Friday, April 14, 2017

የነፍስ ወግ

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
6/08/2009

ረቂቅ የሆነ እርሱ ፈጣሪዬ በእርሱ ፊት ምንም ግዙፍ ብሆን ሚስቴ ላደረጋት ከምድር አፈር ለፈጠራት ሥጋዬ በእርግጥም ረቂቅ ነኝ፡፡ እርሱ የፈጠረኝ አምላክ በእርሱ አርአያና አምሳል የፈጠረኝ ቢሆንም እንደርሱ ረቂቅ ስለሆንኹ ረቂቃኑ መላእክትም ግዙፋኑ ፍጥረታትም የእርሱን አርአያ በግዘፍ እንዲያዩ አምለክ ሥጋ ሚስቴን ግዙፍ አድርጎ ፈጠራት፡፡
 ከመላእክት እኔ የምለየው ከሥጋ ጋር አንድ አካል መሆን ስለሚቻለኝ ነው፡፡ በሌላ ተፈጥሮዬ ግን ከእነርሱ ጋር አንድ ነኝ፡፡ ቢሆንም ለእኔ ከውድቀት በፊት የነበረው የሥጋ ተፈጥሮ በእጅጉ ይስማማኝ ነበር፡፡ ምክንያቱም በገነት ለሥጋ የተሰጡ መብላት ሥጋን በሕይወት እንድትቆይ ምንም ዓይነት ሚና የላቸውምና ሥጋን በሕይወት ለማቆየት ስል ምንም ድካም የለብኝም ነበርና፡፡ ከውድቀት በኋላ ግን ከመላእክት ጉባኤ በልዩ ተፈጥሮ ሆኜ የአምላኬን ፍቅር እየተመገብሁ ከምኖርበት መኖሪያዬ ገነት በራሴው ጥፋት የክፋት ምክንያት የሆነውን ሞትን በሥጋዬ ላይ ሹሜ፥ ፍቅርን አጥፍቼ ፥ ፍርሃትን አንግሼ ከመላእክት ጉባኤ ተለየሁ፡፡