Saturday, January 21, 2012

ስለሦስተኛው ልደት(ጥምቀት) ምን ያህል ያውቃሉ?



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
12/05/2004
እነኋት ክርስትና ከሚለው መጽሐፌ የተወሰደ
እንደ ሶርያ ቅዱሳን አባቶች አስተምህሮ ሦስት ዓይነት ልደታት አሉ፡፡ እነርሱም ከሥጋ እናታችን የምንወለደው ልደት፣ ከውኃና ከመንፈስ የምንወለደው ልደት(ይህ በእግዚአብሔር በሆነው ሁሉ ላይ መብትን የሚሰጠን ነው) ሦስተኛውና መሠረታዊው ልደት የፈቃድ ልደት ነው፡፡ ይህ ልደት ሦስተኛው ልደት በመባል ይታወቃል ወይም ሦስተኛው ጥምቀት ይባላል፡፡ ለዚህ ልደት የሚበቃው ሰውነቱን በጥምቀት የመንፈስ ቅዱስ ቤተመቅደስ ያደረገ ክርስቲያን ነው፡፡ ይህ ክርስቲያን በውስጡ ላደረው መንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ሲታዘዝ ክርስቶስን ወደ መምሰል ይመጣል፡፡ አንድ ክርስቲያን ልክ እንደ ሐዋርያው ጳውሎስ ክርስቶስን ወደ መምሰል ማዕረግ ሲያድግ ሦስተኛውን ልደት ተወለደ ይባላል፡፡ እኛ ክርስቲያኖችም ለዚህ ተጠርተናል፡፡ ለመሆኑ በዚህ በፈቃድ ልደት ውስጥ ያለ ክርስቲያን ላይ የሚንጸባረቁ ጠባያት ምን ምን እንደሆኑ ሶርያዊው ባለራእይው ዮሴፍ የዘረዘራቸውን እንመልከት፡፡