Tuesday, January 24, 2017

ጸሎት በእንተ ትዳር

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
16/05/2009

ጌታ ሆይ ከእናቴ ሆድ ግሩምና ድንቅ አድርገህ ፈጠርኸኝ፡፡ ይህ ተፈጥሮዬም ግሩምና ድንቅ መባሉ በውስጥም በውጪም አንተን እንዲመስል ሆኖ መፈጠሩ ነው፡፡ ወንድና ሴት አድርገህ እንደፈጠርኽን ተናግረህ ካበቃ በኋላ አስቀድመህ የፈጠርኸው  ግን አዳምን ነበር፡፡ በእርሱ ውስጥ ሔዋን እንዳለች ግን አልተረዳንም ፡፡ ጌታ ሆይ ሥራህ ረቂቅ ነው፡፡ አንተ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር በማለት እግዚአብሔር ሰውን በመልኩና በምሳሌው ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠረው” ብለህ አስቀድመህ ሙሴን አጻፍኸው እንዲያም ሆኖ ግን “ ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም” ብለህ በውስጡ የነበረችውን ሴትን በእርሱ ላይ ከባድ እንቅልፍን በማምጣት ፈጥረህ አሳየኸው፡፡ እርሱም ይህቺ ሴት ከአጥንቴ አጥንት ከሥጋዬም ሥጋ ናት ስለዚህ ሴት ትባል አለ፡፡ አንተም ሰው እናትና አባቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይጣበቃል፡፡ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ” አልህ፡፡ ስለዚህ በልዩነት ውስጥ ወደ አለ አንድነት አመጣኻቸው፡፡ በፊት ግን እንዲህ አልነበሩም፡፡  ፍጹም በማይለይ አንድነት ከአብራካችን እንደሚገኝ ልጅ አንድ አካል ነበሩ፡፡ ጌታ ሆይ ነገር ግን ለአንተ ይህ በአንድ አካል አንድ ሆኖ መኖር የተመረጠ አልነበረምና በአንተና በቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ሁለት አድርገህ ግን ደግሞ አንድ ሆነው እንዲኖረ ከአዳም ሔዋንን አስገኘሃት፡፡ እነዚህ ሁለት ሲሆኑ አንድ አንድ ሲሆኑ ሁለት ነበሩ፡፡ በአንድ ጥንድ ብዙ ጥንዶችን በመፍጠርም ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሉዋት ብለህ ሥራህን ፈጸምህ፡፡ በዚህ መሐል ግን አንተን በድለን ፈቃድህን ተላለፈን ስለተገኘን ሁለት ሆኖ አንድ ሆኖ መኖር ለእኛ ፈታኝ ሆነብን፡፡ ስለዚህም  “የባልና የሚስት ሥርዐት እንዲህ ከሆነ አይጠቅምም” ላሉ ሐዋርያት ይህም ሕይወት ለተሰጣቸው ነው ብለህ መለስህላቸው፡፡ እንዲህ ማለትህ ሲሰጥ እንጂ ሳይሰጥ ይህም ጃንደረብነት ከትዳርም ይከፋል ልትለን እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡ ምክንያቱም ሳይሰጥ ጃንደረባ መሆን አለሌ ወደ መሆን ያደርሳልና፡፡ ጌታ ሆይ እለምንሃለሁ እባክህ የሰጠኸንን ሕይወት አጣፍጥልን ትርጉሙም ገብቶኝ የምኖርበት እንዲሆን ፈቃድህ ይሁን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡ 

