Wednesday, February 1, 2012

በረከት



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
24/05/2004
ልጆቹ ያደረገን፣ ፍጹም ከሆነው ለእኛ ካለው ፍቅር የተነሣ “በመስፈሪያው የተጨቆነና የተትረፈረፈ ጸጋውንና በረከቱን ያደለን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይክበር ይመስገንና በረከት የሚባለው ቃል በውስጡ ከላይ ከእርሱ ከፍቅር አምላክ ዘንድ የሚሰጠውን ደግ ቸርነት የሚያውጅ ቃል ነው፡፡ በረከት የሚለው ቃል አንድ ጊዜ ከእግዚአብሔር በተሰጠ ጸጋ ላይ ጭማሪ ወይም ድርጎ ሆኖ የሚሰጠውን የእግዚአብሔር ስጦታን ያመላክታል፡፡ በረከትን ለሁለት ከፍለን መመልከት እንችላለን፡፡ ምድራዊ በረከትና መንፈሳዊ በረከት በማለት፡፡
v ምድራዊ በረከት
ምድራዊ በረከት እግዚአብሔር በድካማችን ጨምሮ የሚሰጠን ስጦታው ሲሆን የእግዚአብሔር የፍቅሩ መገለጫ ነው፡፡ እግዚአብሔር ለሰው እንደ ድካሙ ብቻ መጠን ቢሰጠው ኖሮ ለነገ የሚያተርፈው አንዳች ነገር ባልኖረው ነበር፡፡ ነገር ግን በድካማችን ካፈራነው ላይ እግዚአብሔር የራሱን ቸርነት ያክልበታል፡፡ እንዲህ እንደሆነ እንረዳም ዘንድ ጌታችን አምስቱን እንጀራና ሦስቱን ዓሣት ባርኮ ለአምስት ሺህ ሰዎች መግቦ አጥግቦ አሳይቶናል፡፡ ይህም በሰዎች ኅሊና ውስጥ ሁልጊዜ እንዲታሰብም የተረፈውን በመሶብ ሰብስበው እንዲያስቀምጡት ሐዋርያትን አዘዛቸው፡፡(ማቴ.፲፭፥፴፪-፴፱)
የእግዚአብሔር ሰው የሆነውን የያዕቆብን እርሻ የባረከ አምላክ እንዲሁ የኃጥኡንም እርሻ ባርኳል፡፡(ሉቃ.፲፪፥፲፭-፳፪)  እኛም ይህን በማወቅ በእምነት የማይመስሉንን ከመናቅና ከማቃለል እንዲሁም ከመጸየፍ ተቆጥበን የእርሱን ፍቅር ገንዘባችን አድርገን ከጠፉበት እንመልሳቸው ዘንድ እንዲገባን ሊያሳስበን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ "በሰማይ ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ ... እርሱ በክፉዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን ያወጣልና በጻድቃንና በኃጢአተኞችም ላይ ዝናብን ያዘንባል"(ማቴ.5፡43-46) አለን፡፡


ቅዱስ ጳውሎስም"ወይስ እግዚአብሔር የአይሁድ አምላክ ብቻ ነውን? የአሕዛብስ አምላክ አይደለምን?(ሮሜ.3፡29) እንዲል  እርሱ የጻድቃን አምላክ ብቻ ሳይሆን ለማያመልኩትም አምላክ ነው፡፡  ስለዚህም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “…እርሱ ባለፉት ትውልዶች አሕዛብን ሁሉ በገዛ ራሳቸው ጎዳና ይሄዱ ዘንድ ተዋቸው፡፡ ከዚህም ሁሉ ጋር መልካምን ሥራ እየሠራ ከሰማይ ዝናብን፣ ፍሬ የሚሆንበትንም ወራት ሊሰጠን ልባችንንም በመብልና በደስታ እየሞላው ራሱን ያለ ምስክር አልተወም” ብሎ ተናገረ፡፡(የሐዋ.