Wednesday, January 23, 2019

በዓመፃ ገንዘባችሁ እወቁበት


በመ/ ሽመልስ መርጊያ
 14/05/2011
ልቡናችሁን መቅደሱ አድርጋችሁ በእርሱ ፍቅር ከብራችሁ የምትኖሩ በክርስቶስ ወንድሞቼና እኅቶቼ የሆናችሁ ወዳጆቼ ሆይ እንደው አንድ ሐሳብ ወደ ሕሊናዬ መጣና ሳወጣው ሳወርደው ለምን ከእነርሱ ጋር አብሬ አልጋራውም አልኩና እነሆ አልኳችሁ፡፡
ተወዳጆች ሆይ በእውን እንደ ሰው ምስኪንና የራሱ ያልሆነውን የእኔ ብሎ ዕውር ድንብሩን የሚጓዝ አለን ? የሚደንቀው ግን እርሱ በራሱ አርአያና አምሳል የፈጠረን አምላክ ባልፈጠርነውና የእኛ ባልሆነው ላይ አድራጊና ፈጣሪ አድርጎ ሾመን፡፡ ይህም ባሕርይው በእኛ እንዲከብር ገዢነቱ በእኛ እንዲገለጥ ነው፡፡ ቢሆንም ግን ፍጥረቱ ላይ እንዲህ እንድንሰለጥን ማድረጉ ለሰው ልጆች የሰጠው የመጨረሻው ስጦታው አይደለም፡፡ ይህ ዓለም ለሰው ልጆች እንደ ድርጎ የተሰጠ እንጂ መሠረታዊም አልነበረም፡፡ በአባታችን በአዳም በእናታችን በሔዋን ውስጥም እንዲህ ዓይነት ሐሳብ አልነበረም፡፡ ያኔ በገነት ለማየትና ለመብላት መልካም ሆነው የተሰጡ አትክልትና አዝዕርት እንዲሁም እንስሳት ሁሉ ለመኖር አስፈላጊዎች አልነበሩም፡፡ ስለዚህ ዲያብሎስ በእነርሱ ላይ ይሰለጠኑ ዘንድ በተሰጣቸው ላይ የተንኮል ድሩን ማድራት አልፈቀደም፡፡ ነገር ግን እርሱ አፍቃሪያችን በጊዜ ሂደት እርሱ በፈቀደው ጊዜና ሰዓት እርሱን ወደ መመሰል አምጥቶ አማልክት እንደሚያደርገን በዲያብሎስ ዘንድ የታወቀ ነበር፡፡ ስለዚህ ዲያብሎስ ያለ ጊዜው አምላክ የመሆን ምኞትን አስቀድሞ በሔዋን ሲቀጥል በአዳም ልቡና ውስጥ አሳድሮ ከአምላክ ለያቸው፡፡ እኛም በእነርሱ ምክንያት ወደዚህች ድርጎው መሠረታዊ ነገር ወደ ሆነባትየእለት እንጀራችንን ስጠን ዛሬብለን እንድንጸልይ ወደ ተገደድንባት ምድር ተጣልን፡፡