Saturday, March 31, 2012

ለአንድ ክርስቲያን የሰንበት ትርጉም


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
23/07/2004
አንድ ቅዱስ ሰንበትን ግርዘት ብሎ ይጠራታል፡፡ አንድ ጊዜ የተገረዘ ሰው ድጋሚ መገረዝ እንደማያስፈልገው እንዲሁ አንድ ጊዜ የተጠመቀም ድጋሚ መጠመቅ አያስፈልገውም፡፡ ስለዚህ ግርዘት የጥምቀትም ጥላ ነው ማለት ነው፡፡ በእርግጥ ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህ ሲያስረዳ “የሥጋን ሰውነት በመግፈፍ በክርስቶስ መገረዝ በእጅ ባልተደረገ መገረዝ በእርሱ ሆናችሁ ደግሞ ተገረዛችሁ”(ቆላ.2፡11)ይለናል፡፡
የተጠመቀ ደግሞ ከክርስቶስ ጋር በሞቱ በመተባበር የቀድሞውን አዳም ቀብሮ ዳግማዊውን አዳም ክርስቶስን ለብሶ ይነሣል፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው ሲጠመቅ “የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሊለብስ ይገባዋል” የሚለው የሐዋርያው ቃል በእርሱ ተፈጸመ ማለት ነው፡፡(1ቆሮ.15፡45፣52) ትንሣኤአችን ግን የሚተገበረው እኛ በዚህ ምድር ሳለን እንደ ክርስቶስ ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ ሕያዋን ሆነን የተመላለስን እንደሆነ ብቻ ነው፡፡

Friday, March 30, 2012

የመንፈስ ቅዱስ እናትነት



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
22/07/2004
የክርስቶስ ልብ የተባለ፤ የእግዚአብሔር አብ እስትንፋሱ እንዲሁም የፍጥረት ሁሉ አስገኚ የሆነው መንፈስ ቅዱስ ለእኛ ለተጠማቂያን ክርስቲያኖች እናታችን ነው፡፡ እርሱ የእግዚአብሔር ብቸኛ ልጁ የሆነውን አፍቃሪያችንን ክርስቶስ ኢየሱስን  ይበልጥ እንድናውቀውና እንድንረዳው እንዲሁም እርሱን አብነት አድርገ እርሱ የሞተለትን የሰውን ልጅ ለእግዚአብሔር አብ እንድንማርክና የእግዚአብሔር አብና የእግዚአብሔር ወልድ ልጆች፣ የክርስቶስ ወንድሞች(በጸጋ) በማድረግ እንድናቀርባቸው፤ በጥምቀት ካህናት፤ የክርስቶስ ወታደሮች፤ የእርሱ አባሳደሮች አድርጎ የሾመን ነው፡፡ ስንጠመቅ ለእያንዳንዳችን ራሱ በሰጠን ጸጋ እንደ እናት ሰብስቦ የጸጋውን ወተት የሚመግበን፣ በእርሱም ባገኘነው ክርስቶስን በሚመስል ተፈጥሮአችን በአእምሮም በአካልም በሞገስም ልክ እንደ እናት እቅፍ ድግፍ አድርጎ በፍቅር የሚያሳድገን እርሱ ነው፡፡


Thursday, March 29, 2012

ቅድስት ድንግል ማርያም ስለልጁዋ ስለወዳጁዋ እንዲህ አለች፡-(በቅዱስ ኤፍሬም)




ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
21/07/2004
“ቅድስት ድንግል ማርያም ስለልጁዋ ስለወዳጁዋ እንዲህ አለች፡-  እኔ የተሸከምኩት ሕፃን እርሱ እኔን የተሸከመኝ ነው ፡፡ እርሱ ክንፎቹን ዝቅ አድርጎ በእቅፎቹ ውስጥ አኖረኝ ፡፡ ከእርሱም ጋር ወደ ሰማየ ሰማያትም ተነጠቅኩ ፡፡ በዚያም በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ ለልጄ እንዲሆን ቃል ኪዳን ተገባልኝ ፡፡
ልጄን መልአኩ ገብርኤል ጌታዬ ብሎ ሲጠራው ሰማሁ ፣ ሊቀ ካህኑና አገልጋዩም (ስምዖን አረጋዊ) እርሱን በእቅፉ ይዞ ስለእርሱ ትንቢትን ተናገረ ፡፡ ሰብአ ሰገል በፊቱ ወድቀው ሲሰግዱለት፤ ሄሮድስም ንግሥናዬን የሚቀማ ሌላ ንጉሥ ተነሣብኝ ብሎ ሲርድ ተመለከትኩ ፡፡
ሙሴን አገኘዋለሁ ብሎ የዕብራዊያንን ሕፃናት ያስፈጀ ሰይጣን እርሱን በመስቀሉ ጠርቆ የሚያስወግደውን ሕፃን ለመግደል ሽቶ ሄሮድስን መሳፈሪያው አድርጎ ሕፃናትን ለመግደል ተፋጠነ፡፡ ነገር ግን ጠላቶቹ የሆኑትን ሊያድናቸው የመጣው ጌታ ወደ ግብፅ ተሰደደ ፡፡
ቀዳማይቱ ሔዋን በድንግናዋ የእፍረት ልብስ ለበሰች፡፡ ያንተ እናት ግን በድንግልናዋ ለሁሉ የሚበቃውን የክብርን ልብስ ደረበች ፡፡ እርሱዋ ሁሉን የሚያለብሰውን ጌታ ውሱን የሆነውን ሥጋዋን አለበሰችው ፡፡

Saturday, March 24, 2012

ኑ መጽሐፍ ቅዱስን በቅዱስ ኤፍሬም የንባብ ስልት እናንብበው



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
15/07/2004
መጽሐፍ ቅዱስን ቅዱስ ኤፍሬም እንዴት መነበብ እንዳለበት ሲያስተምር እንዲህ ይላል፡- “ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን በሦስት ዐይነት መንገድ ያነብቡታል፡፡ አንደኞቹ በስሜት ሆነው የሚያነቡ(with passion) ሲሆኑ የእነዚህ ወገኖች አነባበብ ፀሐይ በተኮሰች ጊዜ ሥር ስላልነበረው ደርቆና ጠውልጎ ፍሬ ሳያፈራ የቀረውን በጭንጫ መሬት ላይ የተዘራን ዘር ይመስላሉ፡፡(ማቴ.13፡20) ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለእነዚህ ወገኖች እንደገለጠው ለጊዜው መጻሕፍትን አንብበው እውቀትን በመጨበጣቸው ደስ የሚሰኙ ሲሆኑ፤  ነገር ግን በውስጡ ተጽፈው ያሉትን በጎ ምግባራት ለመፈጸም ከብዶአቸው ከማንበብ የተመለሱ ወይም ከንባብ ተሰላችተው ያቆሙ ናቸው፡፡
 ሌሎቹ ደግሞ አዋቂዎች ለመባልና ለመራቀቅ ሲሉ የሚያነቡ ናቸው፡፡ ጉድለት ለማግኘትም ብለው የሚያነቡ አሉ (without Passion)፡፡ እነዚህ ወገኖች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያለውን እውነት ከሌሎች ጋር ሊሟገቱበት እንጂ በውስጡ የያዘውን በጎ ምግባር ለመተግበር አስበው የሚያነቡ አይደሉም፡፡ ሦስተኞቹ ወገኖች ግን መጽሐፍ ቅዱስን በእግዚአብሔር ፍቅር ውስጥ ሆነው የሚያነቡ ናቸው፡፡ እነዚህ ወገኖች እያንዳንዷን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል እግዚአብሔርን በማፍቀር ሆነው የሚያነቡ ናቸው(with Love of God)"ይለናል፡፡


Friday, March 23, 2012

ነጻ ፈቃድና ቃና ዘገሊላ(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
15/07/2004
ስለእኛ መዳን ራሱን ዝቅ በማድረግ የባሪያውን መልክ ይዞ ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም በሆነ ትሕትና “በላተኛና የወይን ጠጅ ጠጭ፣ የቀራጮችና የኃጢአተኞች ወዳጅ”(ሉቃ.7፡34)ብለው ስም እስኪሰጡት ደርሶ ራሱን ዝቅ በማድረግ ከእናቱና ከደቀመዛሙርቱ ጋር በቃና ዘገሊላ በባሪያው በዶኪማስ ሰርግ ላይ በእንግድነት ተገኘ፡፡ በዚያን ጊዜ ለሰርጉ የተጣለው ወይን ጠጅ አልቆ ነበርና ሙሽራው ሲጨነቅ አይታ እናታችን ቅድስት ንጽሕት ድንግል ማርያም ልጁዋን ወዳጁዋን “ወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” በማለት ልመናን አቀረበችለት፡፡ ጌታችንም “አንቺ ሴት ካንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም”ብሎ መለሰላት፡፡(ዮሐ.2፡3-4) ይህ የጌታችን መልስ ቅድስት እናታችን ለልጁዋ ለወደጁዋ ልመና ስለማቅረቡዋ ምስክር ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህን አስመልክቶ የዮሐንስ ወንጌልን በተረጎመበት 21ኛው ድርሳኑ ለእኛ እንዲህ ብሎ ያስተምረናል፡፡

Saturday, March 17, 2012

"ከእባብም ክርስትናን እንማር፤ እንዴት?"

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
09/07/2004
ከአንድ የቅርብ ቅርብ ወዳጄ አንድ ታላቅ የሆነ ትምህርት ሰማሁ፡፡ ይህ ወዳጄ ነገር መሸፋፈን አይወድምና እንዲህ አለኝ “አንተዬ አንድ የአደባባይ ምስጢር ልንገርህ" ብሎ ይጀምርና በመቀጠል “ካበቁ ከበቃቁ ሰውነታቸውና አእምሮአቸው በኃጢአት ከድሃ ድሪቶ ይልቅ እጅግ ካደፈ በኋላ እንዲሁም ዓለሚቱን በኃጢአታቸው ከከደኗትና  ትውልዱን መንገድ አስተው የአጋንንት መጫወቻ ካደረጉ በኋላ ዓለም በቃኝ አሉ አሉ! እነ እማሆይ! እነ አባሆይ! ዋይ! ... ዋይ! .... ዋይ! ... እኒህ ጽድቅ በቆቤዎች ስለእኛ በመስቀል ላይ ስለተሠዋልን ስለአፍቃሪያችን ስለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንዳች ሳያስተምሩን እኛን ለሰይጣን  ዳርገውን ዓለም(ኃጢአት) በቃችኝ ብለው ቆብ አጠለቁ አሉ! ጉድ ነው! መቼም በኢትዮጵያችን ይህ የተለመደ የጽድቅ ማቋረጫ መንገድ ሆኗል ፤እድሜ ለምንኩስና!! መቼም ሰው ቆቡን ከየትም ያምጣው ከየት እርሱን አጥልቆ በአንዴው ጻድቅ ሆኖ ቁብ ይልብናል፡፡ እኽ ነው እንጂ ሌላ ምን ይባላል!! ግን ግን ልጆቻቸውን በሥርዐት ቀርጸው የሚያሳድጉና ለዓለም ብርሃን እንዲሆኑ የሚያበቁ እንዲሁም ክርስቶስ በእርሱዋ የሰው ልጅ መባልን ያላፈረባታን ቅድስት ድንግል ማርያምን በምግባራቸው የመሰሉ አንዳንድ ቅዱሳን ወላጆችም አይጠፉም፡፡

Wednesday, March 14, 2012

ትምህርተ ድኅነት (ክፍል ሁለት)


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
06/07/2004
እግዚአብሔር ቃል ሥጋ ማርያምን የመልበሱ ምክንያት ምንድን ነው ?
የእግዚአብሔር ቃል ሥጋ ማርያምን የመልበስ ምክንያትን በተመለከት ቅዱሳን አባቶች በተለይ ቅዱስ አትናቴዎስ ዘእስክንድርያ ሲያስረዳ እንዲህ ይላል ፡-
“በፍቅር እጆቹ ያበጀውን ፍጥረት በሰይጣን ተንኮል በመሰናከሉ ጠፍቶ እንዲቀር ማድረግ ርኅሩኅ የሆነው የእግዚአብሔር ባሕርይ አልፈቀደም ፡፡ በተቃራኒው ደግሞ እርሱ ፈታሔ በጽድቅ ኰናኔ በርትዕ ነውና እርሱ ራሱ የፈረደውን ፍርድ ማስቀረት ባሕርይው አልፈቀደም፡፡ እንዲህ ቢያደርግ ኖሮ እግዚአብሔር ቅን ፈራጅ ባላስባለው ነበር፡፡ ስለዚህም በአዳምና በሰው ልጆች ላይ የተፈደውን ፍርድ ከቅድስት ድንግል ማርያም በመወለድና ራሱ ፍርዱን በራሱ ላይ በማድረግ በሰው ልጆች ላይ የፈረደውን ፍርድ በራሱ አስወገደው” ይለናል ፡፡በእርግጥ ይህን በተመለከተ ቅዱስ ጳውሎስ “ኀጢአታችንን በራሱ ካነጻ በኋላ በሰማያት በግርማው ቀኝ ተቀመጠ” ብሎ ይገልጠዋል፡፡(ዕብ.1፡3)