፲፬፥፲፮) ጌታችንም “ምን አንበላለን፣ ምንስ አንጠጣለን፣ ምንስ አንለበሳለን ብላችሁ አትጨነቁ ይህ ሁሉ አሕዛብ ይፈልጋሉ፤ ይህ ሁሉ እንደሚያስፍጋችሁ የሰማዩ አባታችሁ ያውቃል”(ማቴ.፮፥፴፪) ብሎ አስተምሮናል፡፡ ስለዚህም እኛም አስቀድመን እንደ እነርሱ እንደ ነበርን ነገር ግን በቸርነቱ ጎብኝቶን ከእርሱ ጋር እንደተዋሐድን አስበን እነርሱንም ይህ ቸርነቱ እንዲጎበኛቸው መጠየቅ ይገባናል እንጂ ልንታጀርባቸው አይገባንም፡፡ ዳዊት በመዝሙር "አቤቱ በድንኳንህ ውስጥ ማን ያድራል በተቀደሰውም ተራራህ ማን ይኖራል ... በአንደበቱ የማይሸነግል በባልንጀራው ላይ ክፋትን የማያደርግ ዘመዶቹንም የማይሰድብ፡፡(መዘዝ.14፡1-4)"ብሎ ብፁዕ ያለው ሰው ልክ እንደ አምላኩ ሁሉን አስተካክሎ የሚወደውን ሰው ነው፡፡
ይህ ምድራዊ በረከት ዓለም እስክታልፍ ለፍጥረቱ አይቋረጥበትም፡፡ እግዚአብሔር ዝናብን መስጠቱ ፀሐይን ማውጣቱ ፍጥረቱን ሁሉ ለመመገብ ነው፡፡ ቁና እንዘራለን በኩንታል እንሰበስባለን፡፡ ይህ በማንኛውም እርሱ በሚፈቅዳቸው ሥራዎቻችን የምናየው እውነታ ነው፡፡ ምድራዊ በረከት ለክርስቲያን እንደ ድርጎ የተሰጠ ወይም እንደ ድርጎ ሊቆጥረው የሚገባ በረከት ነው፡፡ ይህ በማንኛውም የሥራ መስክ ላይ ላለ ክርስቲያን ሁሉ የሚሠራ ነው፡፡ እንደ አቅሙና ችሎታው መጠን ይሠራል እግዚአብሔርም የድካሙን ፍሬ ከእጥፍ በላይ አድርጎ ይሰጠዋል፡፡
 በዚህ በረከት ላይ የእግዚአብሔር ዓላማ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ መንገድ እርሱ በምድር ባሠለጠነን ሙያ ተጠቅመን አንዱ ሌላውን እንዲያገለግል፣ ፍቅር በምድር ላይ እንድትመሠረትና እንድትሰፋ እንዲሁም እንድትሠለጥን ማድረግ ነው፡፡ በቅንነት ሆነን ሰውን እንደተሠማራንበት የሥራ መስክ  ያገለገልነው እንደሆነ እግዚአብሔር በእኛ ደስ ይሰኛል፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ “ሊሠራ የማይወድ ቢኖር አይብላ” (፩ተሰሎ.፫፥፲)ያለበት ምክንያት፡፡ ሊሥራ የማይወድ ሰው ፍቅርን ያጠፋታል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር አንዱ አንዱን የሚረዳበትን የተለያየ ስጦታ መስጠቱ ዓላማ በሥራ ምክንያት መተሳሰብና ፍቅር በምድር እንዲመሠረት ለማድረግ ነውና፡፡ ለክርስቲያን ሥራ መሠረታዊ መብቶቹን(ፍላጎቱን) የሚያሟላበት ብቻ አይደለም፡፡ እንዳውም መብልና መጠጥ እንዲሁም ልብስ ለእርሱ አስቀድሞ የሚሻቸው መሠረታዊ ፍላጎቶቹ አይደሉም፡፡ የአንድ ክርስቲያን መሠረታዊ ፍላጎቶች የእግዚእብሔር ጽድቅና መንግሥቱ ናቸው(ማቴ.