Thursday, August 9, 2012

የቅድስት ድንግል ማርያም ዘላለማዊ ድንግልና (የመጨረሻ ክፍል)



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
03/12/2004
ካለፈው የቀጠለ....
1.    በኩር (first born)
ሄልፊደስ እንደሚያስበው በኩር የሚለው ቃል ተከታዮች እንዳሉት የሚያሳይ ቃል ሳይሆን መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስረዳን በኩር የሚለው ቃል ትርጉሙ የእናቱን ማኅፀን መጀመሪያ የከፈተ ማለት ብቻ ነው፡፡ ስለዚህም ተከታይ ይኑረውም አይኑረውም የእናቱን ማኅፀን ለመጀመሪያ ጊዜ የከፈተ ሁሉ በኩር ይባላል ፡፡ ቃሉም ለዚህ ብቻ የሚያገለግል ነው እንጂ በኩር ለመባል የግድ ተከታይ ያስፈልገዋል የሚል ትርጉም የሚሰጠን አይደለም፡፡
ቅዱስ ጀሮም ለሄልፊደስ ሲመልስለት “Every only begotten son is a first born son, but not every first born is Only Begotten. But first born understood not only one who is succeeded by on others. By one who has had no predecessor” “ብቸኛ ልጅ ሁሉ የበኩር ልጅ ነው ፤ በኩር ሁሉ ግን ብቸኛ ልጅ ነው አንለውም ነገር ግን እኛ እንደምንረዳው በኩር የሚለው ቃል ተከታዮች ላሉት ብቻ ሳይሆን ተከታዮች ለሌሉትም የሚያገለግል ቃል ነው” ብሏል ፡፡ ለምሳሌ “ከሰው ወይም ከእንስሳ ቢሆን ለእግዚአብሔር ከሚያቀርቡት ሥጋ ሁሉ ማኅፀን የሚከፍት ሁሉ ለአንተ ይሆናል ነገር ግን የሰውን በኩራት ፈጽሞ ትቤዠዋለህ” ዘኁ.18፥15-16 የሚለው ኃይለ ቃል የሚያስረዳን ማኅፀን የሚከፍት ሁሉ (ተከታዮች ይኑሩትም አይኑሩትም) ለአሮን እንደተሰጠ ነው፡፡ በዚህም መሠረት በኩር ማለት እነ ሄልፊደስ እንደሚሉት ሳይሆን ለአንድ ለተወሰነ ድርጊት ብቻ የተሰጠ ቃል መሆኑን ማስተዋል እንችላለን፡፡ እርሱም የእናቱን ማኅፀን መጀመሪያ የከፈተ ማለት ነው ፡፡ /ዘጸ.13፥2/