Monday, February 27, 2012

ዕንቁ፣ ክርስቶስና ኢትዮጵያ በቅዱስ ኤፍሬም




ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
20/06/2004
መግቢያ
ለቅዱስ ኤፍሬም አንድ ወቅት ደቀመዛሙርቱ ዕንቁ ያመጡለታል፡፡ እርሱም ዕንቁውን በተመለከተ ጊዜ ሰማያዊ ምስጢር ተገለጠለት፡፡ ስለዚህም በዕንቁ ነገረ ሥጋዌውንና በጥምቀት ያገኘነውን ክብር ሰበከ፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም ዕንቁን መሠረት አድርጎ ሰባት መዝሙራትን የደረሰ ሲሆን ከእነዚህ ድርሰቶቹ ውስጥ ለአሁኑ ስለኢትዮጵያና ስለንግሥት ሳባ እንዲሁም ስለኢትዮጵያዊው ጃንደረባ የሚያወሳውን ሦስተኛውን መዝሙር ወደ አማርኛ መልሼዋለሁ፡፡

አንተ ዕንቁ ሆይ! ሰውነትህ ከልብስ የተራቆተ ነውና ራስህን መሰወር እንዴት ይቻልሃል? ነጋዴዎች አንተን ከማፍቀራቸው የተነሣ ከልብስ ተራቆቱ፤ ነገር ግን እነርሱ ከልብስ መራቆታቸው የአንተን ራቁትነት በልብሳቸው ለመክደን ሲሉ አልነበረም፡፡ አንተ ምንም እንኳ ከልብስ የተራቆትክ ብትሆን ከውስጥህ ሚፈልቀው ብርሃን ልብስህ ነው፤ መጎናጸፊያህም የብርሃኑ ነጸብራቅ ነው፡፡ ኦ አንተ ዕንቁ ሆይ! ግሩም የሆነው ባሕርይ እንዴት ድንቅ ነው!!
ከስህተት በፊት ሔዋን በገነት ሳለች ምንም እንኳ ከልበስ የተራቆተች ብትሆንም ልክ እንዳንተው ብርሃንን የተጎናጸፈች ውብ ነበረች፡፡ ከዚህ ልብሱዋ ያራቆትካት አንተ ሰይጣን ሆይ ርጉም ሁን፡፡ ጌታ ሆይ! ዕንቁው ያንተ ምሳሌ ነው ፤ አንተን ግን ይህ ሰይጣን ከዚህ ልብስህ ሊያራቁጥህ አይቻለውም፡፡ አሁን በገነት ሴቶች እንደዚህ ዕንቁ ብርሃንን ተጎናጽፈው የቀድሞዋን ሔዋንን መስለዋታል፡፡