ትምህርተ ድኅነት(ክፍል አንድ)


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/07/2004
ድኅነት የሚለው ጥሬ ትርጉሙ አንድ ጤናማ ያልሆነን አካል ወደ ቀደሞው ጤንነቱ መመለስ የሚለውን ትርጉም የሚሰጠን ቃል ነው፡፡ እንደ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፅንሰ አሳብ ደግሞ ከኃጢአትና ኃጢአት ካመጣው የነፍስም የሥጋም ሕመም መፈወስ ማለት ነው፡፡ ድኅነቱም የሚፈጸመው በቤተ ክርስቲያን በሚፈጸሙ ምሥጢራት ነው፡፡ እነዚህ ምሥጢራት ከክርስቶስ ጋር ቀጥተኛ ተሳትፎ እንዲኖረን ያበቁናል፡፡ ስለዚህም ኦርቶዶክሳዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ የተፈጸመልንን የማዳን ሥራ ለማስረዳት ስትል እንደ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን “እርቅ”(reconciliation) ወይም “ቤዛ” (redemption)  ወይም እንደ ፕሮቴስታንቱ “መቀደስ”(Justification) የሚሉትን ቃላት አትጠቀምም፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ቃላት በክርስቶስ የተፈጸመልንን የማዳን ሥራ አሟልተው ሊያስረዱ የሚችሉ ቃላት አይደሉምና፡፡ እርቅ ስንል በሁለት ጠበኞች መካከል የተደረገን መስማማትንና ወዳጅነትን የሚያስረዳን ቃል ሲሆን ቤዛ ስንል ደግሞ አንድ እስረኛን ወይም ባለእዳን ዋጋ ከፍሎ ማስለቀቅ ማለት ነው፡፡ እነዚህ ቃላት በውጭ ሊፈጸሙ የሚችሉትን ድርጊቶችን ሊያስረዱ የሚችሉ ቃላት እንጂ አንድ አካል ወደ መሆን መምጣትን የሚያስረዱ ሆነው አናገኛቸውም ወይም በድኅነት ሥራ የሁለቱን ወገን ተሳትፎ አሟልተው የሚያስረዱ ቃላት አይደሉም ፡፡


