Saturday, March 10, 2012

“ጌታችን መዝጊያህን ዘግተህ…ጸልይ” የማለቱ ትርጉሙ(በአፍርሃት ሶርያዊ)


                 
ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
01/07/2004
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸሎታችን ምን መምሰል እንዳለበት ሲያስተምር “አንተ ግን ስትጸልይ ወደ እልፍኝህ ግባ መዝጊያህንም ዘግተህ በስውር ላለው አባትህ ጸልይ በስውር የሚያይህም አባትህ በግልጽ ይከፍልሃል፡፡”(ማቴ፡፮፥፮)ብሎ አስተምሮአል፡፡ ወዳጄ ሆይ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምንጸልይበት ጊዜ “ወደ እልፈኝህ ግባ መዝጊያህንም ዘግተህ በስውር ላላው አባትህ ጸልይ” ማለቱ የመኖሪያ ቤትህን ደጅ ዘግተህ ጸልይ ማለቱ ነውን ? እንዲህ ነው ብለህስ ስለምን ትረዳለህ ? ጌታችን እንዲህ ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ እስከቻልኩት ድረስ ላብራራልህ እሞክራለሁ፡፡
እርሱ “አንተ ግን ስትጸልይ ወደ እልፍኝህ ግባ መዝጊያህንም ዘግተህ ጸልይ” ሲልህ የልብህን ደጅ በመዝጋት እንድትጸልይ ሲመክርህ አይደለምን ? እኛ ልንዘጋው የሚገባን ጌታ ያዘዘን  በር የቱ ነው ? ቤቱ ሰውነታችን ፣ በሩ ልባችን ካልሆነ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል ? ሐዋርያው እንዳለው ሰውነታችን ክርስቶስ የሚኖርበት ቤተመቅደሱ ነው፡፡ እርሱ“ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት በእናንተ የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተመቅደስ እንደሆነ አታውቁምን?” አላለንምን?(፩ቆሮ.፮፥፲፱፣፳) ወደ ውስጥ ሰውነትህ ወይም ወደ ገዛ ቤቱ ገብቶ ያደር ዘንድ አፍህ ለጸሎት ሳይከፈት አስቀድመህ ማረፊያ ቤቱን ማጽዳት ማስተካከል ይገባሃል ፡፡ መልእክቱ ይህ ካልሆነ በቀር ኃይለ ቃሉ ምን የተለየ ሌላ ትርጉም አለው ? ወይስ አንተ ቤትና በር በሌለበት በምድረበዳ ብትሆን እንዲህ ስለሆነ ለሰማይ አባትህ በስውር መጸለይ አይቻልህም ማለት ነውን ? ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰማይ አባታችን የልባችንን መሻትና አሳብ እንደሚያውቅ “አባታችሁ የሚያስፈልጋችሁን ያውቃልና”(ማቴ፡፮፥፰ )ብሎ አስተምሮናል፡፡