ጸሎት በእንተ ሰንበት


ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
16/05/2009


ኦ የዘለዓለም አምላክ ጌታችን ሆይ!!  የሰንበት ጌታዋ የሆንኽ፣  ሰንበታችንም የሆንኽ እባክህ እኛም የሚቀዋወመንን የሥጋ ፈቃድ ጸጥ አድርገን ልባችንን የቃልህ ጽላት፣ ሰውነታችንን ማደሪያ ቤተ መቅደስህ አድርገን፤ አንተ ግዛታችን ሆነህ እኛም በእውነት ርስትህ ሆነን እኛም ሰንበት እንባል፤ አንተም በሚታይና በተገለጠ ጌታችን ሁነን ያኔ እናርፋለን እረፍታችንም የማይወሰድ ይሆንልናል፡፡ እኛ ፈቃድህን ፈጻሚዎች አንተም በእኛ የምትገለጥ ሁንልን፡፡ ስለምን እሾህና አሜካላ ታብቅልብህ ተብላ በተረገመች ምድራዊ ሥርዓት ውስጥ ወላጅ እንደሌለው ሰው ሆነን ተጥለን እንቅበዘበዛለን፡፡ ጌታ ሆይ እኛን የአንተ ከማድረግህ በፊት በአንተ ከእናታችን መኅፀን ፈጠርኸን፤ ቅዱስ ጳውሎስ እኔ እተክላለሁ አጵሎስ ያጠጣል እግዚአብሔር ግን ያሳድጋል እንዲል ሁሌም ቢሆን አንተ ከሕዋሳታችን ጋር ነበርህ በአንተ ፈቃድ አደገን እንጂ ራሳችንን ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣን አይደለንም፡፡ ምርጫ ሰጠኸን ምርጫችን በወላጆቻችን እጅ በነበረበት ጊዜ እነርሱ ለአንተ ቀደሱን ልጆችህም አደረጉን፡፡ በራሳችን በቆምን ጊዜ የወላጆቻችን ምርጫ ትክክል እንደሆነ ገብቶን የወላጆቻችንን ምርጫ በምርጫችን አጸደቅነው፤ ለአንተም ሆንን፡፡  ምክንያቱም አንተ በእውነት ሰላማችን፣ እረፍታችን ሕይወታችን ነህና፡፡ ስለዚህ ጌታ ሆይ ከዚህ ዘለዓለማዊ ከሆነ ሰላም፣ እርጋታ፣ ፍቅር፣ ሕይወትና እውነት እባክህ አታውጣን በእርሱ ያመነ ወደ እረፍቱ ገብቶአል ይላልና በተግባር አንተን በመምሰል በአንተ ጥላ ሥር እንመላለሰ ዘንድ እባክህ ፍቀድ፤ ጤናችንን መልስ ልጆቻችንን ባርክ እኛንም በዓለም ከመባከን ታደገን፣ ሥራችንን ባርክ፣ ጌታ ሆይ በሁሉ የሆነብንን ታውቃለህና እርዳን ለዘለዓለም አሜን፡፡