፮፥፴፫)፡፡ ስለዚህም ሥራ ለክርስቲያን ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ የሚለውንም አምላካዊ ትእዛዝ በተግባር የሚያሳይበት መድረኩ ነው፡፡ ስለዚህም ሥራውን እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት ሲል በፍቅር ይሠራል፡፡ 
ክርስቲያን በድካሙ ከሚያገኘው ወዋገጋወው በተጨማሪ ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያገኘውን ታላቅ የሆነ በረከት ከግምት ውስጥ በማስገባት ሥራውን በእግዚአብሔር ፊት እንደሚሠራ በቅንነትና በፍቅር ያከናውናል፡፡ ከዚህም የተነሣ እግዚአብሔርን ከማያውቁ ሕዝቦች በተለየ ልዩ የሆነ በረከትን ከአምላኩ ዘንድ ይቀበላል፡፡ እነዚህን መንፈሳዊ በረከቶች ክርስቲያን የሆነ ብቻ የሚያስተውላቸው በረከቶች ናቸው፡፡ እነርሱም የመንፈስ ፍሬዎች የተባሉትን ማለትም ፍቅር፣ ደስታ፣ ሰላም፣ ትዕግሥት፣ ቸርነት፣ በጎነት፣ እምነት፣ የዋሃት ራስን መገግዛትን ገንዘቡ ያደርጋል፡፡(ገላ.5፡22) 
ቅዱስ ጳውሎስም ስለዚህ ሲያስተምር እንዲህ ይላል “የእግዚአብሔርን ፈቃድ እንደሚያደርጉ እንደ ክርስቶስ ባሪያዎች እንጂ ለሰው ደስ እንደምታሰኙ ለታይታ የምትገዙ አትሁኑ ለሰው ሳይሆን ለጌታ እንደምትገዙ በትጋትና በበጎ ፈቃድ ተገዙ ባሪያም ቢሆንም ጨዋ ሰው እያንዳንዱ የሚያደርገውን መልካም ነገር ሁሉ ከጌታ በብድራት እንዲቀበለው ታውቃላችሁና”፡፡(አፌ.፮፥፯-፱) የእግዚአብሔር ፈቃድ እንደሚያደርጉ ሲል ምን ማለቱ ነው? የእግዚአብሔር ፈቃድ እርስ በእርሳችን አንደባሮች እንድንተታዘዝ አይደለምን ? “በፍቅር እርስ በእርሳችሁ እንደባሮች ሁኑ”(ገላ.፭፥፲፬) እንዲል፡፡ ይህ በሥራ የተገለጠ ሲሆን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ተመላልሰናል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ “እያንዳንዳችን እንድናንጸው እርሱን ለመጥቀም ባልንጀራችንን ደስ እናሰኝ፡፡ ክርስቶስ ራሱን ደስ አላሰኘምና ነገር ግን አንተን የነቀፉበት ነቀፋ ወደቀብን ተብሎ አንደ ተጻፈ ሆነበት” ብሎ ገለጸው፡፡(ሮሜ.፲፭፥፪-፫) ስለሆነም ቅዱስ ጳውሎስ በሥራ ምክንያት ከእግዚአብሔር ከምናገኘው በረከት የተነሣ “ለሥራ ከመትጋት አትለግሙ” ብሎ ይመክረናል፡፡ በዚህም ከሌሎች ይልቅ እኛ ክርስቲያኖች ከእግዚአብሔር ታላቅ ዋጋን እናገኛልን፡፡
