፈቃሪ ነበር፡፡ ስለዚህም አባታችን ያዕቆብ ከልጆቹ ይልቅ የክርስቶስ ኢየሱስ አርአያ ያለውን ዮሴፍን እንዲወደው፣ አንተም ጌታ ሆይ! እኛን የሰው ልጆችን ከሌሎች ፍጥረታት ሁሉ ይልቅ የአንተ አርአያ ይታይብናልና ትወደን ነበር፡፡