Wednesday, December 11, 2013

በአታ ለማርያም


03/04/2006
በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
(በዚህ በፊት በማኅበረ ቅዱሳን ድኅረ ገጽ የተለቀቀ ጽሑፍ)
ሰይጣን በእባብ አካል ተሰውሮ ሔዋንን፤ በእርሱዋም አዳምን በማሳት በእነርሱ ላይ ሞት እንዲሠለጥንባቸው ስላደረገ “በአንተና በሴቲቱ መካከል፣ በዘርህና በዘርዋም መካከል ጠላትነትን አደረጋለሁ፤ እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል፤ አንተም ሰኮናውን ትነድፋለህ”በማለት የፍቅር አምላክ እግዚአብሔር ፈረደበት፡፡ “በአንተ” የተባለው ሰይጣን ሲሆን ፣ “በሴቲቱ” የተባለችው ቅድስት ድንግል ማርያም ናት (ገላ.4፡4) ፣ “በዘርህ” ሲል የዲያብሎስ የግብር ልጆችን ሲሆን(ዮሐ.8፡49)፣ “በዘርዋ” የተባለው ክርስቶስ ነው(ገላ.3፡16)፡፡ ትርጉሙ እንዲህ አንደሆነም ወንጌላዊው ዮሐንስ “ዘንዶው በሴቲቱ ላይ ተቆጥቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ የጠበቁትን የኢየሱስም ምስክር ያላቸውን ከዘርዋ የቀሩትን ሊዋጋ ሄደ በባሕርም አሸዋ ላይ ቆመ”አለን፡፡(ራእ.12፡17) እባብ የተባለው ሰይጣን ስለመሆኑም “ዓለሙን ሁሉ የሚያስተው ዲያብሎስና ሰይጣን የሚባለው ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ተጣለ”(ራእ.12፡9) ብሎ ጻፈልን፡፡

Monday, October 21, 2013

ጌታችን የእግዚአብሔር ምሥጢር የመባሉ ምክንያት



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

ቀን 11/02/2006
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለልደቱ ጥንት ለሕይወቱ ፍጻሜ የሌለው አልፋና ኦሜጋ ነው፡፡ በሥጋ ከመገለጡ በፊት ቅዱስ ዮሐንስበዓለምም ነበር ዓለሙ አላወቀውም ነበርእንዲል በዓለሙ ሙሉ ሆኖ የሚኖር እግዚአብሔር ነው፡፡ አንዳንዶች በዓለም ነበር ሲባሉ ለምድር መነሻ እንዳላት ለእርሱም መነሻ አለው እንዳይሉ  ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊውብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበርብሎ አስቀድሞ ጻፈልን፡፡
 በዓለም ነበር ሲልም ዓለምን ፈጥሮ የሚገዛት እርሱ መሆኑን ያስረዳናል፡፡ ነገር ግን በሥጋ ማርያም አስኪገለጥ ድረስ ዓለም አላወቀችውም ነበር፡፡ አይደለንም እኛ መላእክት እንኳ አላዩትም፤ ነገር ግን ለእነርሱ በሰው አምሳያ ይታያቸው ነበረ፡፡ እነርሱም ለእርሱ አምልኮትን በአምሳያው ፊት ይፈጽሙ ነበር፡፡ እርሱ በሰው አምሳል ለመላእክት ተገልጦ ይታያቸው ነበር እንጂ በፍጹም እርሱነቱ ያልተገለጠ ማንም በማይቀርበው መለኮታዊ ብርሃን ውስጥ የሚኖረው ፈጣሪ ነው፡፡ እርሱ ስሙ እውነተኛ ብርሃን የሆነ እኛን ለማዳን ወደ ዓለም መጣ፡፡ ያም ማለት ሰው ሆነ፤ ለእርሱ አንድ ነገርን ለማድረግ መውጣት መውረድ የሚገባው አይደለም፤ ነገር ግን ሰው መሆኑን እንድንረዳ “ወደ ዓለም ይመጣ ነበር” ተብሎ ተጻፈልን፡፡

