Wednesday, August 22, 2012

ትንሣኤሃ ለቅድስት ድንግል ማርያም



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
16/12/2004
በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ለሕዝቡ ሲገለጥ በቃል ኪዳኑ ታቦት ላይ በማደር የምስክሩን ድንኳን በክብሩ ደመና ይከድነው ነበር፡፡(ዘጸአ.40፡34-38) ንጉሥ ሰሎሞንም የእግዚአብሔርን ቤተመቅደስ ሠርቶ ከፈጸመና የቃል ኪዳኗን ታቦት ካስገባ በኋላ እግዚአብሔር በቃል ኪዳኗ ታቦት ላይ በማረፍ መቅደሱን በክብሩ ደመና ከድኖት ነበር፡፡(2ዜና.7፡2-4) እነዚህ የእናታችን የቅድሰት ድንግል ማርያምና የእኛ ምሳሌዎች ናቸው፡፡
ሰውን የሚወድ እግዚአብሔር የሰውን ልጅ  በመተላለፉ ምክንያት ተሰነካክሎ ወድቆ እንዲቀር ስላልወደደ እግዚአብሔር ቃል በራሱና በአባቱ እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ ሰብእናችንንም በራሱ ቀድሶና አንጽቶ ከራሱ ጋር ለማዋሐድና እኛን ቤተመቅደሱ ለማሰኘት ቅድስት እናታችንን ማደሪያ ታቦቱ ትሆን ዘንድ መረጣት፡፡ ከእርሱዋም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሱዋ ነፍስ በመንሳት ተፀንሶ ተወለደ፡፡ በዚህም በነቢዩ አሞጽ አድሮ“በዚያ ቀን የወደቀችውን የዳዊትን ድንኳን አነሣለሁ”(አሞ.9፡11) ብሎ የተናገረውን ቃል ከዳዊት ዘር ከሆነች ከቅድስት ድንግል ማርያም በመወለድ ድንኳን የተባለችውን ሰብእናችንን አከበራት፡፡


Tuesday, August 21, 2012

ጌታችን ሆይ ስማን!!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
15/12/2004
ሞት ሞትን ስቦ እልቂትን እንዳያመጣብን አምላክ ሆይ ጠብቀን፡፡ ሥጋ ወዳዶች ለአንድ አጥንት እርሱም ሥጋ ላልተረፈው እርስ በእርሳቸው ተባልተው ይህን ምስኪን ሕዝብ እርስ በእርሱ እንዳያባሉ ከላይ ከአርዓያም ያለህ አምላክ ሆይ ተቤዠን፡፡ ደምን ለተጠሙ ሞት የልብ ልብ ሰጥቶአቸው ሰይፋቸውን በልባችን ውስጥ እንዳይስጉ፣ የዘለዓለም ቤተመቅደስህ ላደረግኸው ለዚህ ሰውነትህ እና ለእናትህ ልጆች ጌታ ሆይ እራራልን፡፡ ሕዝቡን ከእልቂት ጠብቅ፤ ከውጭ እኛን ሊውጡ ከሚያገሡ ከውስጥ አጥንቶቻችንን ሊቆረጣጥሙ ካሴሩ ጌታ ሆይ ታደገን፡፡
 ለያዕቆብ በሴኬማውያን ፊት ሞገስና ፍርሃት እንደሆንከው ጌታ ሆይ ለእኛም እንዲሁ ሁነልን፡፡ እኛንና የዚህችን ሀገር ሕዝብ ከጥፋት አድን፡፡ ሕዝብን ከሕዝብ የሚያስማማ መሪን ስጠን፡፡ ጌታ ሆይ! ኃይላችን አንተ ነህና አንተን አርዓያ አድርገን እኛ በዚህች ምድር መጻተኞች የሆንና ሀገራችን በሰማይ ያደረግን እንደሆነ ተረድተው፣ ሞት ድል የሚነሣት የዚህች ዓለም ሰዎች በእኛ ላይ እንዳይከፉ ፈቃድህንና ፈቃዳችንን አስታውቃቸው፡፡ በላይ በአርያም ያለህ ፈጣሪያችን ሆይ! አሁን ንቃ መንጎችህንም ጠብቅ! ጊዜው ሥጋ የተጣለበት ጊዜ ነውና ሥጋ ናፋቂዎች እርስ በእርሳቸው ተባልተው ሲያበቁ በመርዘኛ ጥርሳቸው ጤናማውን ሕዝብ ነክሰው እንዳያሳብዱትና እርስ በእርሱ እንዳያነካክሱት መጠጊያችን ሆይ! ስምህን ታዛችን አድርገናልና በአንተ እንመካ እንጂ አንፈር፡፡ ክብር ላንተ ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን!!!   