 በእግዘአብሔር የማያምኑ ሰዎች ሥራ በመሥራታቸው የሚያገኙት በረከት ቢኖር ምድራዊ በረከትን ብቻ ነው፡፡ እኛ ግን መንፈሳዊ በረከትን አስተባብረን እናገኛለን፡፡ ምን እንኳ ይህ ምድራዊ በረከት ለክርስቲያን እንደ ድርጎ የሚቆጠር ቢሆንም እግዚአብሔርን ከማያውቁት ጋር የሚያገኘው በረከት ሲተያይ የሰማይና የምድር ያህል ልዩነት አለው፡፡
 ክርስቲያን በምድር በትጋት በመሥራቱ ምድራዊ የሆነውን በረከት እንደ እርሱ በሥራ ከተጋው ኢአማኒ ጋር አኩል ቢያገኝም ለእርሱ ብቻ በሚሰጠው መንፈሳዊ በረከቶች ምክንያት ግን ከኢአማኒው በእጅጉ ተጠቃሚ ነው፡፡ ስለዚህም ክርስቲያን በምድር ለሥራ የሚተጋው አላፊ የሆነውን ገንዘብ ለማግኘት ወይም ገንዘብን ለማከማቸት ሳይሆን ሥራውን በቅንነት እና ሰዎችን ከማፍቀር የተነሣ በመሥራቱ እንደ እግዚአብሔር ካህንነቱ(royal priesthood) በሥራው ወንጌልን በመስበክ ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ምርኮን ያመጣ ዘንድ ነው፡፡ ስለዚህም ክርስቲያን ይህን ዓላማ አድርጎ እግዚአብሔር አምላክ በዚህ ምድር ባቆየው እድሜው ሁሉ በጎ ሥራን ለመሥራት የሚፋጠን ከሆነ ከቶ በገንዘብ ፍቅር ሊወድቅ አይችልም፡፡
ምንም እንኳ እግዚአብሔር አምላክ ባለጠጋ ቢያደርገን ብልጥግናችን እኛን ግመል አሳክሎ በመርፌ ቀዳዳ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንድንገባ የሚያደርገን አይደለም፡፡ ምክንያቱም ከገንዘብ ይልቅ በእግዚአብሔር ዘንድ የምናገኘውን ታላቅ በረከት ተስፋ አድርገን እንሠራለንና፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ልብ ያሰበውን ኩላሊት ያመላለሰውን የሚያውቅ አምላክ ነውና በክርስትና ሽፋን የገንዘብ ጥምን ለማርካት ሲባል የሚደረጉ ድካሞች ከእኛ ዘንድ ሊወገዱ ይገባቸዋል፡፡ እግዚአብሔርን ማታለል አይቻለንም፡፡ ሊያታልል የሚሞክር ካለ ሳይቀጣ አይቀርም፡፡ ግዴለም አስቀድመን እግዚአብሔርን ፈርተን ሰውን በተሠማራንበት የሥራ መስክ በቅንነትና በፍቅር እናገልግለው፡፡ እንዲህ ፈጽመን ከተገኘን ፍሬውን ወዲያው እንሰበስባለን፡፡ እግዚአብሔር በምድራዊውም በሰማያዊውም በረከት ይባርከናል፡፡
v መንፈሳዊ በረከት
ምድራዊ በረከት ውስጥ መንፈሳዊ በረከት እንዳለ ተመልክተናል፡፡ ይህ በረከት ግን ከእኛ ድካም ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ሌላኛው ከእኛ ድካም ጋር ያልተያያዘ በረከት መንፈሳዊ በረከት ይባላል፡፡ መንፈሳዊ በረከት ሰማያዊውን ደጅ አንኳክተን የሚሰጠን በረከት ነው “ለምኑ ይሰጣችኋል፣ፈልጉ ታገኙማላችሁ፣ መዝጊያውን አንኳኩ ይከፈትላችኋል”(ማቴ.