በነቢዩ ኢሳይያስም “እንዲህም ይሆናል ሳይጣሩ እመልስላቸዋለሁ ገናም ሲናገሩ እሰማቸዋለሁ”(ኢሳ.፷፭፥፳፬)ሲል በተቃራኒው ደግሞ “እጃችሁን ወደ እኔ ብትዘረጉ ዓይኔን ከእናንተ እሰውራለሁ ፤ ልመናንም ብታበዙ አልሰማችሁም”ይላል፡፡(ኢሳ.፩፥፲፭) እንዲሁም “ወደ ጆሮዬም በታላቅ ድምፅ ቢጮኹ አልሰማቸውም”(ይለናል፡፡ሕዝ.፰፡፲፰) ጌታችን እንዲህ ያላቸው በሽንገላ ከልብ ያልሆነ ጸሎትን ለሚጸልዩት አይደለምንእያንዳንዱን ቃል በማስተዋል ሆነህ አድምጥ፤ ትርጉሙን በጥንቃቄ ጨብጥ፡፡ አዳኛችን ክርስቶስ በአንድ ቦታ ይህን የመሰለ ቃል ተናግሮአል፡፡ እናም ምን ለማለት እንደፈለገ በጥንቃቄ አድምጠህ ለይ፡፡
እርሱም “ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰባሰቡበት በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁ” የሚል ነው፡፡(ማቴ. ፲፰፥፳) ወዳጄ ሆይ በአንተ በኩል ይህን ኃይለ ቃል እንዴት ትረዳዋለህ ? መድኃኒታችን ሁለትም ሦስትም ሆናችሁ በተሰባሰባችሁበት ቦታ እኔ እገኛለሁ ማለቱ እኔ ብቻዬን ብሆን ክርስቶስ ከእኔ ጋር አይሆንም ማለት ነውን? ምክንያቱም ክርስቶስ በእርሱ በማመን በቅድስና በሚመላለሱት ዘንድ ማደሪያውን እንደሚያደርግ ተጽፎአልና፡፡(ዮሐ.፮፥፶፮-፶፯)  በዚህ ሊያስረዳ የፈለገው ከእርሱ ሊማሩ ሽተው ሁለትም ሦስትም ሆነው ቢሰባሰቡ በመካከላቸው አንደሚገኝ ሊያስተምረን አይደለምን?
ከሁለት ወይም ከሦስት በላይ ወይም ሺህ ሆነው የተሰባሰቡ ነገር ግን ክርስቶስ የማይገኝበት ጉባኤ አለ ፡፡ በተቃራኒው ደግሞ አንድ ብቻ ሆኖ ክርስቶስ ኢየሱስ ከእርሱ ጋር የሆነለት ሰው አለ ፡፡ ስለዚህም ይህ ቃል የተነገረው ቃሉ ለእነርሱ ውብና መልካም ለሆነላቸውና እርሱን ለመስማት ሁለትም ሦስትም ሆነው በጉጉት ለሚጠብቁት ሰዎች ነው ፡፡ እንደ ክርስቶስ ፈቃድ ልቡን ንጹሕ ያደረገ ሰው ክርስቶስ እና በክርስቶስ ሕልው የሆነው እግዚአብሔር አብ ያድርበታል ፡፡ ከዚያም ወዲህ ይህ ሰው ሦስት አካላት ያሉት አንድ ሰው ይሆናል ፡፡ እርሱ ፣ በእርሱ ያደረው ክርስቶስ እና በክርስቶስ ሕልው የሆነው እግዚአብሔር አብ በአንድ ሰውነት ይገለጣሉ ፡፡ በዚህም “እኔ በአብ እንዳለሁ አብም በእኔ  እንዳለ አታምንምን?”(ዮሐ. ፲፬፥፲-፲፩) ያለው የጌታ ቃል እንዲሁም “አኔና አብ አንድ ነን” የሚለው ቃል በዚህ ሰው እውን ይሆናል፡፡ (አፍርሃት እንዲህ ሲል “እኔ በአባቴ እንዳለሁ እናንተም በእኔ እንዳላችሁ እኔም በእናንተ እንዳለሁ በዚያ ቀን ታውቃላችሁ” ብሎ ጌታችን መድኃኒታችን ያስተማረው ትምህርት ለዚህ ሰው ይፈጸምለታል ሲለን ነው እንጂ አምላክ ይሆናል እያለን አይደለም፡፡)(ዮሐ.፲፥፴፤ዮሐ.፲፬፥፳)
በነቢዩም የተነገረው “በእነርሱ አድራለሁ ከእነርሱም ጋር እሄዳለሁ” (ሕዝ.፵፫፥፱፤ቆሮ.፮፥፲፮) የሚለው አምላካዊ ቃል በዚህ ሰው ሰውነት ውስጥ ይፈጸማል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረውን ይህን ትምህርት በዚህ መልክ መረዳት አለብን፡፡"




8 comments:

  1. ድንቅ አገላለጽ ነው ጸጋውን ያብዛልህን ቃለሕይወት ያሰማልን ወንድማችን

    ReplyDelete
  2. kale hiwot yasemaln !!! yikrta memher eni betam dekama neg stseliy huli emasbew lila new manbebien bicha Egziabhir yasblg enji salawkew lbi wedelila hasab yeseweral min madreg endalebg esti mkereg memher leyloch wedmochim ehtochim tebaberug Pls egziabhir yistelig .

