Thursday, May 7, 2020

አማልክት ከምድር ሲወጡ አየን


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
29/08/2012
አዲስ አበባ
አምላኬ ሆይ ዛሬ ለጸሎቴ መልስን ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ፡፡ አውቃለሁ አንተ ርኅሩኅ አምላክ ነህ እንደ ፈቃድህ የሆነን ጸሎት የሚያቀርብን ሰው ትሰማዋለህ፡፡ ነገር ግን ጌታ ሆይ ዛሬ ምሽቱን በምንጣፌ ላይ ዕንቅልፍ ሳይጥለኝ ግን ጋደም ብዬ ወደ መቃብር ሥጋህ መውረዱን አሰብሁ፡፡ ነፍስ ከሥጋ መቃብር ከገባች ፈጥና ትወጣለች እንጂ ከእርሱ ጋር ምድራዊው መቃብር ውስጥ አትገባም፡፡ እንዲያ ቢሆን ግን ሰው ከነሕይወቱ ተቀብሮአል ይባላል እንጂ ነፍስ ወደ መቃብር ወረደች አትባልም፡፡ እንዲያም ቢሆን ሥጋ በነፍስ ኃይል በምድር ልብ ውስጥ መተንፈስ አትችልምና ነፍስ ፈጥና ሥጋን ትለያታለች፡፡ ነፍስም በዝግ መቃብር ሥጋን ተለይታ በአዳም ላይ የተፈረደውን ፍርድ ተቀብላ ወደ ሲኦል ትወርዳለች፡፡ እንዲህ ስል ከክርስቶስ ትንሣኤ በፊት ያለውን ጊዜ መናገሬ ነው፡፡  ጌታችን ግን ነፍሱን ከሥጋው በፈቃዱ ከለያት በኋላ በነፍሱ ወደ ሲኦል ወረደ፡፡ በምድር በጠባብ ደረት በአጭር ቁመት ተወስኖ በግዘፍ ሥጋ ለፍጥረት ሁሉ እንደተገለጠ በነፍሱም ወደ ሲኦል በመውረድ በመጠነ ነፍስ በሲኦል ለነበሩ ነፍሳት ሁሉ ተገለጠ፡፡  “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ብሎ በጌትነቱ ታያቸው፤ ነፍሳት ሁሉ በእርሱ አርአያና አምሳል ተፈጥረዋልና ጌታቸውን ለዩት “ከመንፈስህ ጋራ ብለው” እንደ ዮሐንስ መጥምቅ በደስታ ሰገዱለት፡፡ እነርሱም በቀኝ በኩል ከተሰቀለው ወንበዴ ጋር ወደ ገነት ከጌታ ጋር ገቡ፡፡