Saturday, March 17, 2012

"ከእባብም ክርስትናን እንማር፤ እንዴት?"

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
09/07/2004
ከአንድ የቅርብ ቅርብ ወዳጄ አንድ ታላቅ የሆነ ትምህርት ሰማሁ፡፡ ይህ ወዳጄ ነገር መሸፋፈን አይወድምና እንዲህ አለኝ “አንተዬ አንድ የአደባባይ ምስጢር ልንገርህ" ብሎ ይጀምርና በመቀጠል “ካበቁ ከበቃቁ ሰውነታቸውና አእምሮአቸው በኃጢአት ከድሃ ድሪቶ ይልቅ እጅግ ካደፈ በኋላ እንዲሁም ዓለሚቱን በኃጢአታቸው ከከደኗትና  ትውልዱን መንገድ አስተው የአጋንንት መጫወቻ ካደረጉ በኋላ ዓለም በቃኝ አሉ አሉ! እነ እማሆይ! እነ አባሆይ! ዋይ! ... ዋይ! .... ዋይ! ... እኒህ ጽድቅ በቆቤዎች ስለእኛ በመስቀል ላይ ስለተሠዋልን ስለአፍቃሪያችን ስለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንዳች ሳያስተምሩን እኛን ለሰይጣን  ዳርገውን ዓለም(ኃጢአት) በቃችኝ ብለው ቆብ አጠለቁ አሉ! ጉድ ነው! መቼም በኢትዮጵያችን ይህ የተለመደ የጽድቅ ማቋረጫ መንገድ ሆኗል ፤እድሜ ለምንኩስና!! መቼም ሰው ቆቡን ከየትም ያምጣው ከየት እርሱን አጥልቆ በአንዴው ጻድቅ ሆኖ ቁብ ይልብናል፡፡ እኽ ነው እንጂ ሌላ ምን ይባላል!! ግን ግን ልጆቻቸውን በሥርዐት ቀርጸው የሚያሳድጉና ለዓለም ብርሃን እንዲሆኑ የሚያበቁ እንዲሁም ክርስቶስ በእርሱዋ የሰው ልጅ መባልን ያላፈረባታን ቅድስት ድንግል ማርያምን በምግባራቸው የመሰሉ አንዳንድ ቅዱሳን ወላጆችም አይጠፉም፡፡