ፊደል ይገድላል መንፈስ ግን ያደናል



ዲ/ሽመልስ መርጊያ
16/05/2009

ጸሐፍት ፈሪሳውያን መጻሕፍትን በማወቅ የዘለዓለም ሕይወት የሚገኝ ይመስላቸው ነበረ፡፡ ነገር ግን ሕይወትን የሚሰጠው ወይም ሰውን ሕያው አድርጎ ሕያው የሆነውን ቃሉን እንዲረዳ የሚረዳው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ጸሐፊው መንፈስ ቅዱስ የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስ መረዳት የሚቻለው በመንፈስ እንጂ ስላነበቡት አይደለም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን ያነበበ ሁሉ መጽሐፍ ቅዱስን አውቆአል ማለት  አይቻልም፡፡ ምክንያቱም ከአእምሮ በላይ የሆኑ፤ ነገሮች ሳይፈጸሙ አስቀድሞ የሚያውቅ እርሱ እግዚአብሔር በመንፈሱ ያጻፈው ነውና፡፡ ስለዚህ ሊረዱዋቸው የሚቻለው በመንፈስ ቅዱስ ድጋፍ ነው፡፡ ስለዚህ መጻሕፍትን ለማስረዳት የተረዳነውን ለማብራራት የመንፈስ ቅዱስ ድጋፍ ብቻኛ መንገድ ነው፡፡ ፍጥረታዊ በሆነ አእምሮ መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳት መሞከር እንደ ጸሐፍት ፈሪሳውያን መሆን ማለት ነው፡፡ ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ ይቀድማል ቅዱሳት መጻሕፍት ይከተላሉ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰው መጽሐፍ ቅዱስን ይረዳል፡፡ 
ያለ መጽሐፍ ቅዱስ ድጋፍ በእርሱ አሳሳቢነት እንደ አበው ቅዱሳን(ከአዳም -ሙሴ) ወይም እንደ ሐዋርያቱ በጽድቅ ጎዳና ሊራመድ ይችላል ነገር ግን መንፈሱ ያላደረበት አይሁዳዊ ከሆነ ግን የግድ መጽሐፍ በሚለው ብቻ ሊራመድ ይገደዳል፡፡ ቢሆንም ግን ያለመንፈስ ቅዱስ ድጋፍ ስለሆነ ማንበቡ ብቻውን ወደ መዳን አያደርሰውም፡፡ ቃል ይገድላል መንፈስ ግን ሕይወትን ይሰጣል እንዲል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰው ግን ቅዱሳት መጻሕፍትን ባነበበ ቁጥር ሁሉ በቀላሉ በመንፈስ ቅዱሰ ገላጭነት ይረዳቸዋል፡:
 በእርግጥ በመጻሕፍት ብቻ ሕይወት የሚገኝ ለሚመስላቸው ወገኖች የመንፈስ ቅዱስን ድጋፍ ስለማያውቁ መንፈስ ቅዱስን ሊሰሙት ሊረዱትንም አይችሉም፡፡ ስለዚህ ክርስቶስን ሊያውቁት ሊረዱት አልቻሉም፡፡ ብዙ ጊዜ ሰዎችን የሚያሰናክለው ያለ መንፈሰ ቅዱስ ድጋፍ በአእምሮ ጠባያቸው ብቻ ተደግፈው መጻሕፍትን እንረዳ ባሉ ጊዜ ነው፡፡ ስለዚህ ስለ ክርሰቶስ ያላቸው ግንዛቤ እጅግ የተዘበራረቀ ይሆናል፡፡ ወይም በቀጥታ ቃሉን ይዘው ሰማያዊ የሆነውን እንደ አእምሮ ጠባያቸው በመረዳት ምድራዊ ያደርጉታል፡፡  መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰው ግን በመንፈስ የተጻፈውን ይረዳል፤ በመንፈስ ቅዱስ ምሪት ሁሉን ይተነትናል ሲያብራራም ለሕሊናችን፣ ለተፈጥሮአችን የሚስማማ በመሀኑ ነፍሳችን ትፈካለች ፡፡ ስለዚህ ከመጽሐፍ ቅዱስ መንፈስ ቅዱስ ይቀድማል፡፡ ኦርቶዶክስ እንዲህ ናት ይህም ማለት ከጥንት የነበረችው እስካሁንም ያለችው ለዘለዓለም ሕያዊት ሆና የምትኖረዋ ክርስትና ማለቴ ነው፡፡

Sunday, January 22, 2017

"ሥጋን ለበሰ" ማለት ትርጉሙና ምንጩ?


ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
14/05/2009
በአበው ሊቃውንት ዘንድ የቃል ሥጋ መሆን ወይም የሥጋ አምላክ መሆን ለማስረዳት ሲሉ “ሥጋ ለበሰ” የሚለውን ቃል መጠቀም የተለመደ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ “ለበሰ” የሚለው ቃል እንደ አገባቡ የራሱ የሆነ ትርጉም አለው፡፡ ልብስ ለበሰ፣ ኤፉዱን ለበሰ፤ ኃይልን ለበሰ ወዘተ የሚሉ ዐረፍተ ነገሮችን በተለይ በኦሪቱ በስፋት ተጽፎ እናገኘዋለን፡፡ ነገር ግን ይህን በምንረዳበት መንገድ ከታች ያሉትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች መረዳት አንችልም፡፡ ለምሳሌ፡- “እግዚአብሔርም ምድርን እነሆ ተበላሸች ሥጋን የለበሰ ሁሉ በምድር ላይ መንገዱን አበላሸቶ ነበርና”(ዘፍ.6፡12) የሚል ቃል አለ፡፡ በዚህ ሥፍራ “ሥጋን የለበሰ ሁሉ” ሲል ሥጋን እንደ ልብስ የለበሰ ማለት ሳይሆን “ሰው የሆነ ሁሉ” ማለቱ እንደሆነ ለሁሉ ግልጽ ነው፡፡