በክርስትና ያለ እምነት እስከዚህ ድረስ ይረቃል


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
11/02/2006
 ክርስቲያን በክርስቶስ እንደሞተ ሊያምን ሕይወቱም ከክርስቶስ ጋር እንደተሰወረ ወይም ሕይወቱ ከሕያዋን ቅዱሳን ጋር አንድ እንደሆነ ሊያምን ይገባዋል፡፡ በክርስቶስ ያለው ሕያውነት በፈቃድ በሚሆን ሞት ማለትም ጥምቀት የመጣ ነው፡፡ በፈቃዳችን በእምነት ከክርስቶስ ጋር ሞተን የትንሣኤውም ተካፋይ በመሆን በክርስቶስ ሕያዋን ሆነን እንኖራለን፡፡ አሁን ያለን ሕይወት ከሕያዋን ጋር አንድ የሚያደረገን ሕይወት ነው፡፡ በሥጋ ሞት ሞትንም አልሞትንም በክርስቶስ በተነሣነው ትንሣኤ ሁሌም ለዘለዓለም ሕያዋን ሆነን እንኖራለን፡፡ ስለዚህ ለአንድ ክርስቲያን የሥጋ ሞት ከሕያዋን ጋር የሚያቆራርጠው ወይም እነርሱ በሥጋ ስለተለዩት ከእርሱ የሚለዩት አይደለም ይልቅ በክርስቶስ አንድ ቤተሰብ በመሆን የአንድ የእግዚአብሔር ልጆች ሆነው የሚኖሩበት ነው፡፡ ይህ በክርስቶስ ሞቼ ከክርስቶስ ጋር ተነሥቼለሁ አሁን ያለሁት ቅዱሳን በከተሙበት በሰማያዊ ሥፍራ ነው፡፡ እንዲያም ቢሆን በሥጋ ስላልሞትሁ በዚህ በሰማያዊ ሥፍራ ሆኜም ውጊያ አለብኝ በውጊያዬ ደግሞ ሰማያዊያን መላእክት እንደሚራዱኝ እንዲሁ በሰማያዊ ሥፍራ ፍጹም ዕረፍትን ያገኙ ቅዱሳን የእግዚአብሔርና የክርስቶስ ካህናት ሆነዋልና እድን ዘንድ በጸሎታቸው ይራዱኛል የሚለው እምነት ከክርስቶስ ጋር ሞቼ በትንሣኤው ሕይወት ሕያው ሆኜ እኖራለሁ ብሎ ማመንን በብርቱ የሚጠይቅ እምነት ነው፡፡

Wednesday, October 16, 2013

ምንኩስናና ትዳር የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች


05/02/2006
በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ


ክርስትና ለሰይጣን ይገዛ ከነበረ ዓለም ወጥቶ እርሱ የጽድቅ ጸሐይ የሆነው ክርስቶስ ብርሃን ሆኖት በቀን እንጂ በጨለማ የማንመላለስበት የቀን ልጅ ተሁኖ የሚኖርበት ሕይወት ነው፡፡ ክርስትና ከክርስቶስ ጋር ተሰቅለን ነፍስ በምትሰጠው ሕይወት ሳይሆን ለዘለዓለም አባ አባ ብለን የምንጠራበትን መንፈስ በሰጠን በመንፈስ ቅዱስ ሕያዋን ሆነን የምንኖርበት ሕይወት ነው፡፡ ስለዚህም ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር ራሳችንን ለጽድቅ ሥራ ያጨን ደናግላን ነን፡፡ አገባንም አላገባንም ለክርስቶስ የታጨን በመሆናችን ደናግላን ነን፡፡ ይህ ድንግልና የሚጠፋው ክርስቶስን ክደን በሰይጣን ሕያዋን ሆነን የኖርን ሰዓት ነው፡፡ቢሆንም ግን ይህም ቢሆን በንሥሐ የሚታደስ ድንግልና ነው፡፡ ጌታ ጠፍተን እንድንቀር የማይወድ ከኃጢአታችን ይልቅ መጥፋታችን የሚያሳዝነው በንስሐ በተመለስን ጊዜም በደስታ እጆቹን ዘርግቶ በፍቅር የሚቀበለን አምላክ ነው፡፡

Friday, August 16, 2013

የሙታን ትንሣኤና የጥምቀት ፍሬ እንዲህ ነው (1ቆሮ.15፡45-50)