Monday, August 20, 2012

ደብረ ታቦር በቅዱስ ኤፍሬም(የመጨረሻ ክፍል)



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
14/12/2004
ክብር ለእርሱ ለወደደን ይሁንና ስለፍቅሩ የእኛን ሥጋ በመልበሱ ምክንያት እኛ የሰው ልጆች የክብሩን ብርሃን ለማየትና ድምፁንም ለመስማት በቃን፡፡ ስለዚህም ከእናታችን በነሣው ሰውነት በኩል ግርማ መለኮቱን  ለደቀመዛሙርቱ ባሳያቸው ጊዜ ሕሊናቸውን ስተው ወድቀው አልተጎዱም ነበር፡፡ ነገር ግን እያዩት እንቅልፍ ይዞአቸው ሄደ፡፡ በዚህም ስለምን ምክንያት በመለኮታዊው ግርማ ለእኛ እንዳልተገለጠልንና ስለምን ሥጋችንን መልበስ እንዳስፈለገው አስተማረን፡፡
ሦስቱ ዋነኞቹ ሐዋርያት የእርሱ ብርሃነ መለኮቱን ሳይሆን ግርማውን ባዩ ጊዜ እንቅልፍ የጣላቸውና ምን እንዳዩና ምን እንደሰሙ ያላስተዋሉ ከሆነ እንዲሁም ስምዖን ጴጥሮስ እንኳ የሚናገረውን ለይቶ እስከማያውቅ ድረስ ደርሶ መረዳታቸው የተወሰደ ከሆነ እንዴት እኛ የእኛን ሥጋ ሳይለብስ መለኮትን ልናይ ከእርሱ በቀጥታ ልንማር ይቻለን ነበር? እኔስ ለእኛ በመለኮታዊው ብርሃን ተገለጠልን ልል እንዴት ይቻለኝ ነበር? የእኛን ሥጋ ገንዘቡ ባያደርግ ኖሮ በምን መንገድ ራሱን ለእኛ ይገልጥልን ነበር?  በእኛው አንደበት ባይናገረን ኖሮ እንዴት ከመለኮት በቀጥታ ልንማር ይቻለን ነበር? በሚታይ አካል ለእኛ ባይገለጥልን ኖሮ እንዴት ተአምራቱን ሲፈጸም እርሱ እንደፈጸመው ተረድተን ልናምነው ይቻለን ነበር?


Saturday, August 18, 2012

ደብረ ታቦር በቅዱስ ኤፍሬም



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
12/12/2004
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት“እውነት እላችኋለሁ የሰው ልጅ በመንግሥቱ ሲመጣ እስኪያይ ድረስ ከዚህ ከሚቆሙት ሞትን የማይቀምሱ አንዳንዶች አሉ፡፡”(ማቴ.16፡28)የማለቱ ምክንያት በትንሣኤ እርሱን ለመቀበል በሕይወት የሚቆዩ እንዳሉ ሲያስረዳቸው ነው፡፡፡ ስለዚህም ጌታችን ሞትን ሳይቀምስ ከእርሱ ዘንድ የተነጠቀውን ኤልያስንና በእርሱ ሕያው የሆነውን ሙሴን ከመቃብር በማስነሣት ከሦስት ምስክሮች ጋር በደብረ ታቦር  ተራራ ላይ ግርማ መለኮቱን ገለጠልን፡፡ እነዚህ ሦስቱ አካላት ክርስቶስ ለሚመሠርታት መንግሥት(ቤተክርስቲያን) ምስክር የሚሆኑ  አዕማድ ናቸው፡፡(ቤተክርስቲያን ማለት በሥጋ ሞት የተለዩ የጻድቃን ነፍሳትና እንደ አልያስም ሞትን ያልቀመሱ ቅዱሳን እንዲሁም በምድር ሕያዋን ሆነን የምንኖር ክርስቲያኖች ኅብረት ማለት ናትና፡፡ ይህን  ምንም እንኳ በዐይናችን ለማየት ባንበቃም በእምነት ዐይኖቻችን  እንመለከተዋለን፡፡ በዚህም በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ለሐዋርያት የተገለጠው መገለጥም ለዚህ እምነታችን  እውነተኛ መረጋገጫችን ነው፡፡)

