Wednesday, January 18, 2012

ሞቴን አስቤ ልደቴን

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
03/06/2000 ዓ.ም የተጻፈ
ቀኑ እንዴት ነጎደ! ውስጤን ፍርሃት ፍርሃት አለው መቼም ሰው ሳያውቀው ወደ እግዚአብሔር መጣራቱ አይቀሬ ነው፡፡ አምላኩ ፊት ለፍርድ ሊቆም ነፍሱ ከሥጋው በተለየች ጊዜ ከትሞ ይኖርባት የነበረችውን ይህችን ግዙፍ ዓለም እንደ ሕልም እንደቅዠት ሆና ትረሳዋለች፡፡ በተቃራኒውም ይህችኛዋም ዓለም እርሱን ፈጥና ለዘለዓለም ትረሳዋለች፤ ስም አጠራርህም ከእነአካቴው ከሰው ሕሊና ይጠፋል፡፡ ወደ አምላካችን በሄድን ጊዜ ለዘለዓለም ከምንለያት ከዚህች ዓለም ሳለን ማወቅና መጠንቀቅ ያለንባቸውን እውቀቶችንና መንፈሳዊ ተግባራት ከፊት ይልቅ ግልጥ ሆነው በሰዋዊ አእምሮአችን ከምናቀው በላይ የመላእክትን እውቀት ገንዘባችን በማድረግ እናውቃቸዋለን፡፡ በፊቱ በቆምን ጊዜ እኛ በእርሱ ዘንድ የታወቅን፣ የጠጉራችንም ቅንጣት የተቆጠረች፣ በእርሱ ዘንድ የተራቆትን እንደሆንን ይበልጥ ግልጥ ይሆንልናል፡፡ በዚህ ምድር ሳለን በእምነት የምንረዳቸውን እውነታዎች በዚያን ጊዜ በግልጥ እናያቸዋለን፡፡

ጥምቀት በቅዱስ ኤፍሬም



ስብከት ወተግሣጽ ዘቅዱስ ኤፍሬም በሚለው መጽሐፌ ቅዱሱ ስለጥምቀት ያስተማረውን ትምህርት አስፍሬዋለሁ፡፡  ከእነዚህ ውስጥ አንዳንዱን እንድታነቡት እነሆ ብያለሁ፡፡

¨ ቅዱስ ኤፍሬም በጥምቀት የገሃነም እሳት ይጠፋል ይለናል፡፡
“የሰውነት ትኩሳት ከሰውነታችን በሚመነጨው ላቦት እንዲቀዘቅዝ እንዲሁ በጥምቀት የገሃነም እሳት ይጠፋል ፡፡”
ከዚህ ተነሥተን እንደ ቅዱስ ኤፍሬም ምልከታ የገሃነም ቦታዋ ከሰውነታችን ውስጥ ናት ማለት ነው፡፡ እሳቱ የማይጠፋ መባሉም ከእኛ ዘለዓለማዊነት ጋር የተቆራኘ መሆኑን መረዳት እንችላልን ፡፡ እኛ ዘለዓለማውያን ሆነን ስለተፈጠርን እሳቱም በሰውነታችን ውስጥ ዳግም አይቀጣጠልም፡፡ ይህ የሚያስረዳን ከጥምቀት በኋላ በራሳችን ፈቃድና ምርጫ  በድርጊትም ይሁን በቃል ጌታችንን እስካልካድነው ድረስ የገሃነም እሳት በሰውነታችን ውስጥ እንደማይኖር ነው፡፡
ስለዚህ መዳን አለመዳን በእጃችን እንደተያዘች መረዳት እንችላለን፡፡ ነገር ግን ይህን መብታችንን የማንጠቀምበት ጊዜ ይመጣል፡፡ እርሱም በምጽአትና በሞት ወደ እግዚአብሔር ለፍርድ በተወሰድንበት ወቅት ነው፡፡ እስከዛው ድረስ ግን የገሃነምን እሳት በሰውነታችን ላይ ማቀጣጠልም ይሁን ማጥፋት ወይም ሰውነታችንን የጌታ ቤተመቅደስ ማድረግ ወይም አለማድረግ የእኛ ፈንታ ይሆናል፡፡ 
 ¨ ቅዱስ ኤፍሬም ጥምቀትን ወደሰማያት የምንወጣጣበት መሰላል ብሎም ይጠራዋል፡፡ 
“እርሱ ወደ ጥምቀት በመውረድ ጥምቀትን መሠረተልን እርሱም በሠራልን ጥምቀት ወደ ሰማየ ሰማያት ተነጠቅን ፡፡”
 ¨ ቅዱስ ኤፍሬም መጠመቂያ ገንዳውን በክርስቶስ መስቀል ይመስለዋል ፡፡ በውስጡም ክርስቶስን ለብሰን እንወለዳለን ሲለን እንዲህ ይላል ፡፡