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
10/12/2005 ዓ.ም
ቅዱስ ጳውሎስ “የሙታን ትንሣኤ እንዲህ ነው፡-” በማለት  ትንሣኤችንን ከለበስነው ሰማያዊ አካል ማለትም በጥምቀት ከለበስነው አዲስ ተፈጥሮ ጋር አዛምዶ ሂደቱን እንዲህ ይገልጥልናል፡፡ “በመበስበስ ይዘራል” ይህ አስቀድመን ስለለበስነው በዘር በሩካቤ ስላገኘነው ሰውነት ሲናገር ነው፡፡ ይህ አካል ሟችና በስባሽ አካል ነው፡፡ ስለዚህም “በመበስበስ ይዘራል” ያም ማለት ይሞታል፡፡ ይህም ስለትንሣኤችን ሊናገር እንደ መንደርደሪያ ያነሣው ነጥብ ነው፡፡ ሲቀጥል “ባለመበስበስ ይነሣል” ይላል፡፡ ይህ ቃል የሰውን ሁሉ ትንሣኤ ይናገራል እንጂ የክርስቲያኖችን ትንሣኤ ብቻ የሚናገር አይደለም፡፡ በትንሣኤ የሰው ዘር ሁሉ ለፍርድ ይነሣል፤ ዘለዓለማዊ ደስታን ወይም ዘለዓለማዊ ኩነኔን በኃጥአንና በጻድቃን ላይ በሚፈርደው በክርስቶስ የፍርድ ወንበር ፊት ቆሞ ይቀበላል፡፡(2ቆሮ.5፡10) ይህም አንዱ ለጽድቅ አንዱ ለኩነኔ መነሳቱን የሚገልጥ ነው፡፡
ቀጥሎ ግን በእውነት ክርስቲያን ለሆኑት ወገኖች የተሰጠው ትንሣኤ ምን እንደሚመስል ያስረዳል፡፡ ምክንያቱም በጥምቀት አዲሱን ሰው ብንለብሰውም ተመልሰን ለኃጢአት ባሮች ከሆንን በጥምቀት አዲሱን ሰው በመልበሳችን አንዳች ዋጋ እንደሌለን አስቀድሞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አስተምሮናልና “ወንድሞች ሆይ” ይለናል “ይህን ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ፡፡ አባቶቻችን ሁሉ ከደመና በታች ነበሩ” አለን፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ያላቸው የቆሮንቶስ ክርስቲያኖችን እንደሆነ አንባቢው ልብ ሊል ይገባዋል፡፡ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ከጣዖት አምልኮ ወደ እግዚአብሔር አምልኮ የመጡ ናቸው ወይም አሕዛብ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ለእነርሱ “አባቶቻችሁ ናቸው” ያላቸው እስራኤላዊያንን እንደሆነ አስተውሉ፡፡

Saturday, June 1, 2013

በድዳና ደንቆሮው ሰው ስለ ሥነ- ተፈጥሮ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
24/09/2005
“ስብከት ወተግሣጽ ዘቅዱስ ኤፍሬም” ከተባለ መጽሐፌ የተወሰደ
እናንተ እውራን ሆይ ኑ ቅረቡ ያለዋጋ ብርሃንን ተቀበሉ ፡፡ እናንተ እግራችሁ የሰለለ ኑና በጌታ ተፈወሱ፤ አንተ ድዳና ደንቆሮ ናና ቃልን ከአምላክህ ተቀበል”
 በእጆቹ ጣቶች ጌታ የፈወሰው ያ ድዳና ደንቆሮ ሰው አምላክ ወደ እርሱ ቀርቦ ምላሱን እንደፈታለት ፣ ጆሮውንም እንደ ከፈተለት ተረድቶ ነበር፡፡(ማር.፯፥፴፩-፴፯) ምላሱ ረቶ እንዲናገር ፣ ጆሮውም እንዲሰማ  የጌታ ጣቶች ባይነኩት ኖሮ መለኮት እንደነካው ባልተረዳ ነበር ፡፡ ነገር ግን በጣቶቹ መለኮት የምላሱን እስራት ፈታ የጆሮዎቹን በሮች ከፈተ፡፡
ሰውነታችን ፈጣሪ የሆነው እርሱ ወደ ሕመምተኛው ቀረበ ግሩም በሆነው ድምፁ ያለአንዳች ሕመም የጆሮዎቹን መስኮቶች ከፈታው፡፡ አንደበቱ ቃልን ከመውለድ መክኖ የነበረውን ይህን ድዳ ሰው የምስጋናን ቃል እንዲወልድ በማድረግ የቃል መካንነቱን አራቀለት፡፡ አዳምን ሲፈጥረው ያለ አንዳች ትምህርት እንዲናገር እንዳደረገው፤ እንዲሁ ይህንንም ድዳና ደንቆሮ የነበረውንም ሰው ተምሮ ለማወቅ አስቸጋሪ የሆነውን ቋንቋ በአንዴ እንዲናገር አበቃው፡፡

Saturday, May 25, 2013

አቤቱ ይህን አትንሣን!!!