Tuesday, January 17, 2017

ፕሊሮማ

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
09/05/2009
ይህ ጽንሰ ሐሳብ ሰው ሁሉ በአዳም እንደሞተ በክርስቶስ ይድናል የሚለውን ነጥብ መሠረት ያደርጋል፡፡ በእርግጥ አንዳንዶች እንደ አዲስ ግኝት ቆጥረው ቢያራግቡትም ጽንሰ ሐሳቡ እንደ ሐሳብ መነሣት የጀመረው 2ኛው /ዘመን በአርጌንስ ወይም በኦሪግን ነው፡፡ አርጌንስ ወይም ኦሪግን ፍጥረት ሁሉ ይድናል ብሎ የተነሣው  በጊዜው በፍልስፍና ውስጥ ተተብትበው የነበሩትን ለመመለስ ሲል ነበር፡፡ በእርግጥ ሰውም ይሁን ሰይጣን ለመዳን ፈቃደኛ ከሆነ እግዚአብሔር ሊያድናቸው ይችላል ቢሆንም ግን የገዛ ፈቃዳቸው ገድቦአቸው ከመዳን ርቀው ተገኝተው ነው እንጂ እግዚአብሔር እነርሱን ለማዳን ፈቃዱ ሳይኖረው ቀርቶ አይደለም።
ለምሳሌ ቅዱስ ጳውሎስ ግሪካውያንን ወደ ክርስትና ለመመለስ ሲል  “የምታመልኩትን እየተመለከትሁ ሳልፍ። ለማይታወቅ አምላክ የሚል ጽሕፈት ያለበትን መሠዊያ ደግሞ አግኝቼአለሁና። እንግዲህ ይህን ሳታውቁ የምታመልኩትን እኔ እነግራችኋለሁ።”(የሐዋ.1723) ማለቱን ልብ እንላለን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ማለቱ ግሪካውያንን ለመመለስ ሲል እንጂ በአግባቡ ሳያውቁ የሚያመለኩት ክርስቶስን ነበር እያለ እንዳልሆነ ማንም ልብ ይለዋል፡፡ ነገር ግን እነርሱን ወደ ክርስትና ለማቅረብ እንደ መግቢያ በር ግን ተጠቅሞበታል፡፡ ይህ መንፈሳዊ ጥበብ ነው፡፡ ስለዚህም ሳታውቁ የምታመልኩትን እኔ ልንገራችሁ በማለት እነርሱን ወደ ክርስቶስ አምልኮ እንዳመጣቸው እንረዳለን፡፡ እንዲሁ በአርጌንስ ጊዜ ፍልስፍና ያለ ልክ ከፍ ከፍ ያለበት ጊዜ ስለነበረና እነርሱም የክርስቲያኖች አምላክ ጭካኝ ነው፤ አምላካቸው በአእምሮ ከእርሱ የሚያንሱትን በድለው ሲገኙ ሳይራራ ወደማይጠፋ ዘለዓለማዊ እሳት ይጨምራቸዋል የሚል አስተምህሮ አላቸው ብለው ክርስትናን ከመቀበል ተመልሰው ነበረና፡፡