፯፥፯)  ወይም “ትጉ ጸልዩ መንፈስስ ተዘጋጅታለች ሥጋ ግን ደካማ ነው”(ማር.፲፬፥፴፰)እንዲል ከላይ ከአምላካችን የምናገኘው በረከት ነው፡፡ በዚህም በረከት ውስጥ ልዩ ልዩ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን የሚያገለግሉ የመንፈስ ቅዱስ ሥጦታቸዎች ይገኙበታል፡፡ ለምሳሌ በመንፈሳዊ እውቀት መጎልበት፣ምሥጢራትን ማስተዋል፣ ሰማያዊውን ዓለም በዚህ ምድር ሆኖ መረዳት፣ የእርሱ ቤተመቅደስ በሆነው በሰውነታችን ውስጥ ንጉሣችን ክርስቶስ በልብሱ ዘርፍ ሰውነታችንን አልብሶት በቅዱሳን መላእክት ሲመሰገን መመልከት እና ዐይን ያላየው ጆሮም ያለሰማውን  ለቅዱሳን ከተሰጡት መንፈሳዊ በረከቶች ተሳታፊ መሆን ይገኙበታል፡፡
ስለዚህ መንፈሳዊ በረከት ጌታችን ሰውነታችንን እርሻ አድርጎ ቃሉን በዘር መስሎ በእኛ ሰውነት ላይ በመዘራቱ ምክንያት ሠላሳ ስልሳ እና መቶ ፍሬ የምናፈራበት መንፈሳዊ አዝመራ ነው(ማቴ.፲፫፥፩-፳፫) ፡፡ ወይም ለባሮቹ ለአንዱ አምስት ለአንዱ ሁለት ለአንዱ ደግሞ አንድ መክሊት በመስጠቱ ምክንያት እነዚያ መክሊቱ የተሰጣቸው ወገኖች መክሊቱን በመጠቀም የሰበሰቡት ትርፍ እርሱ መንፈሳዊ በረከት ይባላል፡፡ (ማቴ.፳፭፥፲፬-፴) ነገር ግን መንፈሳዊ በረከቶችን እናፈራባቸው ዘንድ የተሰጡን እነዚህን ጸጋዎች ያልተጠቀምንባቸው ከሆነ ወገኔ ሆይ እጅግ አስፈሪ የሆነው የእግዚአብሔር ቁጣ በእኛ ላይ እንደሚነድ ልብ በል፡፡ ጌታችን በቁጣ ሆኖ እንዲህ ይለናል “አንተ ክፉና ሃኬተኛ ባሪያ ካልዘራሁበት እንዳጭድ ካልበተንኩበት እንድሰበስብ ታውቃለህን ? ስለዚህ ገንዘቤን ለለዋጮች አደራ ልትሰጠው በተገባህ ነበር እኔም መጥቼ ያለኝን ከትርፉ ጋር እወስደው ነበር፡፡ ስለዚህም መክሊቱን ውሰዱበት አሥር መክሊትም ላለው ስጡት ላለው ይሰጠዋል ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል፡፡ የማይጠቅመውን ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት በዚያም ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል፡፡”(ማቴ.፳፭፥፳፮-፴) አንዲሁም ቅዱስ ጳውሎስ “ብዙ ጊዜ በእርሱዋ ላይ የሚወርደውን ዝናብ የምትጠጣ መሬት ለሚያራሱአትም ደግሞ የምትጠቅምን አትክልት የምታበቅል ከእግዚአብሔር በረከትን ታገኛለችና እሾህና ኵርንችትን ግን ብታወጣ የተጣለች ናት ለመረገምም ትቀርባለች መጨረሻዋም መቃጠል ነው፡፡አለ (ዕብ. ፮፥፯) ኦ እንዴት የሚያስፈራ ቃል ነው፡፡ ጌታችን ስለፍቅር እኛን የሚበቀለን በቀል እንዴት ጽኑ ነው!! ጌታ ሆይ ይህ እንዳይሆንብን ማስተዋልን ስጠንና ፈቃድህን ፈጻሚዎች አድርገን፡፡......