Thursday, August 16, 2012

አሁን ደግሞ ሹመቱ የካህናት ተራ ቢሆን!!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
09/12/2004
ጭንቅ የሆነው የቤተ ክርስቲያን የስደት ዘመን በንጉሥ ቆስጠንጥኖስ እስካበቃበት እስከ3ኛው ክ/ዘመን ድረስ ክርስቲያኖች ፍጹም በሆነ የቅድስና ሕይወት ውስጥ ይመላለሱ ነበር፡፡ በውጭ በአላውያን ነገሥታትና በጣዖት አምልኮ በታወሩ ሕዝቦች እንዲሁም በአይሁድ የሚቀበሉት መከራ እርስ በእርስ ያላቸው ፍቅር እንዲጠብቅና እንዲተዛዘኑ እንጂ ከቅድስና ሕይወታቸው እንዲወጡ አላደረጋቸውም ነበር፡፡ ነገር ግን ከ3ኛ ክ/ ዘመን ጀምሮ በንጉሥ ቆስጠንጥኖስ ክርስትና የመንግሥት ሃይማኖት ስትሆንና ነገሥታት በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ውስጥ ጣልቃ ሲገቡ ፍጹም የተባለው ክርስቲያናዊ ሥነምግባር እየጎደፈ ሕዝቡም መረን እየለቀቀ ውሻ ወደ ትፋቱ እንዲመለስ ብዙዎች ወደ ቀድሞ ግብራቸው ተመለሱ፡፡

Tuesday, August 14, 2012

እናንተስ ምን ትላላችሁ?

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

08/12/2004

አንባቢው እዚህ ላይ እንዲያስተዋልልኝ የምፈልገው ነገር ቢኖር በሐዲስ ኪዳን ክብር ይግባውና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንዴ በመስቀሉ በፈጸመው የድኅነት ሥራ እኛ በጥምቀት ስንተባበርና የተሰጠንን የልጅነት ጸጋችንን ጠብቀን ስንገኝ የምንድን መሆናችንን ነው፡፡ ድኅነቱ አሁን ተሰጥቶናል፡፡ የመዳንና ያለመዳን ምርጫው የተያዘው በእኛው እጅ ነው፡፡  ስለዚህም አንዴ በተቋጨና በተደመደመ ጉዳይ ዙሪያ ነው የምንነጋገረው፡፡ በመሆኑም ይህን ጽሑፍ ሳቀርብም ለእውቀት ያህል ብቻ እንደሆነ አንባቢው እንዲረዳኝ በትሕትና እጠይቃለሁ፡፡    


ነቢዩ ዳዊት ኃጢአት ከእናት ማኅፀን እንደሚጀመር ሲጽፍልን “ኃጥአን ከማኅፀን ጀምረው ተለዩ፤ ከሆድም ጀምረው ሳቱ፤ ሐሰትንም ተናገሩ፡፡”ሲለን(መዝ.57፡3-4) ኢዮብ ደግሞ ሕፃናት ገና ከማኅፀን ሳሉ ጽድቅን እንደሚጀምሩ ሲናገር “ደሃውን ከልመና ከልክዬ፣ የመበለቲቱን ዓይን አጨልሜ እንደሆነ፤ እንጀራዬን ለብቻዬ በልቼ እንደ ሆነ፣ ደሃ አደጉም ደግሞ ከእርሱ ሳይበላ ቀርቶ እንደ ሆነ፤ እርሱን ግን ከታናሽነቱ ጀምሬ እንደ አባቱ ከእኔ ጋር አሳድጌው ነበር፡፡ እርሱዋንም ከእናቴ መኅፀን ጀምሮ መራኋት”አለን፡፡(ኢዮ.31፡16-18)


Monday, August 13, 2012

የፍቅሩ ድልድይ (በቅዱስ ኤፍሬም)



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
07/12/2004
መግቢያ
በዚህ ርእስ ግሩም የሆነውን የቅዱስ ኤፍሬም መጽሐፍ ቅዱስን የመረዳት ጸጋውን እንመለከታለን ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለሰዎች በመጽሐፍ ቅዱስ በኩል ሲናገር  የሰውን ተፈጥሮአዊ ጠባይ በመጠቀም ነበር ፡፡ በፈጣሪና በፍጡር መካከል ያለውን ልዩነት ቅዱስ ኤፍሬም ታላቅ ገደል ወይም ጥልቁ ጸጥታ ብሎ ይጠራዋል፡፡ እንደ ቅዱስ ኤፍሬም አስተምህሮ በሰው ላይ የሚታዩ ተፈጥሮአዊ ጠባዮችን ለራሱ በመስጠት በእርሱና በሰው መካከል ያለውን ሰፊ የሆነ ልዩነት ያጠበበው እግዚአብሔር ራሱ ነው፡፡ እንዲህ ማድረጉ ክብር ይግባውና ለሰው ልጆች ካለው ጥልቅ ፍቅር የተነሣ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ለሰው የሚሰጠውን መጠሪያና ጠባይ ለራሱ ተጠቅሞባቸው እናገኛቸዋለን፤ እንደ ቅዱስ ኤፍሬም የአጻጻፍ ዘይቤ ደግሞ እንደ ልብስ ለብሶአቸው እናገኛቸዋለን፡፡
በብሉይ ኪዳን በእኛ ምሳሌ በመገኘት ራሱን የገለጠልን እግዚአብሔር አምላክ የተመሰገነ ይሁን፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር እንደሚሰማን ሊያሳውቀን ስለጆሮዎቹ ነገረን፤ እኛን እንደሚመለከተን ሊያስረዳንም ስለዐይኖቹ ጻፈልን፡፡ በዚህ መልክ በምሳሌአችን ተገልጦ እግዚአብሔር እኛን ይመክረናል ይገሥጸናል፡፡ እርሱ በባሕርይው ቁጣና ጸጸት የሌለበት አምላክ ሲሆን ስለእኛ ጥቅም እነዚህንም ግብሮች ለራሱ ሰጥቶ ተናገረን፡፡

Saturday, August 11, 2012

ግሩም ድንቅ የሆነው ተፈጥሮ!!!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊ
06/12/2004
በመንፈሳዊው ዓለም ሴት ልጅ ላስተዋላት ከገነትም ይልቅ የምትረቅ ናት፡፡ እኔ ስለሴት ልጅ ሳስብ በአግርሞት እሞላለሁ፡፡ አንድ ወቅት እግዚአብሔርን እንዲህ ብዬ ጠየቅሁት፡- ስለምን ነፍስን ለብቻዋ አልፈጠርካትም ? ስለምን ሥጋን ማኅደሯ አድርገኽ ፈጠርካት ?አልኹት፡፡ ለካ የነፍስ መዳኗና አምላኩዋን የማየቱዋ ምክንያት ሥጋ ነበረች!!! ይህም የተፈጸመው በሴት ልጅ በኩል ነው፡፡ ከእርሱዋ ክርስቶስ ከአጥንቱዋ አጥንት ከሥጋዋም ሥጋ  ሆኖ በአካል ተገለጠ፡፡ ስለዚህም ለእርሱ ከአጥንቱ አጥንት ከሥጋው ሥጋ ስለሆነች ሴት ተባለች፡፡ ሴት ማለት ደግሞ ክፋዬ ማለት ነው፡፡ ክርስቶስ ከቅድስት ድንግል ማርያም የአዳምን ባሕርይ ነስቶ በመወለድ የእርሱዋ ክፋይ(ልጅ) ሲባል እኛ ደግሞ ከእርሱ ከክርስቶስ ከአጥንቱ አጥንት ከሥጋው ሥጋው በመሆን የእርሱ ክፋዮች(ልጆች) እንባል ዘንድ በጥምቀት ከሞቱ ጋር ተባበርን፡፡ 
ሴቶች በሔዋን ሴት ሲባሉ፡፡ እኛ ወንዶች ደግሞ በክርስቶስ በተመሰለውና የአቤል ምትክ በሆነው ሴት በኩል ሴት ተባልን፡፡ ይህ ደግሞ ድንቅ ነው!!! 
ታዲያ ስለምን ሴት ልጅ ከነስሙዋ ድንቅ የሆነች ፍጥረት አትባል? ጥበብን የሚወድ እግዚአብሔር ሴት ልጅን የፍጥረት ጉልላት አድርጎ ፈጠራት፡፡ ከእርሱዋም ስሙ ጥበብ የሆነ ክርስቶስ ተወለደ፡፡ በክርስቶስም እኛ ክርስቲያኖች በጥምቀት ከአጥንቱ አጥንት ከሥጋው ሥጋ በመሆን ተወለድን፡፡ 
አዲሱም አፈጣጠራችን ሔዋን ከአዳም የተገኘችበትን አፈጣጠር ይመስላል፡፡ አዳም አንቀላፍቶ ሳለ ሔዋን ከጎኑ አጥንት ተገኘች፡፡ እንዲሁ እኛም ክርስቶስ በሞት እንቅልፍ አንቀላፍቶ ሳለ ከጎኑ በፈሰሰው ደም ተዋጅተን ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ ነጽተን ዳግም ተፈጠርን (because we are members of His body of His flesh and His bones) እንዲል፡፡(1ቆሮ.12፡27) ታዲያ በመንፈሳዊ መረዳት ውስጥ ያለ ሰው እንዴት በሴት ልጅ ተፈጥሮ  አይደነቅ?