    ReplyDelete
    Replies
    1. ወንድሜ እኔ እንደተረዳሁት ያንተ ትልቅ ጭንቀት የሆነብህ በጎ ሃሳቦች ወይም ዕለታዊ ኑሮዎችህን በተመለከተ በጸሎትህ ጣልቃ እየገቡ የሚታሰቡት ሃሳቦች አይደሉም፡፡ እነዚህ በማንም ላይ የሚከሰቱ ናቸው፡፡ ከዚህ ይልቅ ግን ገና ከኃጢአት ውስጥ ወጥተህ በንስሐ ሕይወት ውስጥ ካለህ ወይም ረዘም ላሉ ጊዜአት ሰውነትህን ገዝተህ በመኖርህ ምክንያት ከሰይጣን የሚመጡብህ ፈተናዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ የጽርፈት(የስድብ ቃላት) ድንገት ከአንደበትህ ወይም ከሕሊናህ ሊመነጩ ይችላሉ፡፡ ወይም የዝሙት ሃሳብ ሊነሳሳብህና ጸሎትህን ሊያውክህ ይችላል፡፡ በዚህን ጊዜ ሃሳቡ ካንተ የመነጨ ከሆነ በትክክል መረዳት ትችላለህና ይህ በእርግጥ ያስፈራል፡፡ስለዚህም እግዚአብሔር ይህን ያርቅልህ ዘንድ ለምን፡፡ ነገር ግን አብዛኛውን ጊዜ ሰይጣን የእኛ ሃሳብ አስመስሎ ድንገት የሚያሰርጻቸው የስድብ ቃላት እና የዝሙት ሃሳቦች አሉ፡፡ ይህ ሆን ብሎ ሰይጣን አንተን ከጸሎት ለማራቅ ሲል የሚጠቀመው ዘዴ ነው፡፡ ስለዚህ የእርሱ እንደሆነ ብቻ ማወቁ ለአንተ በቂ ነው፡፡ የእርሱ መሆኑን የምታውቀው ድንገት እነዚህ አሳቦች በሕሊናህ ሲከሰቱና አንደበትህ ላይ ሲውሉ ነው፡፡ እንዲህ ሲሆን ከሰይጣን የመነጨ እንደሆነ ተገንዝበህ አማትበህ ጸሎትህን ጨርስ፡፡ ይህ በሕይወት ዘመንህ ሁሉ የሚገጥም ፈተና ነው፡፡ ነገር ግን የተመስጦን ሕይወት እየተለማመድህ ስትመጣ በእጅጉ እየቀነሰልህ ይመጣል፡፡ በጸሎት በተሳነፍክ ጊዜ ግን በአንተ ላይ ይበረታብሃል፡፡ ነገር ግን ተመስጦ ሕይወት በአንድ ጊዜ የሚመጣ ሕይወት አይደለም፡፡ ወደ ተመስጦ ሕይወት ለመምጣት አስቀድሞ የትሕርምት ሕይወትን ገንዘብ ማድረግ ጠቃሚ ነው፡፡ ያም ማለት ምን ማለት ነው? ለራስ የጽሙና ጊዜ መስጠት ነው ማለት ነው፡፡ አብዝቶ መጸለይ፣ መንፈሳዊ መጻሕፍትን ማንበብና መመርመር በተለይ መጽሐፍ ቅዱስን፤አብዝቶ አለመመገብ እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡ ይህን የፈጸምን እንደሆነ ቀስ በቀስ ከዓለማዊ አስተሳሰቦች በመውጣት የመንፈሳዊውን ዓለም ጣዕም ወደ መቅመስ እንመጣለን፡፡ ነገር ግን ወደዚህ እንዳትመጣ ሰይጣን በጣም ይተጋል፤ ስለዚህ ከላይ የገለጥኩልህን ፈተናዎች በማምጣት “እኔ በእግዚአብሔር ፊት ጸሎትን ማቅረብ አልችልም” ወደ ማለት እንድትደርስ ይደክማል፡፡ ስለዚህ እወቅበት አርዝሞ መጸለይን በተመለማመድክ ቁጥር በዚያው ልክ ተመስጦንም እየተለማመድክ እንደሆነ ልብ በል፡፡ ተመስጦን ገንዘብህ ካደረግህ በኋላ ግን ሁሌም እግዚአብሔርን በማሰብ፣ ሰማያዊ ነገሮችን በመመራመርና በመፈተሸ ላይ ስለምትወጠር ሰይጣን መግቢያ ቀዳዳ አያገኝም፡፡

      Delete
    2. Egziabhir yakbrlig tsegawim yabzalh wendmi memher leseteheg des yemil hasab Amesegnalew. metshaf kudus anebalew gin gena jemari sle honkunew meseleg bzum aygebagm bedeb . gin Orthodox emnetiyen ewedalew . gin and sew jemari kehone mejemerya yetgaw yemetsihaf kfl manbeb alebet ? btnegreg min yimeslehal gizi kaleh memher keyikrta gara Amesegnalew .

