Sunday, January 15, 2012

ክርስቶስና ክርስትና

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
05/04/2004 ዓ.ም
ክርስትና ማለት ክርስቶስ ማለት ነው፤ ክርስቶስም ክርስትና ማለት ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ሰው ተፀንሶ በመወለድ፣ በየጥቂቱ አደገ መጽሐፍ እንዲል ኃጢአትን እስከ ሞት ድረስ ተቃወመ፡፡ ክርስትናም እንዲሁ ናት ተፀንሳ ልትወለድ በየጥቂቱም ልታድግ ኃጢአትን በመቃወም እስከሞት ልትጸና ይገባታል፡፡
ክርስትና ማለት ክርስቶስ፣ ክርስቶስ ማለት ክርስትና ማለት ነው፤ ቤተሰብም ቤተክርስቲያን ማለት ነው፡፡ ቤተክርስቲያንም በቅድስት ድንግል ማርያም ትመሰላለች፤ ስለዚህ ቤተሰብ ቅድስት ድንግል ማርያምን ሊመስል ይገባዋል፡፡ እርሱዋ እግዚአብሔር ከወላጆች ሊገኝ የሚገባው መንፈሳዊ ብስለት ውስጥ ስለነበረች ክርስቶስን ለ...መውለድ ተመረጠች፡፡ የእርሱዋ ቤተሰብን በመንፈሳዊ እውቀት የመምራት ብቃቱዋን ለማስረዳት ለእኛ “በሰውም በእግዚአብሔርም ፊት በጥበብና በሞገስ እንዲሁም በቁመት አደገ” ተብሎ ጻፈልን፡፡ እርሱዋ የእውነተኞች ወላጆች ምሳሌ ናት፡፡ ቤተሰብና ቤተክርስቲያን እንዲሁ ልጆቻቸውን ክርስቶስን መስለው እንዲያድጉ በሰውም በእግዚአብሔርም ፊት በጥበብና በሞገስ በጤንነትም የማሳደግ ሓላፊነት አለባቸው፡፡ ይህ ሕይወት ክርስትና ይባላል፡፡
ወይም ክርስትና እንደ መስቀሉና ክርስቶስ ናት፡፡ መስቀልን ስናስብ ጌታችንን አምላካችንን ከልደቱ እስከሞቱ ለእኛ አብነት የሆነባቸውን ተግባራዊ የሕይወት ምልልሶችን እናስባለን፡፡ መስቀልን ከክርስቶስ ክርስቶስንም ከመስቀል ነጣጥለን እንዳናስብ ክርስትናንም ከክርስቶስ ክርስቶስንም ከክርስትና ነጣጥለን አናስብም፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም “ስቅለቱ የእርሱን ልደት ሲያውጅ ልደቱ ደግሞ የእርሱን ሞት ያውጃል” ብሎ ያስተምራል፡፡ ክርስቶስ በሥጋ ከእውነተኛይቱ እናት ቅድስት ድንግል ማርያም ካልተወለደ እንዴት ሊሞት ይችላል? እርሱ ሊሰቀል የሚገባው ከሆነ በሥጋ ሊወለድ ግድ ነው፡፡ምክንያቱም መለኮት በባሕርይው ሞት የለበትምና፡፡ ስለዚህ አንዱ ለአንዱ ማስረጃ ሆነ፡፡ ልደቱን ስናስብ ኃጢአትን በመቃወም ክርስቶስን ወደ ማወቅ ልናድግ እንጂ ልደቱን አሳበን የኃጢአት ፈቃዳችንን ልንፈጽም አይደለም፡፡ ቤተሰብ የክርስትና ሕይወታችን መሠረት ነውና እናንተ ወላጆች ሆይ ቅድስት ድንግል ማርያምን ምሰሉዋት፡፡ ልጆቻችሁን በመንፈሳዊ ጥበብና እውቀት አበልጽጋችሁ ክርስቶስን ለብሰው እንዲያድጉ ትጉ፡፡ ንጹሕና ቅዱስ የሆነውን አዲሱን ሰው ክርስቶስን እወቁት ምሰሉት! ክርስትና ይህቺ ናት፡፡ ክርስቶስ በእኛ ይገለጥ ዘንድ በልደቱ እርሱን በመምሰል እስከሞት ድረስ ኃጢአትን በመቃወም እንኑር፡፡ መልካም የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት ይሁንልን አሜን!!

