Tuesday, June 12, 2012

እምነት እውነት ፍቅር በክርስትና



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/10/2004
አንድ በሀገራችን የነገሡ ንጉሥ ነበሩ፡፡ እኒህ ንጉሥ አንድ ወቅት “ልጅ ለአባቱ እምነት ለእናቱ እውነት ነው”ብለው ተናገሩ ይባላል፡፡ እንዲህ ብለው ከሆነ በእውነት ድንቅ የሆነን እውነት ተናገሩ፡፡ እኔ ግን እንዲህ እላለሁ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ሔዋን አዳምን ታውቀውና ታፈቅረው እንዲሁም እንደ እናትነቱና እንደ አባትነቱ ትታዘዘው ዘንድ፣ እርሱን ፈጥሮ ካበቃ በኋላ ልክ ልጅ ከእናቱ ተወልዶ በአካል እስኪገለጥ ድረስ ከእናቱ ሰውነት ውስጥ ተሰውሮ እንዲቆይ እንዲሁ በአዳም አካል ተሰውራ እንድትቆይ አደረጋት፡፡ እናት ልጁዋን በዐይን ለማየት እንድትናፍቅ እርሱዋን ለማየት አዳም በናፈቀ ጊዜ እግዚአብሔር ወልድ በሥጋ በመስቀል ላይ በተቀበለው ሕማም አርዓያ ሔዋንን ከአዳም ጎኑ አስገኛት፡፡ ስለዚህ ለአዳም አባታችን ሔዋን እውነቱ እንጂ እምነቱ አልነበረችም፡፡ እንዲሁም ሔዋን በአዳም አካል ውስጥ በነበረችበት ወቅት አዳም ፈጽሞ እንደሚወዳትና እንደሚያውቃት መጠን እርሱዋም እርሱን ፈጽማ ትወደውና ታውቀው ነበርና ለእርሱዋ አዳም እምነቷ ብቻ ሳይሆን እውነቷም ነው፡፡