 መቀደስም ቢሆን ኃጢአትን ከመሥራት ተከልክሎ በቅድስና ሕይወት መመላለስን የሚያስረዳ ቃል ነው ፡፡ እንደውም እንደ ፕሮቴስታንቱ ዓለም አስተምህሮ አንድ ሰው ሊጸድቅ የሚችለው በእምነት እንጂ በሥራ አይደለም ፡፡ እንዲህም ስለሚሉ ክርስቶስን በተግባር ላለመምሰል ፈቃደኞች አለመሆናቸውን እንረዳለን ፡፡
እኛ ኦርቶዶክሳውያን ግን ሰው ሊድን የሚችለው በእግዚአብሔር ጸጋ ነው ፤ ነገር ግን ጸጋውን ለመቀበል የግድ እምነትና ምግባር ይዘን ልንገኝ ያስፈልገናልን ብለን እናስተምራለን ፡፡ ስለዚህም ቤተክርስቲያናችን ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራ ጋር ያለንን የእኛን ተሳትፎ እና ከእርሱ ጋር የተፈጸመውን ፍጹም አንድነት ለማስረዳት ስትል ድኅነት(Salvation or Sotoria) የሚለውን ቃል አብዝታ ትጠቀማለች፡፡ ይህን ቃል መጽሐፍ ቅዱስ በሐዲስ ኪዳን ብቻ  የክርስቶሰን የማዳን ሥራ ለመግለጽ ሲል ከአርባ ጊዜ በላይ ተጠቅሞበታል፡፡ 
 በክርስቶስ የማዳን ሥራ ላይ የእኛ ተሳትፎ የምንለውም፡- በጥምቀት ከክርስቶስ ጋር በሞቱ መተባበራችንን ፣  በትንሣኤውም ተካፋዮች መሆናችንን ፣ ከቅዱስ ሥጋውና ከክቡር ደሙ መቀበላችንን እንዲሁም በቤተክርስቲያን ከሚፈጸሙ ሌሎችም ምሥጢራት ተካፋዮች መሆንን ፣ በተጨማሪም በተግባራዊ ምልልሳችንም እርሱን መስለን በመገኘታችንም ጭምር ነው ፡፡ ከምሥጢራት ያልተሳተፈ ወይም በተግባራዊ ምልልሱ እንደ ክርስቶስ ፈቃድ ያልኖረ ሰው ድኖአል ብላ ቤተክርስተያን አታስተምርም ፡፡ ስለዚህም  በክርስቶስ ያገኘነውንና በእርሱ የማዳን ሥራ የእኛ ሚና ምን እንደሆነ ለማስረዳት ስትል ቤተክርስቲያን ድኅነት የሚለውን ቃል ትጠቀማለች ፡፡ ይህንንም የተለመከተውንም አስተምህሮ ትምህርተ ድኅነት ብላ ሰይማዋለች ፡፡  
ቅድስት ቤተክርስቲያን ትምህርተ ድኅነት ስትሰጥ ከጥንተ ተፈጥሮአችን በመነሣት ነው ፡፡ ምክንያቱም ድኅነታችን ከአፈጣጠራችን ጋር በጥብቅ የተቆራኘ በመሆኑ ነው ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ የሰውን ልጅ በራሱ መልክና ምሳሌ ፈጠረው ፡፡ ፈጥሮም ካበቃ በኋላ ቅዱስ ጳውሎስ “እኛስ የክርስቶስ ልብ አለን”(ቆሮ.2፡16) እንዲል የእግዚአብሔርን አሳብንና ፈቃድ ያውቅና እንደ እርሱ ፈቃድና አሳብ ሥራውን ያከናውን ዘንድ የሕይወት እስትንፋስ የተባለውን መንፈስ ቅዱስ በንፍሃት አሳደረበት ፡፡ በንፋሃት ለአዳም የተሰጠው እስትንፋስ የተባለው መንፈስ ቅዱስ እንደሆነ እንረዳም ዘንድ ወንጌላዊው ዮሐንስ ጌታችን በሐዋርያት ላይ መንፈስ ቅዱስን በንፋሃት ማሳደሩን “እፍ አለባቸው ፡- መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ” በማለት ገልጾልን እናገኛለን ፡፡ (ዮሐ.20፡22) እንዲህም ስለሆነ ሥልጣኑ የተሰጣቸው ካህናት አዲስ ተጠማቂን  ካጠመቁት በኋላ እፍ በማለት “መንፈስ ቅዱስን ተቀበል” በማለት ሰውነቱን የጌታ ቤተመቅደስ እንዲሆን ያበቁታል ፡፡  
እንዲሁ በንፍሃት በአዳም ላይ ያደረው መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፈቃድ ምን እንደሆነ ይገልጥለት ዘንድ ነው ፡፡ በዚህ ታግዞ አዳም ዓለምን መግዛት ፍጥረታትን ማስተዳደር ቻለ ፡፡ እንዲህ ቢባልም ግን መንፈስ ቅዱስ በአዳምና በሔዋን ነጻ ፈቃድ ላይ ጣልቃ ይገባል ማለት ግን አይደለም ፡፡ ይህ እውነታ መንፈስ ቅዱስ በተቀበልነው በእኛ ክርስቲያኖች ላይ የሚታይ እውነታ ነው ፡፡ መንፈስ ቅዱስ በእኛ ሰውነት ውስጥ ከትሞ አለ ፡፡ ነገር ግን እኛ ለነፍሳችን  እንደነፍስ ነፍስ በመሆን እንዲመራን ፈቃደኞች እስካልሆንን ድረስ በሰውነታችን ይኑር እንጂ አንዳች ሥራን ሳይሠራ በዝምታ ይቀመጣል ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ነጻ ፈቃዳችንን ያከብራል ፡፡
ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእኛ ሰውነት ውስጥ ሥራውን እንዲሠራ ከፈቀድን ለእኛ እንደ ልብ ሆኖ የእግዚአብሔርን ፈቃድና አሳብ ያለአንዳች መደነቃቀፍ እንድንፈጽም ሲረዳን እናገኘዋለን ፡፡ እውቀታችንም ቅዱስ ጳውሎስ “ለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም በመንፈስ የሚመረመር ስለሆነ ሊያውቀው አይችልም”(1ቆሮ.2፡14) እንዲል  ከፍጥረታዊው ነፍስ የተለየ እጅግ የጠለቀና ቅዱስ ነው ፡፡
 እንዲሁ እግዚአብሔር አምላክ አዳምንና ሔዋንን ጥንት ሲፈጥራቸው ነጻ ፈቃድ በመስጠት አክብሮአቸው ነው ፡፡ ነጻ ፈቃዳቸውንም ይተገብሩባት ዘንድ ክፉና ደጉን የምታሳውቀውን ተክል በገነት መካከል አኖረ ፡፡ “በገነት መካከል ካለው ከዛፉ ፍሬ … አንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ አትንኩትም ፡፡”(ዘፍ.3፡3)ብሎ ፈቃዱን ገለጠላቸው ፡፡ የእርሱ ፈቃድ ክፉና ደጉን ከሚያሳውቅ ተክል እንዳይበሉ እንደሆነ ነገር ግን ላለመብላት እንዳልተከለከሉ ቢበሉት ግን ሞትን እንዲሞቱና ከእርሱም እንዲለዩ አሳወቃቸው ፡፡    
ነገር ግን አዳምና ሔዋን በውስጣቸው ያደረውን የመንፈስ ቅዱስን ፈቃድ ቸል በማለት በራሳቸው ማስተዋል ተደግፈው ከእነርሱ በክብር በእጅጉ የሚያንሰውን የእባብን ምክር በማዳመጥ ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጪ ክፉና ደጉን ከሚያሳውቀው ዕፀ በለስ በሉ ፡፡በዚህም ምክንያት መንፈስ ቅዱስ ከእነርሱ በመለየቱ ከእግዚአብሔር አምላክ ጋር የነበራቸው ኅብረት ተቋረጠ ፡፡ ስለዚህም በእነርሱ ምክንያት እግዚአብሔርን የምንመስልበት አርአያ ተጎሳቆለ ፣ ሞት በእኛ ላይ ሠለጠነብን ፣ ከሕያዋን ቦታ ከንግሥናችን ሥፍራ ከገነት ተሰደደን ወደ ተፈጠርንባትም ምድር ተመለስን ፣ ምድርም በእኛ ምክንያት ተረገመች ፣ ጽድቅንም መፈጸም ተሳነን ፣ ማስተዋላችን ተወገደ ፣ ድንቁርና ወረሰን በዚህም ምክንያት ክፉ ለሆነው ለሰይጣን ፈቃድ ተገዛን ፡፡
ቢሆንም እግዚአብሔር አምላክ የሰውን ልጅ ከገነት አውጥቶ ወደዚች ምድር መስደዱ ስለጠላው አልነበረም ፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሔርን ፈቃድ መውጣት ምን ያህል ከክብር እንዳዋረደው ተረድቶ እንዲጸጸትና በንስሐ ወደ እርሱ እንዲመለስ በመፍቀዱ ነው ፡፡ እግዚአብሔርም የአዳምን ክፉ ምርጫ ስለሚያውቅና በኋላም እንዲጸጸት ስለተረዳ የሰውን ዘር ሁሉ ሊያድን ሰው እንደሚሆን እርሱን ያሰነካከለውንም ሰይጣን በሚለብሰው ሰውነት ድል እንዲነሣውና ወደ ቀደመው ክብሩ እንደሚመልሰው ጌታችን “በአንተና በሴቲቱ መካከል፣ በዘርህና በዘሩዋ መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል አንተም ሰኰናውን ትቀጠቅጣለህ ፡፡”(ዘፍ.3፡15) ብሎ አስቀድሞ ተናገረ ፡፡ ይህንንም የእግዚአብሔርንም አሳብ አዳም ተረዳ ፡፡  
 በአንተ የተባለው ሰይጣንን ነው ፣ በሴቲቱ የተባለው በድንግል ማርያም ወይም በቤተክርስቲያን ነው ፣ በዘርህ ሲል የዲያብሎስ  የግብር ልጆችን ሲሆን ፣ በዘርዋ የተባለው ክርስቶስ  ነው ፡፡አንድም የቤተክርስቲያን ልጆችን ነው ፡፡ ይህን በራእይ.12፡17 “ዘንዶው በሴቲቱ ላይ ተቆጥቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ የጠበቁትን የኢየሱስም ምስክር ያላቸውን ከዘርዋ የቀሩትን ሊዋጋ ሄደ በባሕርም አሸዋ ላይ ቆመ ፡፡” በሚለው ኃይለ ቃል ወይም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም ግን በነጻነት የምትኖር ናት እርሱዋም እናታችን ናት …እኛም ወንድሞች ሆይ እንደ ይስሐቅ የተስፋ ቃል ልጆች ነን ፡፡”(ገላ.4፡26-31)ብሎ ባስተማረው ትምህርቱ ማረጋገጥ ይቻላል ፡፡ ከዚህም በኋላ ነበር አዳም አጋሩ ትሆን ዘንድ ለተሰጠቸው ሴት “ሔዋን” ብሎ ስም ያወጣላት ትርጓሜውም የሕያውን ሁሉ እናት ማለት ነው ፡፡ ከእርሱ ወገን ከሆነችው ከቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር በሥጋ በመወለድ አዳምንና ልጆቹን ወደ ቀደመ እሪናቸው እንዲመልሳቸው በማወቁ ነበር ሔዋን ብሎ ስም የሰጣት ፡፡ የአዳምንም እምነት የተመለከተ ሥላሴ እግዚአብሔር ቃል ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ሰውን ከቀድሞው ክብሩ በላቀ መልኩ እጅግ እንደሚያከብረው ሊያረጋግጥለት “ እነሆ አዳም መልካሙንና ክፉውን ለማወቅ  ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ”(ዘፍ.3፡ )ማለቱ ፡፡
ይህም የእግዚአብሔር ቃል ሥጋ ማርያምን በመልበስ አዳምና ልጆቹን ማዳኑ አይቀሬ መሆኑን የሚያሳይ ኃይለ ቃል ነው ፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ ክርስቶስን ዳግማዊው አዳም ብሎ ሲጠራው አላፈረም “ፊተኛው አዳም ሕያው ነፍስ ያለው ሆነ ተብሎ ተጽፎአል ኋለኛው አዳም ግን ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ሆነ ፡፡” አለን ፡፡ (1ቆሮ.15፡45) 



Tuesday, March 13, 2012

አንድ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስን እንዴት ይረዳው?








በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
04/07/2004
ይህን ጽሑፍ አንድ ወንድሜ የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብን በተመለከተ ለጠየቀኝ ጥያቄ የሰጠሁት መልስ ነው፡፡ ይህም በዚህ ድኅረ ገጽ ላይ ይገኛል ነገር ግን ለሁሉ አንባቢያን እንዲደርስ በመፈለጌ ርእስ ሰጥቼ እንዲህ አቅርቤዋለሁ፡፡  
ውድ ወንድሜ ሆይ እርግጥ ነው መጽሐፍ ቅዱስን ወዲያው ለመረዳት አስቸጋሪ ነው፡፡ ምክንያቱም በአንድ ምዕራፍ ውስጥ ብዙ በይዘታቸው የተለያዩ መልእክቶች ስለሚተላለፉ ነው፡፡ ይህ የአንድ መንፈሳዊ መጽሐፍ ጠባይ ነው፡፡ እንደ መጽሐፍ ቅዱስ ዓይነት አጻጻፍ በጥንት ቅዱሳን አባቶች መጻሕፍት ላይ ይገኛል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደ አንድ ዛፍ ነው፡፡ ግንዱ አንድ ሲሆን ብዙ ቅርንጫፎችና እጅግ ብዙ ቅጠሎች ያሉት ሲሆን ፍሬው ግን ምንም በቁጥር አንዱ ቅርንጫፍ ከአንዱ ቅርንጫፍ ይበልጥ የሚያፈራ ቢሆን አንድ ነው፡፡ ይህን ላስረዳህ፡፡ ግንዱ አንድ እግዚአብሔር ነው፡፡ ወይም ሥሩ እግዚአብሔር አብ ነው ግንዱ ክርስቶስ ነው ለዛፉ ሕይወት የሚሆነውና ፍሬ እንዲሰጥ የሚያደርገው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡




Monday, March 12, 2012

ምጽዋት በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
03/07/2004 
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲያስተምር መብራታቸውን ከዘይታቸው ጋር አስተባብረው ይዘው የተገኙት ደናግላን ወደ ሰርጉ እንዲታደሙ እንዳደረጋቸው ገልጦልናል፡፡ በዘይት የተመሰለው ተግባራዊ ምልልሳችን ሲሆን እርሱም የእግዚአብሔር ስም በእኛ ይበልጥ እንዲከብርና እንዲመሰገን ያደርገዋል፡፡ ይህም የጽድቅ ሕይወታችን ለሌሎች ብርሃን ለመሆን እንድንበቃ ያግዘናል፡፡ ስለዚህም ነው ጠቢቡ ሰሎሞን “የጻድቅ መንገድ ግን እንደ ንጋት ብርሃን ነው” ማለቱ፡፡ (ምሳ.4፡18) መንገድ የተባለው ለክርስቶስ ፈቃድ መታዘዛችን ነው፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ በማለት ያስተምረናል፤
“በመቅረዛችን ውስጥ ዘይቱን በመጨመር መንፈሳዊውን መብራት ደምቆ እንዲበራ እናድርገው፡፡ መሥዋዕት አድርገን የምናቀርበውን መብራት ሰማያዊውን ሙሽራ ለመቀበል የሚያገለግል መሥዋዕት ነው፡፡ እንዲያም ስለሆነ ከመቅረዙ ውስጥ ተጨማሪ ዘይት ሊጨመርበትና እስከ ላይ ደርሶ ሊበራ ይገባዋል፡፡ እንዲህ ካልሆነ መቅረዝ በመያዛችን ብቻ ከእግዚአብሔር ዘንድ አንዳች ዋጋን የምናገኝ አይደለንም፡፡ እንዲህም ስለሆነ ጌታችን “ምሕረትን እወዳለሁ መሥዋዕትን አይደለም” ብሎ አስተማረን ፡፡ (ማቴ.12፡7፤ሆሴ.6፡6)