17/09/2005
በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ሰው የሚድነው በእግዚአብሔር ጸጋ ነው “በጸጋ ድናችኋልና” እንዲል፡፡ ክርስቶስ ዘለዓለማዊውን ጸጋውን ከሰጠን ቆየ ክርስትናም በክርስቶስ ከተመሠረተች እጅግ ቆየች ግን አሁንም ያው ነች ሰማያዊት ናትና የዘመን ቁጥር የላትም ሁሌም አዲስ ናት፡፡ ሰዎችን ዘመን ከማይቆጠርባት ሰማያዊት ሀገር ታፈልሳለች በዚያም ሰማያውያን ቅዱሳን መላእክትና ቅዱሳን ነፍሳት ከትመዋል፡፡ ሰው ልቡናው ከበራ የሚኖርባትን ዘመን የማይቆጠርላትን ሰማያዊቱን ዓለም ይረዳታል ጣዕሙዋንም ይቀምሳል፡፡ ጣዕሟን ማንም በቃላት ሊገልጣት አይችልም፡፡ ለዚህ ዓለም ቋንቋ ባዕድ ናት ሕይወቱዋም ልዩ ነው፡፡ ይህችን ጣዕም እየቀመሱ መኖር እንዴት መታደል ነው!!! ቢሆንም የሚወደን አምላክ እርሱዋን አልነሣንም ግቡም ይህ ነው የዚህች ሰማያዊት ስፍራን ጣዕም በሁለመናችን እንረዳትና በእርሱዋ ውስጥ ለዘለዓለም እንድንኖር ነው፡፡ ጌታ ሆይ ከዚህች ሥፍራ በመንፈስ እንዳንወጣ ሁሌም የዚህችን ሰማያዊት ሥፍራ እያጣጣምን እንድንኖር እርዳን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡ 

የትኛውን በግ ኖት?


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
17/09/2004


አቤል ቅን ሰው ነበር፤ ነገር ግን እንደ በግ ወደ ዱር በገዛ ወንድሙ ቃየን ተነድቶ ተገደለ፡፡ እንደ አቤል በቃየል የተገደሉ ብዙ ወገኖች አሉን፡፡ በአሁኑ ጊዜ ግን እንደ ቀድሞው አቤል መሆን የሚያዋጣ አይደለም፡፡ በአሁኑ ቃየኖች የሚገደሉ አቤሎች ሞታቸው የነፍስ ሞት ነው፡፡ ቃሉም የሚነግረን አሰናካዩም ተሰናካዩም አብረው እንደሚጠፉ ነው፡፡ በግ እንድንሆን የተጠራን ቢሆንም የትኛውን የበግ ዐይነት መሆን እንደሚገባን ግን ልንለይ ይገባናል፡፡ ሁለት ዓይነት በጎች አሉ፡፡ አንደኞቹ በጎች በእውነት ክርስቶስን የመሰሉ በቀኝ የሚቆሙት ቅዱሳን ናቸው፡፡ እነዚህ በየትም አቅጣጫ እንደቀድሞው አቤል ላታላችሁ ብትሉ አይሳካላችሁም፡፡ ምክንያቱም እነርሱ የሚመሩት በመንፈስ ቅዱስ ነውና፡፡ መንፈሳዊውን ሰው ፍጥረታዊው ሰው ሊመረምረው አይችልም፡፡ ፍጥረታዊው ሰው መንፈሳዊው መረዳት የለውም፡፡ መንፈሳዊው ግን ፍጥረታዊውን ያውቀዋል ይመረምረዋል፡፡ እናም የፍጥረታዊውን የቃየንን አመለካከት የሐዲስ ኪዳኑ አቤል፣ ጌታን የለበሰው ከጻድቃን ሕብረት ያለው በግ ፈጥኖ ይረዳዋል፡፡ ነገር ግን እንደው የጥፋትም በጎች አሉ፡፡ ለእነርሱ ልቤ ያዝናል፡፡ ዳዊት ስለእነርሱ
“ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ አያውቅም እንደሚጠፉ እንስሶች መሰለ፡፡ ይህች መንገዳቸው መሰናክላቸው ናት ከእነርሱም በኋላ የሚመጡ በአፋቸው እሺ ይላሉ፡፡ እንደ በጎች ወደ ሲኦል የሚሄዱ ናቸው እረኛቸው ሞት ነው፡፡”(መዝ.48፡12-14) ይላቸዋል፡፡ እነዚህ በጎች ያሳዝኑኛል፡፡ ለነፍሳቸው እረኛው ሞት ነው፤ ሞትም በቁማቸው ይገድላቸዋል፡፡ መሞታቸውን ግን አይረዱትም እነዚህ እንደ ቀድሞውም አቤል በነፍሳቸው ያልተጠቀሙ ከአዲሶችም አቤሎች ኅብረት የሌላቸው እንደው ሞት የነጋራቸውን ሁሉ አሜን ብለው የሚቀበሉ ናቸው፡፡ አቤቱ ሰውን ሁሉ ሞት ወደ ሲኦል የሚመራው በግ አታድርገው፡፡ ይልቅ አንተን መስለው ሰይጣንን ወደ ሲኦል የሚነዱ አድርጋቸው እንጂ፡፡

