Friday, August 16, 2013

የሙታን ትንሣኤና የጥምቀት ፍሬ እንዲህ ነው (1ቆሮ.15፡45-50)



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
10/12/2005 ዓ.ም
ቅዱስ ጳውሎስ “የሙታን ትንሣኤ እንዲህ ነው፡-” በማለት  ትንሣኤችንን ከለበስነው ሰማያዊ አካል ማለትም በጥምቀት ከለበስነው አዲስ ተፈጥሮ ጋር አዛምዶ ሂደቱን እንዲህ ይገልጥልናል፡፡ “በመበስበስ ይዘራል” ይህ አስቀድመን ስለለበስነው በዘር በሩካቤ ስላገኘነው ሰውነት ሲናገር ነው፡፡ ይህ አካል ሟችና በስባሽ አካል ነው፡፡ ስለዚህም “በመበስበስ ይዘራል” ያም ማለት ይሞታል፡፡ ይህም ስለትንሣኤችን ሊናገር እንደ መንደርደሪያ ያነሣው ነጥብ ነው፡፡ ሲቀጥል “ባለመበስበስ ይነሣል” ይላል፡፡ ይህ ቃል የሰውን ሁሉ ትንሣኤ ይናገራል እንጂ የክርስቲያኖችን ትንሣኤ ብቻ የሚናገር አይደለም፡፡ በትንሣኤ የሰው ዘር ሁሉ ለፍርድ ይነሣል፤ ዘለዓለማዊ ደስታን ወይም ዘለዓለማዊ ኩነኔን በኃጥአንና በጻድቃን ላይ በሚፈርደው በክርስቶስ የፍርድ ወንበር ፊት ቆሞ ይቀበላል፡፡(2ቆሮ.5፡10) ይህም አንዱ ለጽድቅ አንዱ ለኩነኔ መነሳቱን የሚገልጥ ነው፡፡
ቀጥሎ ግን በእውነት ክርስቲያን ለሆኑት ወገኖች የተሰጠው ትንሣኤ ምን እንደሚመስል ያስረዳል፡፡ ምክንያቱም በጥምቀት አዲሱን ሰው ብንለብሰውም ተመልሰን ለኃጢአት ባሮች ከሆንን በጥምቀት አዲሱን ሰው በመልበሳችን አንዳች ዋጋ እንደሌለን አስቀድሞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አስተምሮናልና “ወንድሞች ሆይ” ይለናል “ይህን ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ፡፡ አባቶቻችን ሁሉ ከደመና በታች ነበሩ” አለን፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ያላቸው የቆሮንቶስ ክርስቲያኖችን እንደሆነ አንባቢው ልብ ሊል ይገባዋል፡፡ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ከጣዖት አምልኮ ወደ እግዚአብሔር አምልኮ የመጡ ናቸው ወይም አሕዛብ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ለእነርሱ “አባቶቻችሁ ናቸው” ያላቸው እስራኤላዊያንን እንደሆነ አስተውሉ፡፡