Saturday, March 10, 2012

ለቤተክርስቲያን መሪዎች የቅዱስ ኤፍሬም መልእክት






ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
02/07/2004
ቅዱስ ኤፍሬም በዚህ ጽሑፉ ላይ ቤተ-ክርስቲያን የሚለው እኛን ክርስቲያኖችን ነው፡፡ በእኛ ግንባር ላይ ስንጠመቅ የሥላሴ ስም ተጽፎአል ስለዚህም የክርስቶስ ቤተሰዎች ተሰኝተናል፡፡ በዚህ ስም ላይ ሌላ ስም መለጠፍ ወይም መጨመር ወይም መቀነስ ፈጽሞ የሚገባ ተግባር አይደለም፡፡ እንዲህ ማለት በክርስቶስ የተፈጸመልንን የማዳን ሥራ ዋጋ ማሳጣት ይሆናል፡፡ ምናልባት በቅዱስ ኤፍሬም ዘመን ቤተ ክርስቲያንን በራስ ስም መጥራት ወይም ሌላ ተጨማሪ ስም መስጠት ወይም መቀነስ ታይቶ ይሆናል፡፡ በዚህም ዘመን በራሳቸው ስም ቤተ ክርስቲያንን ከፍተው  እንደግል ንብረታቸው ቆጥረው የሚኖሩ እንዳሉ ከወደ አሜሪካ ይሰማል፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም ለጭብጡ መነሻ ነጥብ የሚያደርገው ቅዱስ ጳውሎስ “እያንዳንዳቹ ፡- እኔ የጳውሎስ ነኝ እኔስ የአጵሎስ ነኝ እኔ ግን የኬፋ ነኝ እኔስ የክርስቶስ ነኝ ትላላችሁ፡፡ ክርስቶስ ተከፍሎአልን ጳውሎስስ ስለእናንተ ተሰቀለን ወይስ በጳውሎስ ስም ተጠመቃችሁን” (1ቆሮ.1፡12)ብሎ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖችን የጻፈውን መልእክት መሠረት አድርጎ ሳይሆን አይቀርም፡፡
አንተ በመንጎቹ ላይ የተሾምህ ካህን ሆይ ለጌታህ ሙሽራ የሆነችው ቤተክርስቲያን እነሆ!! እርሱዋን ከክፉ ሁሉ ጠብቃት፤ እርሱዋን በማባበል የራሳቸውን ስም ለመለጠፍ  ከሚተጉትም ተኩሎች ጠብቃት፡፡ የእርሱዋ የሆነው የሙሽራው ስም በላይዋ ላይ ታትሞአልና ሌላ ስም ለእርሱዋ በመስጠት ከሌሎች ጋር ታመነዝር ዘንድ አትፍቀድ፡፡ እርሱዋ የታተመችበት ስም በሩቁ ብእሲ ስም አይደለምና በግንባሯ ላይ የታተመውን ስም በመጥራት በአብ በወልድ በመንፈስ ቅድስ ማመኑዋን በይፋ ትገልጥ ዘንድ አስተምራት፡፡ በሥላሴ ስም ትጠራ ዘንድ ያበቃሃት ጌታችን ሆይ! ስምህ ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ የተመሰገነ ይሁን!!!

“ጌታችን መዝጊያህን ዘግተህ…ጸልይ” የማለቱ ትርጉሙ(በአፍርሃት ሶርያዊ)


                 
ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
01/07/2004
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸሎታችን ምን መምሰል እንዳለበት ሲያስተምር “አንተ ግን ስትጸልይ ወደ እልፍኝህ ግባ መዝጊያህንም ዘግተህ በስውር ላለው አባትህ ጸልይ በስውር የሚያይህም አባትህ በግልጽ ይከፍልሃል፡፡”(ማቴ፡፮፥፮)ብሎ አስተምሮአል፡፡ ወዳጄ ሆይ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምንጸልይበት ጊዜ “ወደ እልፈኝህ ግባ መዝጊያህንም ዘግተህ በስውር ላላው አባትህ ጸልይ” ማለቱ የመኖሪያ ቤትህን ደጅ ዘግተህ ጸልይ ማለቱ ነውን ? እንዲህ ነው ብለህስ ስለምን ትረዳለህ ? ጌታችን እንዲህ ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ እስከቻልኩት ድረስ ላብራራልህ እሞክራለሁ፡፡
እርሱ “አንተ ግን ስትጸልይ ወደ እልፍኝህ ግባ መዝጊያህንም ዘግተህ ጸልይ” ሲልህ የልብህን ደጅ በመዝጋት እንድትጸልይ ሲመክርህ አይደለምን ? እኛ ልንዘጋው የሚገባን ጌታ ያዘዘን  በር የቱ ነው ? ቤቱ ሰውነታችን ፣ በሩ ልባችን ካልሆነ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል ? ሐዋርያው እንዳለው ሰውነታችን ክርስቶስ የሚኖርበት ቤተመቅደሱ ነው፡፡ እርሱ“ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት በእናንተ የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተመቅደስ እንደሆነ አታውቁምን?” አላለንምን?(፩ቆሮ.፮፥፲፱፣፳) ወደ ውስጥ ሰውነትህ ወይም ወደ ገዛ ቤቱ ገብቶ ያደር ዘንድ አፍህ ለጸሎት ሳይከፈት አስቀድመህ ማረፊያ ቤቱን ማጽዳት ማስተካከል ይገባሃል ፡፡ መልእክቱ ይህ ካልሆነ በቀር ኃይለ ቃሉ ምን የተለየ ሌላ ትርጉም አለው ? ወይስ አንተ ቤትና በር በሌለበት በምድረበዳ ብትሆን እንዲህ ስለሆነ ለሰማይ አባትህ በስውር መጸለይ አይቻልህም ማለት ነውን ? ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰማይ አባታችን የልባችንን መሻትና አሳብ እንደሚያውቅ “አባታችሁ የሚያስፈልጋችሁን ያውቃልና”(ማቴ፡፮፥፰ )ብሎ አስተምሮናል፡፡


