Monday, February 25, 2019

ጸሎት በኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ትርጓሜ

በመ/ር ሽመልስ መርጊያ
18/06/2011 ዓ.ም  
ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት እኔስ ቅዱሳን ብላቸው እመርጣለሁ በአንድነት የተስማሙባት አንዲት ደግ ትርጉም አለች እርሷንም በሕሊናዬ ሳደንቃት ሳወጣ ሳወርድ አረፈድኩ፡፡ እርሷም ጸሎት ማለት ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር ናት የምትለዋ ትርጓሜ ናት፡፡ እሊህ ሊቃውንት በአንድ ድምፅ ጸሎት ማለት ልመና፣ ምልጃ ወይም ምስጋና ማለት ነው ብለው አልተረጎሙልንም ነገር ግን ጻድቁ አብርሃም አምላኩን ሥላሴን በእንግድነት ተቀብሎ ያነጋገረውን ንግግር ዓይነት፣ ሎጥ ወንድሙንና ቤተሰቡን እንዲያድንለት ከአምላኩ ጋር የተነጋገረውን መነጋገር ዓይነት፣ ያዕቆብ በጵንኤል ከአምላኩ ጋር ታግሎ ካልባረከኝ አልለቅህም ያለውን ዓይነት መነጋገር፣ ሙሴ በደብረ ሲና ተራራ ላይ ዐራባ ቀንና ሌሊት ከፈጣሪው ጋር የተነጋገረበትን ዓይነት እና ክብርህን አሳየኝና እርሱ ይበቃኛል ብሎ የተነጋገረውን መነጋገር ዓይነት፣ ኤልያስ እና ኤልሳዕ ከአምላካቸው ጋር የተነጋገሩበትን መነጋገር ዓይነት፣ ነቢያት ሁሉ ከአምላክ ጋር የተነጋገሩትን መነጋገር ዓይነት ናት አሉን ወዳጆቼ፡፡

Friday, February 22, 2019

ተዋሕዶ ኅትመት


 መ/ር ሽመልስ መርጊያ 

ቀን 14/06/2011 ዓ.ም

አምላክ በሕይወት ካቆየኝ አንድ በጎ እና ለቤተ ክርስቲያን ቅናቱ ያለው ሰው ይህን ሐሳብ ከግብ ሊያደርሰው ይችላል ብዬ በማመን  ይህን ሕልሜን ለአንባቢያን ላከፍለው ወደድሁ 
 ስያሜ፡- ተዋሕዶ ኅትመት
የስያሜው ምክንያት፡- ተዋሕዶ ማለት በሁለት አካላት መካከል የተደረገ ፍጹም የሆነ አንድነትን የሚገልጽ ቃል ሲሆን አንዱ አካል እና የአካሉ ባሕርይ የሌላኛውን አካልና ባሕርይ ሳያጠፋ፣ ሳይመጥ፣ ሳይቀይር፣ ሳይቀይጥ፣ ሳይለውጥ ነገር ግን አንዱ አካል ሌላኛውን አካል የራሱ አካልና ባሕርይ በማድረግ አንድ አካል አንድ ባሕርይ በመሆን የሚገለጡበትን ምሥጢር ለማስረዳት ቤተ ክርስቲያናችን በብቸኝነት የምትጠቀምበት ቃል ነው፡፡ ይህ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ሰው ሆኖ በመወለድ የገለጠው ምሥጢር ነው፡፡ እርሱ እግዚአብሔር ቃል ከአብ ጋር በመተካከል ሲኖር ሳለ ሰውን ለማዳን ሲል ከቅድስት ድንግል ማርያም በጽንሰት ሥርዓት ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍሷ ነፍስ በመንሳት ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው ሆኖ በአንድ አካልና በአንድ ባሕርይ ለፍጥረት ሁሉ ተገልጦአል፡፡ ይህን የእግዚአብሔር ቃል ሰው የመሆን ምሥጢር ቤተ ክርስቲያናችን ተዋሕዶ ትለዋለች፡፡ ይህንንም ቃል የራሷ መገለጫ ስም አድርጋም ትጠቀምበታለች፡፡ ይህንንም መጠሪያ ስሟ አድርጋ በመጠቀሟም ከሌሎች የክርስትና የእምነት ተቋማት ሁሉ ትለያለች፡፡  ስለዚህ ተዋሕዶ ስንል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማለት እንደሆነ ማንም በቀላሉ ይገነዘበዋል፡፡ ለዚህም ነው ወደፊት እግዚአብሔር ቢፈቅድ እንዲመሠረት ለምፈልገው የሕትመት ተቋም ተዋሕዶ ኅትመት የሚል ስያሜ መስጠቴ፡፡   

Sunday, February 10, 2019

እግዚአብሔርን ማወቅ ራስን ለማወቅ


በመ/ር ሽመልስ መርጊያ

ቀን 03/06/2011 ዓ.ም

እውነቱን እንናገር ካልን ሰው ራሱን ወደ ማወቅ የሚደርሰው እግዚአብሔርን ወደ ማወቅ ሲደርስ ብቻ ነው፡፡ ሰው እግዚአብሔርን ሳያውቅ የሚኖረው ኑሮ ከእንስሳት በእጅጉ በተዋረደና ባለማስተዋል እንደ ሰይጣን ፈቃድና ሐሳብ በሆነ አኗኗር ውስጥ  ነው፡፡ ሰው ንጹሕ የሆነውን ባሕርይውን ተረድቶ ክፉ ፈቃዱን ገቶ በመልካም ሰብእና መመላለስ የሚችለው አስቀድሞ እግዚብአብሔርን ሲያውቅ ነው፡፡ አንድ ሰው ስለ እግዚአብሔር እየተማረ ሲያድግ ራሱን ወደ ማወቅ ይደርሳል፡፡ እግዚአብሔርን ሳያወቁ ራስን ማወቅ አይቻልም፡፡ ምክንያቱም ሰው በተፈጥሮው እግዚአብሔርን እንዲመስል ሆኖ የተፈጠረ ፍጥረት ነውና፡፡ ስለዚህ ሰው እግዚአብሔርን ሲያውቅ ንጹሕ የሆነውን እግዚአብሔርን የሚመስልበትን ባሕርይውን ወደ ማወቅ በእርሱም ወደ መመላለስ ይመጣል፡፡ እግዚአብሔርን በማወቅ ውስጥ ሆነን ራሳችንን ወደ ማወቅ ስንመጣ በውስጥም በውጪም ሥራ የሚሠራውን እግዚአብሔርንና ፈቃዱን እንረዳለን፡፡ እግዚአብሔርን ለማወቅ አለመሻት ራስን ለማወቅ ፈቃዱ እንደሌለን ማሳያ ነው፡፡  በራስ ጥረት ራስን ለማወቅ የሚደረግ ድካም  እንደው ደንዝዞ በስሜት መንሆለል፤ በሐሳብ መጋለብ፤ በምናብ መንጎድ ቢሆን እንጂ የትም አያደርሰንም፡፡ ይህም በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ እንደመዳከር ነው፡፡