Tuesday, March 12, 2013

“በሥጋ ሞተ በመንፈስ ግን ሕያው ሆነ”(1ጴጥ.3፡18)



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
03 /07/2005
እግዚአብሔር መንፈስ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስም እግዚአብሔር ነው፤ ስለዚህ በእግዚአብሔነቱ መንፈስ ነው፡፡ ያም ማለት ግን ሥጋና አጥንት የለውም ማለት አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ሰው ሲሆን አምላክነቱ ሳይለወጥ እንደሆነ እንዲሁ ሥጋ አምላክ ሲሆን የሥጋ ባሕርይውን ሳይለውጥ ነው፡፡ ያም ማለት ረቂቁ ረቂቅነቱን ሳይተው ግዙፍ ሆነ፤ ግዙፉም ግዙፍነቱን ሳይለቅ ረቂቅ ሆነ ማለት ነው፡፡ ይህም ሰውነቱ አምላክም ሰውም ነው ማለት ነው፡፡
ይህን ከትንሣኤ በፊት ከልደቱ ጀምሮ የምናስተውለው እውነታ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በድንግልና ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ፡፡ ይህ ግዙፍ ሆኖ ነገር ግን ረቂቅ መሆኑን ያሳየናል፡፡ መጽሐፍ ሰብአ ሰገል ለሕፃኑ ሰገዱ ይለናል፡፡(ማቴ.2፡30) ለመለኮት ሕፃን የሚለውን ቃል አንጠቀምም ነገር ግን ከድንግል ማርያም ለነሳው ሰውነት ይህን ቃል እንጠቀማለን፡፡ ስለዚህ ለሕፃኑ ሰገዱ ሲሉ ለሰውነቱ ሰብአ ሰገል ሰገዱ ሲለን ነው፡፡ ይህም ሥጋ አምላክ መሆኑን ያረጋግጥልናል፡፡

Wednesday, February 27, 2013

የዛሬ ገጠመኜ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
20/06/2005
ዛሬ አንድ የገጠመኝን ገጠመኝ ላውጋችሁ እንዲህ ነው፡- አንድ የልብ ወዳጄለሆነ ጉዳይ እፈልግሃለሁብሎ ወደ እርሱ በታክሲ አመራሁ የሥራ ቦታው ወደ መስቀል ፍራዎል አካባቢ ነበር፡፡ ሄድኩ በፍቅር ተወያየን ለእኔ ጥሩ አሳቢ ነበርና በእርሱ አምላኬን አመሰገንኹት፡፡ ከእርሱ ጋር ውይይቴን ከጨረስኩ በኋላ ከአምባሳደር ዐራት ኪሎ የሚለውን ታክሲ ይዤ ወደ ቤቴ አመራሁ፡፡
በመንገድ ላይ ሳለሁ ግን አንድ ወዳጄ ከክፍለሀገር ደወለልኝ፡፡ ስለ ግል ጉዳያችን ከተጠያየቅን በኋላ ወደ መጨረሻ ላይ ለመሆኑየአብርሃም ርስት ርስታችንየሚለውን ምንባብ ተመለከትከውን? አልኩት ተመልከቼዋለሁ ግን ካነበብኩት ስለቆየሁ እስቲ ትን አስታውሰኝ አለኝ፡፡ እኔምለአብርሃም በራሱ ምሎ በመሐላ መካከል የገባውና በሞቱ ርስቱን ለአብርሃምና የአብርሃምን እምነት ይዘው ላሉት ሊያወርስ ሰው ሆኖ በመስቀል ላይ ራሱን ስለሰዋው እግዚአብሔር ቃል የሚያትት ነው” ብዬ አስታወስኩት፡፡ እርሱም ፈላስፎች የሚያነሡትን ጥያቄ አስታውሶ እንዲህ አለኝ፡- “ክርስቶስ እግዚአብሔር ከሆነ እርሱ ሞቶ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት በከርሰ መቃብር ውስጥ ከነበረ በእነዚህ ሦስት ቀናት ውስጥ ዓለምን የሚመግባት ማን ነበር? ብለው ፈላስፎች ይጠይቃሉና ስለዚህ ምን ትላለህ? ብሎ ጠየቀኝ፡፡ ይህ ጥያቄ እንደው ለእነርሱ ከባድ መስሎአቸው ያነሱት ጥያቄ እንጂ ፍልስፍናን በማወቃቸው የጠየቁት ጥያቄ አይመስለኝም፡፡