Thursday, March 8, 2012

በእኛ ተፈጥሮ ውስጥ ያለው ሦስትነትና ዕፀ በለሷ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
30/06/2004
የሰው ልጅ ከሦስት አካላት ጋር ኅብረት ያለው ፍጥረት ነው፡፡ አንደኛው ከምድር ፍጥረታት ጋር ሲሆን እርሱ ገዢያቸው ነውና በገዢና በተገዢ መካከል እንዳለ ዓይነት ኅበረት ከእነርሱ ጋር ይኖራል፡፡ ሌላኛው ከመላእክት ጋር ነው፤ መንፈሳዊት ረቂቅ አካል ስላለችው ከመላእክት ጋርም ኅበረት አለው፡፡ ሦስተኛውና ዋነኛው የሁለቱ ውሕደት ውጤት የሆነው የእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ አለውና ከእግዚአብሔር አምላኩ ጋር ኅብረት አለው፡፡

 ሰው ከእነዚህ ከሦስት አካላት መካከል ከአንዱ ጋር ኅብረቱ ከተቋረጠ ሕይወቱ ጣዕም ታጣለች፡፡ እነዚህ ኅብረቶች የሰው ልጆችን ሙሉ የሚያደረጓቸው ኅብረቶች ናቸው፡፡  ነገር ግን እነዚህ ሁሉ በሰውነታችን ውስጥ አሉ፡፡ ፍጥረታዊውን ዓለም የምትወክል ከምድር አፈር የተበጀት ሰውነት አለች፡፡ ሰማያውያን መላእክትን የምትወከል ረቂቅ ነፍስ አለችን፡፡ረቂቃንንና ግዙፋንን በአንድነት የሚገዛ ስለመሆኑ ምስክር የምትሆን የእግዚአብሔር የገዢነቱ ምልክት የምትሆን "እኔ" የምንላት ማንነት አለችን፡፡  በሥጋ ተፈጥሮአችን ምድራውያን ፍጥረታትን ብንመስልም እነርሱን ሙሉ ለሙሉ መስለን መኖር አንችልም፡፡ በነፍስ ተፈጥሮአችን መላእክትን ብንመስለም ሙሉ ለሙሉ በእነርሱ ሥርዐት ልንኖር አይቻለንም፡፡ እኛ ከሁለቱ በተውጣጣ ሥርዐት እንኖራለን፡፡ ስለዚህም ሰው አኗኗሩን ከእግዚአብሔር ጋር ማድረግ ካሻ እነዚህን ሁለቱን ፍጥረታት በተፈጥሮው በኩል ማወቅና መረዳት ይገባዋል፡፡

Wednesday, March 7, 2012

በዓለ እግዚእ በቅዱስ ኤፍሬም




ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
29/06/2004 
ይህቺ ቀን ለቅዱሳን ነቢያት ነገሥታትና ካህናት የደስታቸው ቀን ናት፡፡ በዚህች ቀን በይሁዳ አውራጃ በቤተልሔም እንደ ተስፋ ቃሉ የሰው ልጆችን ከኃጢአት ሊያድናቸው ከቅድስት ንጽሕት ድንግል ማርያም አማኑኤል ተወለደ፡፡ እነሆ ድንግል አስቀድሞ በነቢዩ ኢሳይያስ “እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች”(ኢሳ.7፡14)ብሎ የተነገረው የትንቢት ቃል እውን ሆነ፡፡ አሕዛብን ወደ እርሱ የሚያቀርባቸው በዚች ቀን ተወለደ፡፡ ነቢዩ ዳዊት ስለእርሱ የተናገረው ትንቢት ዛሬ ተፈጸመ፡፡(መዝ.130፡1-7) ሚክያስ የተናገረው የትንቢት ቃልም እንዲሁ፡፡(ሚክ.5፡2) ጌታችን በኤፍራታ እረኛ የሆነው ክርስቶስ ተወለደ፡፡(ማቴ.2፡1-2) በበትሩም(በመስቀሉም) በእርሱ የታመኑትን ይጠብቃቸዋል፡፡ ከያዕቆብ ኮከብ ወጣ ከእስራኤልም ራስ የሆነው ተነሣ፡፡ በልዓም አስቀድሞ “አያለሁ አሁን ግን አይደለም እመለከታለሁ በቅርብ ግን አይደለም ከያዕቆብ ኮከብ ይወጣል ከእስራኤልም በትር ይነሣል”ብሎ የተናገረው የትንቢት ቃል በዛሬዋ ቀን ተፈጸመ፡፡(ዘኁል.24፡17) በሕቡዕ የነበረው ብርሃን በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ መገለጥ ታየ፡፡ በነቢዩ ዘካርያስ የተነገረው ብርሃን ዛሬ በቤተልሔም አበራ!(ዘካ.4፡1-3)

ጌታችን ሆይ!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
28/06/2004
ጌታችን ሆይ! ዛሬ ወደ ኋላ ተመልሼ የአዳምና የሔዋን ቅድስናና ንጽሕና ምን ይመስል እንደነበረ ለማስተዋል ሞከርኩ፡፡ ጌታ ሆይ! የኃጢአታችንን ታላቅነት እኛ በአንተ ላይ ባደረስነው መከራ ስንመለከተው፣ የጥንት ቅድስናችንንና ንጽሕናችንን በአንተ ሰው መሆን ውስጥ ተመለከትነው፡፡ አዎ ጌታችን ሆይ! በአንተ የቀደመው የቅድስና ሕይወታችን ምን ያህል ማራኪ እንደነበረ አስተዋልነው፡፡ አንተ በልብህ ትሑትና የዋህ እንደሆንክ ነገር ግን የዋህነትህ ከእውቀት ጉድለት እንዳልሆነ እንዲሁ ከውድቀት በፊት የአዳም አባታችንና የሔዋን እናታችን ትሕትናና የዋህነት በእውቀት የተሞላ ነበር፡፡
አንተ ፍጥረትህን ነፍስህን እስከ መስጠት ደርሰህ እንድትወድ እንዲሁ አዳምና ሔዋንም ራሳቸውን እስከመስጠት ድረስ ደርሰው አንተንና ከሥራቸው ያስገዛህላቸውን ፍጥረታት ይወዱ እንደ ነበር አሳየኸን፡፡ ጌታ ሆይ! አዳምና ሔዋን እርስ እርሳቸውም ያላቸው ፍቅር በአንተና በአባትህ መካከል እንዳለው ዓይነት ፍቅር ይመስል ነበር፡፡ ቅድስናቸውም አንተ “የሰማዩ አባቴ ቅዱስ እንደሆነ እናንተም ቅዱሳን ሁኑ” ብለህ እንዳስተማረከን ዓይነት ሥላሴን አብነት ያደረገ ቅድስና ነበር፡፡ ይህ እንደ ሕፃን ቅዱስና ንጹሕ የሆነ የአዳምና የሔዋን ተፈጥሮ በአንተ ዘንድ እጅግ ተፈቃሪ ነበር፡፡ ስለዚህም አባታችን ያዕቆብ ከልጆቹ ይልቅ የክርስቶስ ኢየሱስ አርአያ ያለውን ዮሴፍን እንዲወደው፣ አንተም ጌታ ሆይ! እኛን የሰው ልጆችን ከሌሎች ፍጥረታት ሁሉ ይልቅ የአንተ አርአያ ይታይብናልና ትወደን ነበር፡፡

