Monday, October 21, 2013

ጌታችን የእግዚአብሔር ምሥጢር የመባሉ ምክንያት



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

ቀን 11/02/2006
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለልደቱ ጥንት ለሕይወቱ ፍጻሜ የሌለው አልፋና ኦሜጋ ነው፡፡ በሥጋ ከመገለጡ በፊት ቅዱስ ዮሐንስበዓለምም ነበር ዓለሙ አላወቀውም ነበርእንዲል በዓለሙ ሙሉ ሆኖ የሚኖር እግዚአብሔር ነው፡፡ አንዳንዶች በዓለም ነበር ሲባሉ ለምድር መነሻ እንዳላት ለእርሱም መነሻ አለው እንዳይሉ  ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊውብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበርብሎ አስቀድሞ ጻፈልን፡፡
 በዓለም ነበር ሲልም ዓለምን ፈጥሮ የሚገዛት እርሱ መሆኑን ያስረዳናል፡፡ ነገር ግን በሥጋ ማርያም አስኪገለጥ ድረስ ዓለም አላወቀችውም ነበር፡፡ አይደለንም እኛ መላእክት እንኳ አላዩትም፤ ነገር ግን ለእነርሱ በሰው አምሳያ ይታያቸው ነበረ፡፡ እነርሱም ለእርሱ አምልኮትን በአምሳያው ፊት ይፈጽሙ ነበር፡፡ እርሱ በሰው አምሳል ለመላእክት ተገልጦ ይታያቸው ነበር እንጂ በፍጹም እርሱነቱ ያልተገለጠ ማንም በማይቀርበው መለኮታዊ ብርሃን ውስጥ የሚኖረው ፈጣሪ ነው፡፡ እርሱ ስሙ እውነተኛ ብርሃን የሆነ እኛን ለማዳን ወደ ዓለም መጣ፡፡ ያም ማለት ሰው ሆነ፤ ለእርሱ አንድ ነገርን ለማድረግ መውጣት መውረድ የሚገባው አይደለም፤ ነገር ግን ሰው መሆኑን እንድንረዳ “ወደ ዓለም ይመጣ ነበር” ተብሎ ተጻፈልን፡፡

በክርስትና ያለ እምነት እስከዚህ ድረስ ይረቃል


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
11/02/2006
 ክርስቲያን በክርስቶስ እንደሞተ ሊያምን ሕይወቱም ከክርስቶስ ጋር እንደተሰወረ ወይም ሕይወቱ ከሕያዋን ቅዱሳን ጋር አንድ እንደሆነ ሊያምን ይገባዋል፡፡ በክርስቶስ ያለው ሕያውነት በፈቃድ በሚሆን ሞት ማለትም ጥምቀት የመጣ ነው፡፡ በፈቃዳችን በእምነት ከክርስቶስ ጋር ሞተን የትንሣኤውም ተካፋይ በመሆን በክርስቶስ ሕያዋን ሆነን እንኖራለን፡፡ አሁን ያለን ሕይወት ከሕያዋን ጋር አንድ የሚያደረገን ሕይወት ነው፡፡ በሥጋ ሞት ሞትንም አልሞትንም በክርስቶስ በተነሣነው ትንሣኤ ሁሌም ለዘለዓለም ሕያዋን ሆነን እንኖራለን፡፡ ስለዚህ ለአንድ ክርስቲያን የሥጋ ሞት ከሕያዋን ጋር የሚያቆራርጠው ወይም እነርሱ በሥጋ ስለተለዩት ከእርሱ የሚለዩት አይደለም ይልቅ በክርስቶስ አንድ ቤተሰብ በመሆን የአንድ የእግዚአብሔር ልጆች ሆነው የሚኖሩበት ነው፡፡ ይህ በክርስቶስ ሞቼ ከክርስቶስ ጋር ተነሥቼለሁ አሁን ያለሁት ቅዱሳን በከተሙበት በሰማያዊ ሥፍራ ነው፡፡ እንዲያም ቢሆን በሥጋ ስላልሞትሁ በዚህ በሰማያዊ ሥፍራ ሆኜም ውጊያ አለብኝ በውጊያዬ ደግሞ ሰማያዊያን መላእክት እንደሚራዱኝ እንዲሁ በሰማያዊ ሥፍራ ፍጹም ዕረፍትን ያገኙ ቅዱሳን የእግዚአብሔርና የክርስቶስ ካህናት ሆነዋልና እድን ዘንድ በጸሎታቸው ይራዱኛል የሚለው እምነት ከክርስቶስ ጋር ሞቼ በትንሣኤው ሕይወት ሕያው ሆኜ እኖራለሁ ብሎ ማመንን በብርቱ የሚጠይቅ እምነት ነው፡፡

Wednesday, October 16, 2013

ምንኩስናና ትዳር የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች


05/02/2006
በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ


ክርስትና ለሰይጣን ይገዛ ከነበረ ዓለም ወጥቶ እርሱ የጽድቅ ጸሐይ የሆነው ክርስቶስ ብርሃን ሆኖት በቀን እንጂ በጨለማ የማንመላለስበት የቀን ልጅ ተሁኖ የሚኖርበት ሕይወት ነው፡፡ ክርስትና ከክርስቶስ ጋር ተሰቅለን ነፍስ በምትሰጠው ሕይወት ሳይሆን ለዘለዓለም አባ አባ ብለን የምንጠራበትን መንፈስ በሰጠን በመንፈስ ቅዱስ ሕያዋን ሆነን የምንኖርበት ሕይወት ነው፡፡ ስለዚህም ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር ራሳችንን ለጽድቅ ሥራ ያጨን ደናግላን ነን፡፡ አገባንም አላገባንም ለክርስቶስ የታጨን በመሆናችን ደናግላን ነን፡፡ ይህ ድንግልና የሚጠፋው ክርስቶስን ክደን በሰይጣን ሕያዋን ሆነን የኖርን ሰዓት ነው፡፡ቢሆንም ግን ይህም ቢሆን በንሥሐ የሚታደስ ድንግልና ነው፡፡ ጌታ ጠፍተን እንድንቀር የማይወድ ከኃጢአታችን ይልቅ መጥፋታችን የሚያሳዝነው በንስሐ በተመለስን ጊዜም በደስታ እጆቹን ዘርግቶ በፍቅር የሚቀበለን አምላክ ነው፡፡