ቀጣዩ ክፍል






እያንዳንዳችን ከእግዚአብሔር አምላክ ዘንድ በመንፈስ ቅዱስ የተለያዩ ጸጋዎችን ተቀብለናል፡፡እነዚህን መንፈሳዊ ጸጋዎችን በሁለት እንከፍላቸዋለን፡፡
1.    በተፈጥሮ ከእኛ ዘንድ ያልነበሩ ነገር ግን ከእግዚአብሔር የምናገኛቸው

 እነዚህንም የመንፈስ ቅዱስ የጸጋ ስጦታዎች በሁለት እንከፍላቸዋለን፡፡

ሀ. ገና ክርስትና ስታብብ ክርስትናን ለማስፋፋት ሲባል ለጊዜው ብቻ የተሰጡ ጸጋዎች

 ከጊዜው ነባራዊ ሁኔታ አንጻር ይጠቅሙ ከነበሩ ነገር ግን አሁን  ስለማይጠቅሙ ከቀሩ ጸጋዎች መካከል በልዩ ልዩ ቋንቋ(በልሳን) መናገርና ትንቢትን መናገር ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ እነዚህና ሌሎች ጸጋዎች ወንጌልን በዓለም ዙሪያ ለማስፋፋት በጊዜው እጅግ አስፈላጊ ነበሩ፡፡ አሁን ግን ወንጌል ከሰማይ በታች ተሰብካ አብቅታለች በእኛ ዘመን ሳይሆን በሐዋርያት ዘመን “ያም ወንጌል ከሰማይ በታች ባለው ፍጥረት ሁሉ ዘንድ የተሰበከ ነው አኔም ጳውሎስ የእርሱ አገልጋይ ሆንሁ”(ቆላ.፩፥፳፫)እንዲል፡፡የሐዋርያት ስብከት በምደር ሁሉ ተሰምቷል፡፡ስለዚህ አሁን እነዚህ ጸጋዎች አስፈላጊዎች ስላልሆኑ አሁን አይሰጡም ምክንያቱም አሁን ቤተክርስቲያንን የሚጠቅሙ ወይንም ማኅበሩን የሚያንጹ አይደሉምና፡፡
ለ. ዘመን ሳይሽራቸው እስካሁን ድረስ የሚሰጡ ጸጋዎች ፡፡
 ከእግዚአብሔር በቀጥታ የምንቀበላቸው እስካሁን ድረስ ከሚያገለግሉን ጸጋዎች መካከል ጥበብን መናገር፣ እውቀትን መናገር፣ የመፈወስ ስጦታ፣ መናፍስትን የመለየት፣ ተአምራትን የማድረግ ጸጋዎች፣ ለቤተክርስቲያን ጥቅም እስካሁን የሚሰጡ ናቸው፡፡
ከክርስቶስ የበለጠ ነቢይ አለተነሣምና ወንጌል ደግሞ በዓለም ዙሪያ በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ተጽፎአልና፡፡ በአሁኑ ጊዜ ማንም እግዚአብሔርን አወቅ ብለን ልናስተምረው አንችልም ለእኛ የተሰበከው ወንጌል ለእነርሱም ተሰብኮአል፡፡ ከላይ የተመለከትናቸው ጸጋዎች በጊዜው ያገለገሉ ጸጋዎች ናቸው፡፡

2.   በውስጣችን የነበሩ ተፈጥሮአዊ ስጦታዎች ሆነው በመንፈስ ቅዱስ የታደሱ ጸጋዎች፡፡

 ሌሎቹ በመንፈስ ቅዱስ የምናገኛቸው ጸጋዎች ደግሞ በውስጣችን የነበሩትን ተፈጥሮአዊ ተሰጦዎች በአግባቡ እንድንጠቀምባቸው የሚረዱን ናቸው፡፡ ከመንፈስ ቅዱስ የጸጋ ስጦታዎች በፊት የነበሩን ተፈጥሮአዊ ችሎታዎች በማራ ውሃ ይመሰላሉ(ዘጸአ.፲፭፥፳፫-፳፭)፡፡ የማራ ውሃ መራራ ስለነበር ለመጠጣት አስቸጋሪ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ነቢዩ ሙሴ ስለዚህ ውሃ ለምኖ እግዚአብሔር አምላክ ውሃውን የሚያጣፍጠውን እንጨት ስላሳየው ያን እንጨት ውሃው ላይ ሲጥልበት ጣፈጠ፡፡