Monday, March 5, 2012

ተወዳጆች ሆይ እናንተ……ናችሁ!!(በአፍርሃት ሶርያዊ)


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
26/06/2004
"ተወዳጆችና የሰላም ልጆች እንዲሁም የክርስቶስ ደቀመዛሙርት ሆይ! እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፤ እናንተ የምድር ጨውና የሰውነት(የዓለም) ዓይኖች ናችሁ፡፡ እናንተ የሙሽራውና የመልካሙ ዘር እንዲሁም የሕይወት ውኃ ለሚፈልቅበትና የማዕዘን ራስ ለሆነው ሕያው ዓለት ክርስቶስ ሚዜዎች ናችሁ፤ እናንተ አጥልቃችሁ በመቆፈር ቤታችሁን በዓለት ላይ የምትሠሩ ብልህ አናጺዎች ናቸሁ፡፡
እናንተ የብዙ ብዙ የሆነ እህልን በጎተራችሁ የምታከማቹ ታታሪ የጽድቅ ገበሬዎች ናችሁ፡፡ እናንተ የተሰጣችሁን ጥሪት ብዙ እጥፍ አትርፋችሁ የተገኛችሁ ትጉሃን ነጋዴዎች ናቸሁ፡፡ እናንተ ዋጋችሁን ተቀብላችው ሌላ ይጨመርላችሁ ዘንድ ያልጠየቃችሁ ቅን ሠራተኞች ናችሁ፡፡


Saturday, March 3, 2012

ሴቶች ሊያውቁዋት የምትገባ እውነት!!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
24/06/2004
ዛሬ ባነሣሁት ጭብጥ ላይ:- ደግሞ ምን አመጣህ? ትሉኝ ይሆናል፤ ነገር ግን ይህ ፍጥጥ ያለ እውነትና እውቀት ነው፡፡ ይህቺ እውነት እናቶቻችን፡- "ድሮ አግኝተናት ቢሆን ኖሮ ዛሬ ይህች ዓለም የአውሬዎች መፈንጫ ባልሆነች ነበር" ብለው የሚቆጩባት እውነት ናት፡፡ ይህቺ እውቀትና እውነት ፡-  ዓለምን ሴቶች ይገዙአትና ይመሩዋት ዘንድ ተፈጠረች የምትል ናት፡፡ መቼም ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል? ብላችሁ በመገረም ትጠይቁኝ ይሆናል፡፡ እውነቱና ሐቁ ግን ይህ ነው፡፡
እግዚአብሔር አምላክ ሴት ልጅ ገነትን እንደራሱዋ ሃሳብና ጥቅም ትመራትና ትጠቀምባት ዘንድ በዚህም እርፍ ብላ ትኖርባት ዘንድ አዳምን ጨምሮ ሁሉን አደላድሎ ከፈጠረ በኋላ የፍጥረት ሁሉ ዘውድ አድርጎ ከአዳም አስገኛት፡፡ አዳም አስቀድሞ በሥጋ መገለጡ ለእርሱዋ በእግዚአብሔር ፈንታ ሆኖ ገነትን እንዴት መምራትና ማስተዳደር እንደምትችል ያስተምራት ዘንድ ነበር፡፡ በእርግጥም አዳም ይህን ፈጽሞላታል፡፡ ስለዚህም ነው ሰይጣን እርሱዋን በተንኮል “በእውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን? ብሎ በጠየቃት ጊዜ “በገነት ካለው ዛፍ ፍሬ እንበላለን ነገር ግን በገነት መካከል ካለው ከዛፉ ፍሬ እግዚአብሔር አለ፡-እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ አትንኩትም”ብላ መመለሱዋ፡፡(ዘፍ.3፡2-3)

Thursday, March 1, 2012

ገነት በቅዱስ ኤፍሬም


ትርጉም ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
22/06/2004
በዚህ መዝሙር ቅዱስ ኤፍሬም እስራኤላውያንን በምድረ በዳ ይከተላቸው የነበረውን ዓለት በማንሣት እግዚአብሔር ፍጥረታትን እንዴት እንደፈጠራቸውና ስለገነት ያለውን አስተምህሮ እንመለከታለን፡፡

እስራኤላውያንን በምድረ በዳ ይከተላቸው የነበረውን አለትን አስታውሼ ዓለማትን የፈጠረውን የእግዚአብሔርን ቃል ልብ አልኩ፡፡ እንደ ታላቅ ወንዝ ለእነርሱ ከአለቱ ውስጥ የፈለቀው ውኃ በውስጡ ካለው የውኃ ቋት የተገኘ አልነበረም ፡፡ በአለቱ ውስጥ አንድም ጠብታ ውኃ የለም፤ ነገር ግን ልክ የእግዚአብሔር ቃል ፍጥረትን ከምንም እንዳስገኛቸው፤እንዲሁ ታላቅ የውኃ ጅረት ከደረቅ ድንጋይ ውስጥ ፈልቆ የተጠሙትን አረካቸው፡፡
ሙሴ በመጽሐፉ ስለ ሥነ ተፈጥሮ ገልጦ ጽፎልናል  ስለዚህም ተፈጥሮና መጽሐፍ ቅዱስ ስለፈጣሪ ምስክሮች ሆኑ፡፡ የሰው ልጅ ተፈጥሮን ለራሱ ጥቅም ሲገለገልባት እንደሚያውቃት እንዲሁ መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብ በውስጡ የያዘውን መረዳት ይቻለናል እነዚህን ሁለቱን ምስክሮች በሁሉ ስፍራ እናገኛቸዋለን፡፡