ስለፍቅር



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ቀን ሰኞ 30/05/2003
አዲስ አበባ 

እግዚአብሔር በባሕርይው ፍቅር ነው፡፡ እርሱ እጅግ ጥልቅ ከሆነው ለእኛ ለሰዎች ከመረዳት ባለፈ ፤ በእርሱ ብቻ በሚታወቅ ፍቅር ውስጥ ይኖራል፡፡ ሰውን በእርሱ አርዓያና አምሳል ፈጠረው ስንልም በባሕርይው ፍቅር የሚስማማው አድርጎ ፈጠረው ስንል ነው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ሰዎችን እጅግ ይወዳል፡፡ ሰውን በማንኛውም ማለትም በትልቅም ይሁን በትንሽ ባለማወቅም ይሁን በድፍረት በስውርም ይሁን በግልጽ በተንኮልም ይሁን በተግዳሮት የምናሳዝነው ከሆነ የምናሳዝነው ሰውየውን ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔርን ጭምር ነው፡፡ በእኛ ያዘነው ሰው ልቡ በሃዘን ሲሰበር፤ እግዚአብሔርም እጅግ ያዝናል፡፡ በሃዘን ውስጥ ያለውን ሰው ከልቡ ደስ እንዲሰኝ ስናደርገው እግዚአብሔርም ደስ ይለዋል፡፡ በቅንነት ወደ ሰዎች ሁሉ ስንቀርብ እርሱም ከእኛ ጋር በቅንነት ይቀርባል፡፡ ሰዎችን ሁሉ እኩል ስናይለት ልቡ በደስታ ትፈካለች፡፡ በተንኮል ስንቀርብ ግን ግርማው ብቻ እንደሚያርድ አንበሳ በቁጣው ያርበደብደናል፡፡ በክፋታችን ከጸናን ደግሞ ያደቀናል ከእርሱ እጅ የሚታደገን ማንም አይኖርም ፡፡ ክፋታችንን አውቀን ከልባችን መጸጸታችንን ሲመለከት ደግሞ ልጁዋን እንደምታፈቅር እንስፍስፍ እናት ኃጢአታችንን ሁሉ ረስቶ በጸጋዎቹ እየሳመን ያጽናናል፤ ከእቅፉ ውስጥም በማኖር በፍቅሩ ያሞቀናል፡፡ የእርሱ ሃዘን ሰዎች ፍቅር ያጡ ጊዜ ነው፡፡

ኤደን ገነት በቅዱስ ይስሐቅ ሶርያዊ

“ኤደን ገነት የተባለችው የእግዚአብሔር ፍቅር ናት፡፡ በዚች ውስጥ የገነት በረከቶች ሁሉ ይገኛሉ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ከምድር በመነጠቅ መለኮታዊ ምግብን ተመግቦ የጠገበባት ቦታ ይህቺ ናት፡፡(፪ቆሮ.፲፪፥፪-፬) ከዚያ የሕይወት ዛፍ ፍሬ በልቶ ከጠገበ በኋላ “ዐይን ያላየችው ጆሮም ያለሰማው በሰው ልቡና ያልታሰበው እግዚአብሔር ለሚወዱት ያዘጋጀው” ብሎ መሰከረላት፡፡( ፩ቆሮ.፪፥፱ )… እንደእኔ እምነት በሲኦል ያሉ ነፍሳት የሚቀጡት በፍቅር ማጣት ነው እላለሁ ፡፡ ፍቅርን ከማጣት የበለጠ እጅግ የሚጎዳና የሚያም ሕመም ምን አለ ? በፍቅር ላይ በደልን የፈጸሙ ሰዎች በራሳቸው ላይ እጅግ የከበደና አስፈሪ ቅጣትን አመጡ ፡፡….” (ቅዱስ ይስሐቅ)

የአምላክ እናትነት




ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ቀን 4/06/2003 ዓ.ም
አዲስ አበባ

ጌታ ሆይ የእጅህ ሥራ ስለሆንኩ እጅግ ግሩምና ድንቅ ነኝ፡፡ ስለኃጢአቴ ራሴን ብወቅስም አንተ ግሩምና ድንቅ አድርገህ የፈጠርከውን ሰውነቴን በኃጢአቴ ምክንያት የተዋረደ ነው አልለውም፡፡ ይህ ሰውነት በአንተ ንጹሐን እጆች የተበጁ ናቸውና፡፡