 አንዲሁ በኃጢአታችን ምክንያት መሮ የነበረው በተፈጥሮ የተሰጠን ችሎታ በመስቀሉ በተደረገልን ቤዛነት በኩል በመንፈስ ቅዱስ ጣፍጧል፡፡  አስቀድመን በዚህ ተፈጥሮአዊ ችሎታ ምንም ፍሬ አላፈራንበትም ነበር፡፡ ከዚህ ይልቅ ሰዎችን የምንበዘብዝበት መሳሪያ አድርገን ተገልግለንበታል፡፡ እንዲህ የሆነበትም ምክንያቱ በእነዚህ ተፈጥሮአዊ ስጦታዎች ላይ የእግዚአብሔር ፈቃድ  ምን እንደሆነ አስቀድመን ስለማናውቅ ነበር፡፡
 በአሁንም ዘመን በእነዚህ ተፈጥሮአዊ ስጦታዎች ላይ ያለውን የእግዚአብሔርን ዓላማ ጠንቅቀው ወይም ጨርሶውኑ ባለማወቃቸው ምክንያት የተሰነካከሉ ብዙዎች ናቸው፡፡ክርስቲያን ግን እንዲህ ሊሆን አይገባውም ሰውነቱ የእግዚአብሔር ቤተመቅደስ በመሆኑ ምክንያት በሰውነቱ ውስጥ በተፈጥሮ የተሰጡት ችሎታዎቹ ሁሉ የእግዚአብሔር ሆነዋል፡”፡ወይስ ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት በእናንተ የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደሆነ አታውቁምን ? በዋጋ ተግዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩት” (፩ቆሮ.፮፥፲፱፣፳) እንዲል ቅዱስ ጳውሎስ፡፡
እነዚህ ከእግዚአብሔር በተፈጥሮ ለሰው ሁሉ  የተሰጡ ልዩ ልዩ ስጦታዎችን አንዱን አካል ማለትን ክርስቶስን ለማገልገል የተጠቀምንባቸው ከሆነ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተትረፈረፈ መንፈሳዊ በረከቶችን እናገኝባቸዋለን፡፡እነዚህም ጸጋዎች የአስተዳደር ፣ የኪነ ጥበብ ፣ የፈጠራ ተሰጦዎች፣ የልዩ ልዩ የሙያ ባለቤትነት  አና አነዚህን የመሰሉ ሁሉ ይገኙበታል፡፡ሲተነተኑ የማስተዳደር ችሎታ፣ የሒሳብ አያያዝ ክሂሎት፣ ጸሐፊነት፣ የስዕል ባለሙያ ፣በድምፅ የማገልገል ችሎታ፣ አርቲስት፣ የሥነጽሑፍ፣ የፈጠራ ችሎታ ያለው፣ሐኪም፣ማሃንዲስ፣አማካሪ፣ወዘተ ናቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለመፈጸም የምንጠቀምባቸው በተፈጥሮ ከእግዚአብሔር ያለ አድሎ ለሰው ሁሉ የተሰጡ ጸጋዎች ናቸው፡፡ በእነዚህ ላይ የእግዚአብሔር ጸጋ ሲታከልበት እግዚአብሔር አንደሚወደው አድርገን ሥራዎችን እናከናውንባቸዋለን፡፡ ከዚህም የተነሣ  ታላላቅ በረከቶችን ከጌታችን ዘንድ እናገኛለን፡፡ 

No comments:

Post a Comment