Saturday, January 26, 2019

ቅዱስ ኤፍሬምና የትሕርምት ሕይወቱ




 መ/ር ሽመልስ መርጊያ
ቀን 18/05/2011 ዓ.ም 

ቅዱስ ኤፍሬም እውነተኛ ክርስቲያን ከሆኑ ቤተሰብ ስለ ተወለደ እነርሱም በትሕርምት ሕይወት ውስጥ እንዲያልፍ መሠረት ስለጣሉለት ሕይወቱ እንደ መጥምቁ ዮሐንስ በንጽሕናና በቅድስና ያጌጠ ነበር፡፡ እርሱም ስለ  ስለዚህ ሕይወቱ ሲጽፍልን፡-
ከልጅነቴ እስከ እርግናዬ ዘመን ጌታዬ ሆይ ያንተን ቀንበር በደስታ ተሸከምኹ ይህንንም ሥራዬ አድርጌ በየቀኑ ያለ መሰልቸት ፈጸምኹብሎአል፡፡
ሰውነቱንም በጾም እንዴት ይጎስማት እንደ ነበረ ሲናገርም እንዲህ ይላል፡-

ተፈጥሮዬ ምግብን ብትጠይቀኝም ዘወትር በርሃብ እጎስማታለሁ፡፡ ምክንያቱም ለጸዋሚያን ለተዘጋጀው ተድላ ደስታ የተገባሁ እሆን ዘንድ" ሲል
ከውኃ መጠማትንም አስመልክቶ፡-
"ይህች ምድራዊ አካሌ ጥሜን እንድቆርጥ በእጅጉ ታስገድደኛለች፡፡ ነገር ግን ከገነት በሚፈልቀው ብርሃን ደስ ትሰኝ ዘንድ እንደ ተጠማች ደረቅ ሆና እንድትቆይ አደርጋታለሁ"
በሕይወት ዘመኑ ሙሉ እንዲህ ሰውነቱን በጾም እየቀጣ ይኖር ስለ ነበረ በእርሱ ሕይወት ዙሪያ የጻፈ ጸሐፊ እንዲህ ብሎአል፡-
"ደረቅ የሆነ ቂጣና በቀን አንዴ አንዳንዴ አትክልት ይመገባል እንጂ እንደ ሰዉ ምግብ አይመገብም ነበር፡፡ ከውኃ በቀር ምንም ዓይነት መጠጥ አይጠጣም፡፡ ሸክላ ሠሪ እንደሚሠራው ዕቃ ሆኖ ቆዳው ከአጥንቱ ጋር የተጣበቀ ነበር፡፡ ልብሱ ብዙ ዓይነት ጨርቆች የተደራረቱበትና ከልብሱ ላይ የተጣበቀው የምድር ትቢያ ጭቃ ሠርቶ አንዱ አንዱ ላይ ተነባብሮ ይታይ ነበር፡፡ ቁመናው አጭር ሲሆን ፊቱ ሁል ጊዜ የማይፈታ እንዳዘነ የሚኖር አባት ነበር፡፡ በአጋጣሚ እንኳ ስቆ አየሁት የሚል የለም:: ራሰ በርሃና ጽሕም የለውም ነበር፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም ጽኑ በሆነ የትሕርምት ሕይወት ውስጥ የሚኖር አባት ቢሆንም ከመንጋው ራሱን ሳይለይ በንጽቢንና በኋላም በኤዲሳ(ዑር) ባሉ ትምህርት ቤቶች ያስተምር እና ለሴት ዘማርያንም ድርሰቶችን በመድረስ መዝሙር ያስጠና ነበር፡፡
የተመስጦ ሕይወቱንም አስመልክቶ እንዲህ በማለትም ይገልጽልናል፡-
"በየእለቱ ከአምላኬ ጋር የማወጋው ነገር አለኝና ያለማቋረጥ ከቀን ውስጥ ሰርቄ ከልጅነት እስከ እርግናዬ ድረስ በተመስጦ ኖርኹይለናል፡፡
 
ቅዱስ ኤፍሬም እንደ ሌባ ድንገት የሚመጣውን ሞት እያሰበ ሁል ጊዜ በትጋት ለአምላኩ በመገዛት ይመላለስ ነበር፡- ይህንንም አስመልክቶ፡-
ጠዋት ሲነጋ በቀጣዩ ሌሊት ልