Sunday, February 19, 2012

ያልታወቀው የጦም ጥቅም



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
12/06/2004



ብዙዎቻችን የጦም ጥቅሙ ከምግብ ተከልክለን ራሳችንን ከእግዚአብሔር ፊት በማዋረድ ከእርሱ ዘንድ ሰማያዊ ጸጋን ማግኘታችን ነው፤ ብለን እናስባለን፡፡ ይህ ፍጹም ትክክል ነው፤ ነገር ግን ክብር ለእርሱ ይሁንና ሌላ እኛ የማናውቀው በጦም የኖሩ ቅዱሳን የሚያውቁት አንድ ልዩና ግሩም የሆነ ጥቅም አለው፡፡ እንዲህ ሲባል “ከእኛ ምን ተሰውሮ! በጦም ነፍሳችን ለሥጋ ከመትጋት ወጥታ ከእግዚአብሔር ጋር በተመስጦ በመኖሯ ነፍሳችንም ሥጋችም የሚጠቀሙት ጥቅም አላቸው፡፡” ብላችሁ ትመልሱልኝ ይሆናል፡፡ እንዲህ የመለሳችሁ እንደሆነ እኔ ልገልጠው ያሰብኩትን ጭብጥ አላገኛችሁትምና ሌላ ሞክሩ፡፡ ወይም "ከጤና አኳያ ሰውነታችንን ከምግብ በከለከልናት ጊዜ አካላችን በራሱ የአሠራር ሥርዐት በሰውነት የተከማቸውን ስብ ወደ መጠቀም ስለሚመጣ የስብ ክምችታችን ይቀነሳል፤ ስለዚህም በስብ ክምችት ምክንያት ከሚመጡ ሪህ፤ ደም ግፊትና ስኳር እንዲሁም እነዚህን ከመሰሉ ሕመሞች ይጠብቀናል፡፡ ስለዚህም ሰውነታችንን ጤናማ በማድረግ ያለምንም የጤና መጓደል መንፈሳዊ የሆኑ ተግባራትን ለማከናወን ስለሚያገለግለን ነው” ብላችሁ ልትመልሱ ትችላላችሁ፡፡ እኔ ግን መልሱን አላገኛችሁትም ነው መልሴ፡፡ “እሺ ይህ ካልሆነ እኛ ጌታችንን መስለን በመጦም ሰይጣንን ድል መንሳታችን ነው ጥቅሙ” ትሉኝ ይሆናል፡፡ እርሱም ጥሩ መልስ ነው፡፡ ምክንያቱም ጦም ነፍስን እንደ መልአክ ስለሚያደርጋት ወይም የሥጋ ሥራ ስለሚቀልላት ዐይኖቹዋ በጦም ሰዓት አጥርተው ይመለከታሉና በቀላሉ ሰይጣን ድል ሊነሳት አይቻለውምና ነው፡፡ ነገር ግን ከላይ የመለሳችኋቸው ሁሉ ትክክለኛ መልሶች ቢሆኑም እኔ ልል የፈለግሁትን ግን አላገኛችሁትም፡፡ "እሺ ከእነዚህ ውጪ ምን ልዩ የሆነ መልስ ሊኖር ይችላል? ብላችሁ ጽምፃችሁን አሰምታችሁ ልትናገሩኝና የእኔንም መልስ ጆሮአችሁን አቀቅራችሁ ልትጠባበቁኝ ትችላላችሁ፡፡