እናቴ ሆይ ንገሪኝ አንቺ ትሆኝ ከሆድሽ ሳለሁ ሰው እንድሆን ዐይንና ጆሮ አፍንጫንና ግንባርን የሠራሽልኝ፣ ወይስ አንቺ ትሆኚ ሥጋዬን ከአጥንቴ ጋር አዛምደሽ ያበጃጀሻቸው? ወይስ በሥጋዬ ውስጥ ደምሥሮቼንና ጅማቶቼን አንዲሁም ልብና ኩላሊቴን ሌሎችንም ውስብስብ የሆኑ የሰውነት ሥርዐቶችን የሠራሻቸው? አንቺ ከሆንሽ በምን እውቀትሽ? እንዲህ ከሆነ ከእናቴስ በላይ አዋቂ ማን አለ? ከእናቴስ በላይ ሁሉን ቻይ ማን አለ? ነገር ግን እናቴ ዐይኖቹዋን በፍቅር ወደ አምላኩዋ አቅንታ “አንተን ከእኔ እኔንም ከእናቴ ማኅፀን ያበጀኝ እርሱ እግዚአብሔር ነው” ብላ አመላከተችኝ፡፡ ከልቡዋም ሆና እርሱዋን ሠርቶ በእርሷ ልጆቹዋን የፈጠራቸውን አምላኩዋን ዐይኖቹዋ የፍቅርን እንባ አንዳጋቱ ሲጋ እየተናነቃት ወደ እርሱ አንጋጠጠች፤ ተንበርክካም ስለቸር ስጦታው አመሰገነችው፡፡ በግንባሩዋም ተደፍታ ሁሉን እንዲህ ላከናወነው ለእርሱ ሰገደችለት፡፡ ከሰጊዱዋም ቀና ስትል ጉንጮቹዋ በእንባ ረጥበው ነበር፡፡ ዐይኖቿንም አቅንታ ክርስቶስ ከሥጋዋ ከፍሎ ወደ ፈጠራቸው ልጆቹዋ ተመለከተች፡፡ ነገር ግን እንባዋ ከጉንጮቹዋ መጉረፉን አላቋረጠም ፡፡ ምክንያቱም ጌታ ሆይ የአንተ እጅ ሥራ ናቸውና፡፡

በእውን ክርስቶስ ኢየሱስን እናውቀዋለንን?


ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/04/2004
አዲስ አበ

እጅግ ጠንቅቄ የማውቀው አንድ ሰው ነበር ፡፡ በእጁ ምንም ስባሪ ሳንቲም የለም ፤ ጸጉሩም አድጓል ፡፡ በእጁ ምንም ባለመኖሩ ምክንያት ጸጉሩ ቢያድግም መከርከም አልቻለም ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ሌላም የገንዘብ እዳ አለበትና ጭንቅ ይዞታል ፡፡ ወዲያው አንድ ነገር ትዝ አለኝ፤ ለራሴ“በእውኑ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጉሩን ያሳደገው ከድህነት የተነሣ ይሆንን? አልኩኝ ፡፡ ምክንያቱም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረው “ለወንድ ጠጉርን ማስረዘም ነውር ነውና”(፩ቆሮ.፲፩፥፲፬፣፲፭) ድህነት ደግሞ ለዚህም ያጋልጣል ፡፡
ጌታችንም ያደገው በምድራዊው ሀብት ደሃ ከምትባለው በሰማያዊው ብልጥግና ግን እጅግ ባለጠጋ ከሆነችው ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥር ሆኖ ነው ፡፡ ሐዋርያት “እኛ ድሆች ስንሆን ብዙዎችን ባለጠጎች እናደርጋለን”(፪ቆሮ.፱፥፲፪) ካሉ ቅድስት ድንግል ማርያም እንዴት ከእግዚአብሔር ዘንድ ባላት ሞገስ የተነሣ ከጸጋ ተራቁተው ያሉትን ባለጠጎች አታደርግ ? እርሱዋ የክርስቲያኖች ሁሉ ተማሳሌት የሆነች ፣ ራሱዋን በቅድስና ሕይወት በማመላለስ እግዚአብሔር ለሌላ የማይፈጽመውን ወደ እርሱዋ በመምጣት በሥጋ ከእርሱዋ በመወለድ እናቱ ትሆን ዘንድ የመረጣት ፣ እውነተኛ እናቱ ናት ፡፡ ቢሆንም በምድራዊ ብልጥግና በእርግጥም ደሃ ነበረች ፡፡ “እፎ ቤተ ነዳይ ኀደረ ከመ ምስኪን እምሰማያት ወረደ ላዕሌሃ ፈቲሖ ሥነዚአሃ ወተወልደ እምኔሃ” እንዲል፡፡

ኦ ክርሰቶስ!!!