Sunday, January 15, 2017

አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ስለ ጥንተ አብሶ

በቀጥታ የተወሰደ
08/05/2009


መቼም የአለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት መጽሐፍን  የቃላትን ትርጉም ሽቶ የማያነብ የለም ብዬ እገምታለሁ፡፡ ነገር ግን መግቢያቸው ከመርዘሙ የተነሣ ትግሥእት ኖሮት የሚያነብ ጥቂቱ ነው ብዬ አምናለሁ ከእኔ ጨምሮ ማለት ነው፡፡ አንድ ወቅት እንዲሁ አለፍ አለፍ ብዬ የመዝገበ ቃላቱን መግቢያ ስመለከት ይህን ጽሑፍ አገኘሁት፡፡ ዛሬ ደግሞ ደግሜ አነበብሁት ይህ ጽሑፋቸው ምናልባት በጥንተ አብሶ ዙሪያ ያለውን የቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ግልጽ ሳያደርግልን አይቀርም በሚል አንባቢ እንዲያነበው ስል እነሆ ብያለሁ፡፡

በእውነት ብፅዕት


ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
7/5/2009

ያቺ ቅድስት ብላቴና ንጉሥ እልፍኙ ያደርጋት ዘንድ ሳይፈጥራት ያወቃት፥ ከማኅፀን ሳይሠራት እናቱ ትሆን ዘንድ የነፍሷን ውበት ተመልክቶ የወዳዳት፥ ቤተ መቅደሱ በመሆን የእንስሳት መሥዋዕት የሚሠዋበትን የኦሪቱን ቤተ መቅድስ ልታሳልፍ የ"ቃል" ቤተ መቅድሱ ለመሆን ተመረጠች። በመንፈስ ቅዱስ የከበረች፥ አብ ልጁን ጸንሳ ትወልድ ዘንድ የሚያጸናት ፥ ራሱን ቤተመቅደስ ላለው ቃል ቤተ መቅድሱ ለመሆን የታጨች፥ ወላጅነትን ከአብ ጋር ለመጋራት የተመረጠች፥ መንፈሷ በመንፈስ ቅዱስ በሆነ ደስታ የተሞላ፥ ነፍሷ በአምላኳና በመድኅኒቷ ሐሴት የምታደርግ ፥ በሲኦል ላሉ ነፍሳት  በምድር ላሉ ሙታን የመዳናቸው ተስፋ የነበረችና ናፍቆታቸው የሆነች በእናቷ ሃና እጅ እርጅና ወደ ደቆሳት ቤተመቅድስ ገባች።

Friday, January 6, 2017

የዕብራውያንን መልእክት እንዲህ እንረዳው? መቅድም

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ቀን 28/04/2009)

ክብር ይግባውና ሥላሴ በፍቅር ሸንጎው ስለ ሰው ልጆች መዳን ምክርን መከረ፡፡ ሰው በድሎአል አሳዝኖናልም ቢሆንም አርዓያችን ነውና ፈጽመን ልንጥለው አይገባንም  አለ። በመቀጠል “አዳም ከእኛ እንደ አንዱ ይሆናል” ለጊዜው ግን ከእኛ ርቆ ይኖራል ብሎ ወሰነ፡፡ ምክራቸውንም እውን ለማድረግ ዘመን የማይቆጠርለት ሥላሴ ቀን ቆረጠ፡፡ በአርዓያውና በአምሳሉ የፈጠረውን የሰውን ልጅ ቤተሰብ ሊያደርግና ከወደቀበት ሊያነሣው እንዲሁም በእሪናው ሊያስቀምጠው ወልድ በፈቃዱ ሰው ሆነ፡፡
እርሱም ከአምላክነት እሪናው ሳይለይ ከቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ተገኘ፤ ሥጋና ነፍስ ነሥቶ ከጸጋ ተጓድሎ ደህይቶና ጎስቁሎ የነበረውን የሰውን ባሕርይ ገንዘቡ በማድረግ ሁሉን ወራሽ አደረገው፡፡ ከሥጋዌ በፊት የአብ የሆነ ሁሉ የወልድ ነበር የወልድ የሆነ ሁሉ የአብ ነበር፡፡ ይህ ሥጋ በመሆኑ የቀረ አልነበረም፡፡ ይልቁኑ የቃል የሆነ ሁሉ የሥጋ በመሆኑ ምክንያት ቃል ሥጋን ሁሉን ወራሽ አደረገው፡፡
በዚህ ግን ቃል ብቻ ሳይሆን አብም መንፈስ ቅዱስም ሥጋን ሁሉን ወራሽ አድርገውታል፡፡ አብ በማጽናት መንፈስ ቅዱስ በመክፈል ወልድ በመዋሐድ እኩል ተሳትፎ ነበራቸው፡፡ ስለዚህ ሥጋን የእግዚአብሔር ቃል የሆነውን ሁሉ ገንዘቡ እንዲያደርግ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ እኩል ሚና ነበራቸው፡፡  ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ አብን ርስት ሰጪ በማድረግ ስለ ክርስቶስ “ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን” ማለቱ፡፡