በቅዱሱ መጽሐፍ እንደሰፈረው እጅግ ውዱና አንጸባራቂው ዕንቁ የጥቁሮች ምድር ለሆነችው ለኢትዮጵያ የተሰጠው ዕንቁ ነው፡፡ ለአሕዛብ ብርሃንን የሰጠ አማናዊው  ዕንቁ ክርስቶስ ለኢትዮጵያና ለሕንድም ብርሃኑን ሰጠ፡፡ 
ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ከሰረገላው ሆኖ ፊልጶስን ተመለከተው፡፡ የብርሃኑ መቅረዝ የሆነው ፊልጶስ ወደ ጋዛ በሚወስደው ጎዳና ኢትዮጵያዊውን ጃንደረባ የኢሳይያስን መጽሐፍ እያነበበ በወንዝ ዳርጃ ተገናኘው፡፡ ስለክርስቶስም ሰብኮት ከወንዙ ውኃ አጠመቀው፤ ይህም ጃንደረባ በደስታ በርቶ በሐሴት ወደ ሀገሩ ተመለሰ፡፡ እርሱም ሀገሩ ሲገባ በትምህርቱ ደቀ መዛሙርትን አፈራ ጥቁር የሆነውን ሕዝብ በትምህርቱ ብርሃን ብሩሃን አደረጋቸው፡፡ ጥቁሮቹ የኢትዮጵያ ሴት ልጆች ለእግዚአብሔር ወልድ  ራሳቸውን የሚያበሩ ዕንቁዎች አድርገው ቀደሱ፡፡ እርሱም እነዚህን ኢትዮጵያውን ደናግላንን ልክ እንደተወለወለና እንደሚያንጸባቅ ዘውድ አስጊጦና አስውቦ በእግዚአብሔር አባቱ ፊት መባዕ አድርጎ አቀረባቸው፡፡
አስቀድማ ወደ ንጉሥ ሰሎሞን የመጣችው ንግሥት ሳባ ወደ ተኩሎች የመጣች በግን ትመስላለች፡፡ እርሱዋም ከእርሱ ተጋብታ እውነተኛውን የብርሃን መቅረዝ ከእርሱ ተቀበለች፡፡ ብርኑንም እያበራች ወደ ሀገሩዋ ተመለሰች፡፡ ነገር ግን አይሁድ እንደ ግብራቸው ጨለማ ወርሶአቸው ቀሩ፡፡ 
ቅድስት ሳባ ወደ ቤቱዋ በተመለሰች ጊዜ ይዛው የመጣችው የመቅረዙ ብርሃን እውነተኛው የአጥቢያ ኮከብ እስኪወጣ ድረስ በጨለማ ለነበረው ሕዝብ ብርሃንን ሲሰጥ ቆየ፡፡ በንግሥት ሳባ ወደ ኢትዮጵያ የገባው የመቅረዙ ፋና ከእውነተኛው የአጥቢያ ኮከብ ብርሃን በጋዛ ጎዳና ከኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ጋር ሲገናኝ ሀገሪቱን በብርሃኑ ከደናት፡፡
አንተ ዕንቁ ሆይ! በባሕር ውስጥ ልዩ ልዩ መጠን ያላቸው ግዙፋን ዓሣት ቢኖሩም፤ የእነርሱ ጠቅላላ ግዝፈት ከባሕሩ ግዝፈት ጋር ሲነጻጸር እንደ ኢምንት ናቸው፤ ነገር ግን አንተ ! ታናሽ ሆኖ በሰው አርአያ በመገኘት አዳምን እንዳከበረው ክርስቶስ  ምንም ታናሽ ብትሆንም ባሕር በአንተ ምክንያት ከበረች፡፡
አንተ ለራስ ዘውድነት የተመረጥኽ ነህ፡፡ ዐይኖች ሁሉ ውበትህን ያደንቃሉ፤ ጆሮዎችም ያንተን መልካምነት ያውጃሉ፡፡  ሰው ሁሉ አንተን እንደሚያፈቅሩህ ምሳሌው ነህና የእርሱን ሕያው የሆነ ቃሉን ሰምተው ያፈቅሩት ዘንድ ና ወደ ጎረቤትህ ወደ ምድር ውጣ፤ በእርሱም ላይ እየተዘዋወርክ ድምፅህን አሰማ፡፡
ጆሮ በውስጡ በሚሰማው ቃል ይጌጣል በውጪ ደግሞ በአንተ ያጌጣል፡፡ ጌታ ሆይ በዕንቁ ያጌጠው ይህን ጆሮ ጥበብን ከአጌጠበት ዕንቁ ሰምቶ ውስጡን አንተን በመስማት ያስጌጠው ዘንድ የዕንቁውን ምስጢር ግለጥለት፤ እኛንም በእውነተኛው ቃልህ አስጊጠን፡፡
አንተ ዕንቁ ሆይ! ለጆሮአችን መስታወቱ ሁነው፤ በአንተ ውበት የእግዚአብሔር ቃልን ውበት ጆሮአችን ይስማ፡፡ በአንተ መስታወትነት ማደሪያው በአርያም የሆነውን የእግዚአብሔር ቃልን ልዕልና እንረዳ፡፡ ጌታችን ሆይ! ለቃልህ ሥጋችን ዛፉ ነው፡፡ በቅርንጫፎቹ ያፈራው ፍሬ ከውስጡ ብርሃንን የሚያፈልቅ ዕንቁን ይመስላል፡፡ በዕንቁ የተመሰልከው ፍሬአችን አንተ ነህ፤ ከአንተም ብርሃን መንጭቶ ለሁሉ ያበራል፡፡  
የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ሆነህ የተጠቀስክ አንተ ዕንቁ ሆይ! እርሱ ጌታችን እንደመሰከረው እነዚያ አምስቱ ትጉሃን ደናግላን አንተን መቅረዝ አድርገውሃልና ብርሃንን ለበሱ፡፡ የእነኝህ ጎበዛዝት ደናግላን ሰውነት በብርሃኑ እንደደመቀ መቅረዝ ነው፡፡ 
ጌታ ሆይ! ለብሰውት በብርሃኑ ደምቀው ይታዩበት ዘንድ ለድሆቹ ደናግላን ዕንቁውን የሚሰጣቸው ማን ነው? እናንት ደናግላን ሆይ ዕንቁውን አግኝታችሁ ከድህነታችሁ ትወጡ ዘንድ ያለ ዋጋ በክርስቶስ እመኑ፡፡ ይህም እምነት በሁሉ ዘንድ የተገለጠ እምነት ነው፡፡ በዕንቁ የተመሰለው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ይህን በእምነት አግኝታ የተጌጠችበት ድንግል ከእንግዲህ ታጌጥበት ዘንድ ወርቅ አያስፈልጋትም፤ ነገር ግን እንደው በከንቱ ይህን ዕንቁ አውልቀሽ ብትጥይው ታላቅ ጥፋት ይመጣብሻል፡፡
ዕንቁ በሆነ ጊዜአችን ዘለዓለማዊ የሆነውን ይህን ዕንቁ ገንዘባችን እናድርግ፡፡ ምድራዊው ዕንቁ በእጅ ቦርሳ ወይም በሳጥን ወይም በግምጃ ቤት ውስጥ ሊገኝ ይችላል፡፡ ሰማያዊውን ዕንቁ ለማግኘት ግን አስቸጋሪ ነው፡፡ በሰማያት ወደ አለው የዕንቁ ማስቀመጫ ግምጃቤት ቢገቡ እንኳ ሌሎች የተቆለፉና የራሳቸው የሆነ መክፈቻ ቁልፍ የሚያስፈልጋቸው በሮች በድጋሚ ያጋጥሟቸዋል፡፡ ስለዚህም ወደ ውስጥ ዘልቆ በመግባት ዕንቁውን ማግኘት አይቻልም፡፡ ነገር ግን እኛ በእምነት ያገኘነው ይህ ዕንቁ እጅግ የከበረው ዕንቁ ነውና በሰማያት ከተከማቹት ዕንቁዎች ሁሉ በላይ እጅግ የከበረ ነው፡፡ በእርሱም የተዘጉትን የሰማያት ደጆች ሁሉ አልፈን ከእግዚአብሔር አብ ዘንድ እንደርሳለን፡፡  
ዕንቁው ክርስቶስ ነው፤ ዕንቁው ሥጋው ወደሙ ነው፤ ዕንቁው በጥምቀት የለበስነው የጸጋው ልብሳችን ነው፤ ዕንቁው ለክርስቶስ ኢየሱስ የታጨንበት በጥምቀት ያገኘነው ድንግልናችን ነው፡፡ ዕንቁው በእርሱ የተሰበከችልን ወንጌል ናት፤ ዕንቁው በእርሱ ያገኘነው እምነታችን ናት፤ ዕንቁው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ከልብስ ተራቁተው እርሱን ለማግኘት ወደ ውኃ ውስጥ የጠለቁት ነጋዴዎች እኛ ነን፡፡ እኛም እርሱን በጥምቀት በመልበስ ወደ ቀድመው ክብራችን ተመለስን፡፡ እርሱን ለብሰናልና ለዘለዓለም አንገፈፈም፡፡ ምስጋና ይሁን ለወደደን ወደ ቀደመው ክብራችንም በጥምቀት ለመለሰን ለአብ ፣ ለወልድ፣ ለመንፈስ ቅዱስ ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን !!!  

2 comments:

  1. kale hiyiweti yasemalin wenidimachin tsegawin yabizali

    ReplyDelete
  2. dere getsun lmen beleloch dehre gets lay aastawawkewum malete abthe haghaw hezeb yemiwkachew dehre getsoch mkidusan dejeselam daniel vies adebabay..lay be tastewawkew lebthwoch erft tehonalech enem yagehoat beagatami sekorekur new

    ReplyDelete