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ
05/04/2004 ዓ.ም
አዲስ አበባ
ኦ ክርስቶስ ስላንተ ሴቶች ወንዶችን ተከትለው ሄዱ፡፡(ሰው አባትና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይጣበቃል የሚለውን ቃል ሽረው) ዘፍ.2፡24 ፡፡መበለት የነበረችው ትዕማር እርሱን(የባሎቿን አባት የአባታችን የያዕቆብ ልጅ ይሁዳን) ተመኘችው ፡፡ሩት ስለአንተ በእድሜ ያረጀውን ሰው ወደደችው፡፡ አዎን ሰዎችን በዝሙቷ የምትማርከው ረዓብ ባንተ ተማረከች፡፡ ትዕማር ጨለማን ለብሳ በጨለማ ወጣች ብርሃንንም ሰረቀች፡፡ ንጹሕ ባልሆነ መንገድ ንጹሕ የሆነውን ሰረቀች፡፡ ሰውነቷን በማራቆት አንተን ለመስረቅ ተጓዘች፡፡ንጹሕ ካልሆነው ንጹሕ የሆነውን የምታስገኝ አምላካችን ሆይ! ሰይጣን እርሷን አይቶ ተንቀጠቀጠ፤እናም እርሷን ለማሸበር ተፋጠነ፤ በእርሷ አእምሮ ውስጥ ፍርድን አስገባ፤ ነገር ግን እርሷ አልተሸበረችም፡፡ ስለአንተ በድንጋይ መወገርና በሰይፍ መቀላት አላስደነገጣትም፡፡ ይሁዳን ለማጥመድ ዘማውያንን መሰለች ከእዛ በኋላ ግን ልትዘሙት አልወጣችም፤ ምክንያቱም ዝሙትን የማይፈቅደውን ጌታ ሽታ ነውና የወጣችው፡፡ (ቅ/ ኤፍሬም ዘሶሪያ)

የተባረከው ሩካቤ (ለሙሽሮች)



ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
19/02/2003 ዓ.ም
አዲስ አበባ


ባልና ሚስትን ሰማያዊ ወደ ሆነው የደስታ ሥፍራ እንዲነጠቁ የሚያደርጋቸው፤ ፍቅር ከሞላበት ኩልል ካለው ከብርሃናዊ ምንጭ ጠጥተው የሚረኩበት፤ የደስታን እንባ በማንባት በፍቅር ግለት ልክ ከእናቱ ማኅፀን ግሩም በሆነ ጥበብ በእግዚአብሔር እጅ እንደሚፈጠር እቦቀቅላ ሕፃን አንድ አካል ለመሆን በእግዚአብሔር የሚሠሩበት ማኅፀን፡፡
የጌታን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም በየእለቱ አንድንቀበል በዚህም ወደሰማያዊ ምንድግናና ከክርስቶስ ጋር ፍጹም ወደሆነ ተዋሕዶ አንደምናድግ፤ እንዲሁ በዚህ የተባረከ ሩካቤ እግዚአብሔር ፍጹም ወደሆነ የአካል፣ የመንፈስ፣የስሜት ፣የፈቃድ አንድነት እንድንመጣ ለመላእክት ያይደለ ለእኛ ...ለሰው ልጆች ብቻ በእጁ ከምድር አፈር እንዳበጀው አዳም ሆነን ዳግም እንድንፈጠር የተሰጠ ግሩም ስጦታ፡፡

“እናንተ የመንግሥቱ ካህናት ናችሁ”(1ጴጥ.2፡5-9)



ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
5/04/2004
አዲስ አበ
መቼም ካህን የሚለውን ቃል ትርጉም የሚያጣው ክርስቲያን አይኖርም፡፡ ለማስታወስ ያህል ግን ካህን ማለት አገልጋይ ማለት ነው ፡፡ በእግዚአብሔርና በሕዝቡ መካከል ሆኖ እግዚአብሔርንም ምዕመናኑንም የሚያገለግል መካከለኛ ፡፡ ይህ ይጠፋዋል ተብሎ የሚታሰብ አንድም ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን የለም ፡፡ ባይሆን ወዳጄ ሆይ ይልቁኑ አንተ ራስህ ስለእነርሱ መዳን ለሞተላቸው ነገር ግን ወደ ክርስትና እምነት ላልተመለሱ ዘመዶችህ በምግባር አብነት ሆነኻቸው፣ በቃልም አስተምረሃቸው ወደ ጥምቀት በማቅረብ ከእግዚአብሔር ጉባኤ እንዲቀላቀሉ ቤተክርስቲያን ካህን አድርጋህ እንደሾመችህ ታውቃለህን ? መቼም እንዲህ ስትባል “እንዴ ! ምነው! ቤተክርስቲያንን ይመሩና ያስተዳድሩ ዘንድ ጳጳሳት የሾሟቸው ካህናት የት ሄደው ነው እኔን ካህን ማለትህ ? ብለህ ልትጠይቀኝ ትችላለህ ፡፡