ከ20 በላይ የሆኑ መንፈሳዊ ጉራማይሌ አጫጭር ጽሑፎች




በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/12/2004
(እነዚህ ጽሑፎች በተለያዩ ጊዜአት ፖስት ያደረጉኋቸው ናቸው)
ክርስትናና ፍቅር የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች
ፍቅርን የማያውቃት ክርስትናንም አያውቃትም ፡፡ ፍቅርን ሳያውቃት ክርስትናን አውቃታለሁ የሚል ሰው በእውነት እርሱ ሐሰተኛ ነው፡፡ በፍቅር ውስጥ ላለ ሰው ክርስትና ትፈቀራለች እንጂ አትከብድም፡፡ ክርስትና በፍቅር ውስጥ በሚገኝ ማስተዋል የምትመራ፣ የማታሰለች፣ ሁሌም ጥበበኛ የሆነች፣ ርኅሪት፣ ታጋሽ፣ አዛኝ፣ ሰው በሰው ማንነት ውስጥ ሆኖ ሰውነቱን እንዲያጣጥም የምትረዳ፣ ውስጡዋ ሰላም፣ ፍስሐ፣ ፍጹም ፍቅር የሞላባት፣ በተመስጦ የምታኖር የሰው ሰውነት ትርጉም ናት፡፡So let's build our faith on these, let's open our eyes with love and see all human beings with kindness. Don’t judge on others but appreciate their good deeds. Help each other without reward. In order to have pure mind, excellent thinking and healthy perspective, let us know God our lover and love all human beings on the eyes of God and love each other sincerely. Not in word but in deed.

ብሔርተኝነት
ክርስትና ዓለማቀፋዊት ናት ማንም በየትም ሀገር ይሁን ወደ እውነተኛይቱ የእግዚአብሔር መንግሥት በጥምቀት ከገባ በኋላ ክርስቲያን እንጂ የዚህ ሀገር የዚያ ሀገር አይባልም፡፡የተጠመቀ ሁሉ አንድ አካል ሆኖአል፡፡ የአንድ ሰማያዊት ሀገር ዜጋ ነው፡፡ለክርስቶስ ደግም አንዱ የአካል ክፍል ነው፡፡ይህን ቅዱስ ጳውሎስ ሀገራችን በሰማይ ነው ብሎ ይገልጽልናል፡፡ እጅ የምትሠራውን እግር አይሠራውም ዐይን የምትሠራውን ጆሮ አትሠራውም፡፡ ነገር ግን የአንዱ የአካል ክፍል ተግባር ሌሎችን የአካል ክፍሎች በአግባቡ እንዲኖሩ ያደርጋቸዋል፡፡ ስለዚህ ብሔርተኝነት በክርስትና አይሠራም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ነው ያስተማረን፡፡ በአንድ እምነት ውስጥ ካለን የሌሎች እውቀትና ልምድ ለእኛ የጎደለንን ሲሞላልን የእኛ ደግሞ የሌሎችን ጉድለት ይሞላል፡፡ ስለሆንም በዓለም አቀፍ ደረጃ በአንድ እምነት ሥር ያለን እርስ በእርሳችን ካልተመጋገብን ክርስትናን ኖርናት አያስብለንም አካለ ጎደሎዎች ነን እንጂ፡፡ ወገኖቼ ሆይ ብሔርተኞች አንሁን(Nationalist) ክርስትና ዓለማቀፋዊት ናት፡፡ ዓለማቀፋዊት የሆነችውን ብሔራዊት የምናደርጋት ከሆነ ራሳችንን ብንጎዳ እንጂ አንጠቀምም፡፡ ምክንያቱም ብሔርተኝነት በራሱ ምንፍቅና ነውና፡፡