Thursday, January 5, 2017

ዐይንተ አልባቢነ


ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
27/04/2009
መጽሐፍ ቅዱስ ሥጋንም ነፍስንም በተናጠል ሰውነት ይላቸዋል፡፡ ግዙፉን አካል ሰውነት እንዲለው አንዲሁ ቅዱስ ጳውሎስ “በመንፈሱ በውስጥ ሰውነታችሁ በኃይል እንድትጠነክሩ ክርስቶስም በልባችሁ በእምነት እንዲኖር እንደ ክብሩ ባለ ጠግነት መጠን ይስጣችሁ፤ የእናንተ መሠረት በፍቅር ይጸና ዘንድ”(ኤፌ.3፡16-17) ብሎ እንደጻፈልን ረቂቋንም ነፍስ ውስጣዊ ሰውነት ይላታል፡፡ ይህ የተዋሕዶን ምሥጢር ለማስረዳት  ትልቅ ቁልፍ ቃል ነው፡፡ ምንም እንኳ መጽሐፍ ሥጋንና ነፍስን በተናጠል ሰውነት ይበላቸው እንጂ ሰውነታችን አንድ ነው፤ ሁለት አይደለም፡፡ ሰውነት ስንል ደግሞ በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ የሥጋና የነፍስ አንድነት ስያሜ ነው፡፡ ሥጋና ነፍስ ፍጹም በሆነ ተዋሕዶ አንድ ሆነዋል፡፡ ነገር ግን የየራሳቸው ግብር አላቸው ቢሆንም በተናጠል አይደለም፡፡
በክርስቶስም የምናየው ይህንን ነው፡፡ እርሱ “እንግዲህ የሰው ልጀ አስቀድሞ ወደ ነበረበት ሲወጣ ብታዩ እንዴት ይሆናል?” በሚለው ቃሉ ለሰው ልጅነቱ ቅድምና ሰጥቶ መናገሩን እናስተውላለን፡፡ “በሁሉ ወንድሞቹን ሊመስል ተገባው”(ዕብ.2፡17) የሚለው ደግሞ ሰዋዊ ማንነቱ እንዳልተለወጠ ያስገነዝበናል፡፡ በዚህ ማነንቱ ሆኖ አምልኮ ለእርሱ ለእግዚአብሔር በግ ቀረበለት፡፡ ጌታ ተወለደልን ተባለ፤ ሕፃን ሳለ አምልኮን ከሰብአ ሰገል ተቀበለ፡፡ አንድያ የአግዚብሔር ልጅ፣ አምላክ፣ እግዚአብሔርም ተባለ፤ በደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ” ተብሎ”ደሙ" የእግዚአብሔር ደም ተባለ፡፡ በዚህም መለኮታዊ ልዕልናውን የሰው ልጅ ሲል እኛንም በመምሰሉ ራሱን የሰው ልጅ ብሎአል፡፡ ለሁለቱም ማንነቱ አንድ "የሰው ልጅ" የሚለውን ስያሜ ተጠቀመ፡፡ ይህም ከድንግል የተካፈለውን ሰውነት ከመለኮታዊ ልዕልናው መለኮታዊ ልዕልናውን ከሰውነቱ ነጣጥሎ እንዳላስተማረን በተረዳ ነገር ታወቀ፡፡ በዚህ ጥቅስና በሌሎችም ጥቅሶች ጌታችን የተዋሕዶውን ምሥጢር ገለጸልን፡፡