      Delete
  3. ልክ ነህ ወንድሜ መጽሐፍ ቅዱስን ወዲያው ለመረዳት ያስቸግራል፡፡ ምክንያቱም በአንድ ምዕራፍ ውስጥ ብዙ በይዘታቸው የተለያዩ መልእክቶች ስለሚተላለፉ ነው፡፡ ይህ የአንድ መንፈሳዊ መጽሐፍ ጠባይ ነው፡፡ እንደመጽሐፍ ቅዱስ ዓይነት አጻጻፍ በጥንት ቅዱሳን አባቶች መጻሕፍት ላይ ይገኛል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደ አንድ ዛፍ ነው፡፡ ግንዱ አንድ ሲሆን ብዙ ቅርጫፎች ያሉት እጅግ ብዙ ቅጠሎች ያሉት ሲሆን ፍሬው ግን አንድ ነው ምንም በቁጥር አንዱ ቅርንጫፍ ከአንዱ ቅርንጫፍ ይበልጥ የሚያፈራ ቢሆን፡፡ ይህን ላስረዳህ፡፡ ግንዱ አንድ እግዚአብሔር ነው፡፡ ወይም ሥሩ እግዚአብሔር አብ ነው ግንዱ ክርስቶስ ነው ለዛፉ ሕይወት የሚሆነውን ፍሬ እንዲሰጥ የሚያደርገው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡
    ቅርንጫፎቹ እኛ ነን ቅጠሎቹም ፍሬ እንድናፈራባቸው የተሰጡን ጸጋዎች ናቸው አንድ ዛፍ ፍሬ ከሰጠ በኋላ ቅጠሉን እንደሚያረግፍ እንዲሁ ፍሬ መንግሥተ ሰማያትን ካፈራን በኋላ ጸጋዎቹ አያስፈልጉንም ፡፡ ሌላም አለ የመጽሐፍ ቅዱስ አንዱ ክፍል ከአንድ ጉዳይ ይነሣና ከተነሣበት ጭብት ጋር ፈጽሞ የተለየ ሃሳብን አንስቶ ምናልባትም ብዙ ሃሳቦችን ሊሆን ይችላል ከዚያ በኋላ ወደተነሣበት ርዕሰ ጉዳይ ይመለሳል፡፡ ግንዱን አይለቅም፡፡ ይህን የአንድ የዛፍን ባሕርይ በመመልከት መረዳት ትችላለህ፡፡ አንድ ዛፍ ምንም እጅግ ቅርጫፎች ቢኖሩት ከግንዱ የተቀበለውን ከተጠቀመ በኋላ በምላሹ ለግንዱ የሚያደርሰው የራሱ የሆነ ሥርዐት አለው፡፡ ተመልከት ወዳጄ ምግቡን የሚያዘጋጅበትን ውሃና ሌሎችም ንጥረ ነገሮች ሲያገኝ ከባቢ አየሩንና ፀሐይን በቅጠሉ ተጠቅሞ ምግቡን ያዘጋጃል ይህንን ሲፈጽሙ ከግንዱ ያገኘውንም በአንድነት ነው፡፡ ስለዚህ ግንዱ ያ ቅርንጫፍ ፍሬ እንዲያፈራ ያደርገዋል፡፡ ቅርንጫፉ እርሱ የሚወጣው ሚና አለው ነገር ግን ፍሬ እንዲያፈራ የሚያደርገው ግንዱ ነው፡፡
    ስለዚህ የዚህ ሒደት ተጠቃሚ ለመሆን ከፈለግህ ዛፉን በትክክል ማወቅ ይኖርብሃል፡፡ ያም ማለት መጽሐፍ ቅዱስን ከሀ - ፐ ማለትም ከዘፍጥረት እስከ ራእይ ዮሐንስ ድረስ አንብበህ መጨረስ አለብህ፡፡ ያለበለዚያ መጽሐፍ ቅዱስን መረዳት አትችልም፡፡ አንዱን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል አንብበህ ሌላውን መተው ማለት ሥሩን አውቀህ ግንዱንና ቅርንጫፉን አለማወቅ ወይም ግንዱን አውቀህ ሥሩንና ቅርንጫፉን ብሎም ቅጠሉንና ፍሬውን አለማወቅ ማለት ነው ይህ ደግሞ ተሰነካከለ መውደቅህ የማይቀር ይሆንብሃል፡፡ ስለዚህ ፕሮግራም አውጥተህ መጽሐፍ ቅዱስን ሙሉ ለሙሉ ቢያንስ በዓመት ሦስቴ መላልሰህ ልታነበው ይገባሃል፡፡ ያለበለዚያ እንደ አንድ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን ልትቆም አትችልም፡፡ ኦርቶዶክሳዊ ጽንሰ አሳቦችንም መረዳት የምትችለው ከዚያ በኋላ ነው፡፡ ምሳሌ እንዲሆን እኔ የምጠቀምበትን ፕሮግራም ልስጥህ፡፡
    የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባብ መርሐ ግብር
    መጽሐፍ ቅዱስን የማንበብ ልማድን ለማዳበር ሲባል የወጣ የምንባብ መርሐ ግብር፡፡ በዚህ መልክ መጽሐፍ ቅዱስን የምናነብ ከሆነ መጽሐፍ ቅዱስን በዓመት ውስጥ ከሁለት ጊዜ በላይ ከማንበብ ባለፈ በየቀኑ በሕሊናችን የምናኖረው እግዚአብሔራዊ እውቀት ይኖረናል፡፡
     የንባብ ሰዓቶቹ በቤተክርስቲያን የፀሎት ሥርዐት መሠረት ሰባት ሰዓታት ሲሆኑ እነርሱም ከጠዋት12 ሰዓት፣ እኩለ ቀን 6ሰዓት ፣ከሰዓት 9 ሰዓት ፣ከምሽቱ 12 ሰዓት፣ ከሌሊቱ 6 ሰዓት፣ ከሌሊቱ 9 ሰዓት ናቸው፡፡
     የንባብ መነሻ ክፍሎች የሚሆኑት ዘፍጥረት (ብሔረ ኦሪት)፣ ኢዮብ ( የጥበብ መጻሕፍት)፣ ኢሳይያስ (የትንቢት መጻሕፍት)፣ ማቴዎስ( ወንጌላት)፣ ሮሜ (መልእክታት)፤ እነዚህ መነሻ የምንባብ ክፍሎችና ዋና ዋናዎቹ የመጽሕፍ ክፍሎች ናቸው፡፡
     ከእነዚህ በቀን ውስጥ አንድ ጊዜ የዮሐንስ ወንጌል በሦስት በሦስት ምዕራፍ ተከ
    ለምሳሌ
    የእለቱ ምንባብ ክፍል
    የምንባብ ቀን የቀን ምንባብ
    ከተሰጡት የምንባብ ክፍሎች በቀን ውስጥ የማታ ምንባብ
    12 ሰዓት 6ሰዓት 9 ሰዓት 12ሰዓት 12 ሰዓት 6ሰዓት 9 ሰዓት
    1 መስከረም1 ዘፍ.1-3፣ ኢዮ.1-3 ኢሳ.1-3፣ ማቴ.1-3 ሮሜ.1-3 ዘፍ.4-6፣ ኢዮ.4-6 ኢሳ.4-6፣
    ማቴ.4-6 ሮሜ.4-6
    2 መስከረም2 ዘፍ.7-9፣ ኢዮ.7-9 ኢሳ.7-9 ማቴ.7-9 ሮሜ.7-9 ዘፍ.10-12 ፣ኢዮ.10-12 ኢሳ.10-12፣ማቴ.10-12 ሮሜ.10-12፣

    ReplyDelete
  4. Egziabhir yistilg memeher tsegawn yabizalhh Amesegnalew.

    ReplyDelete
  5. memihiri wedtemesito lemitati wanignawi menigedi minidin new memihiri ebakowin biyasiredugni Egiziabihari yisitiligni segawin yabizaloti

    ReplyDelete
    Replies
    1. በቅርብ ምላሽ ለመስጠት እሞክራለሁ ወንድሜ

      Delete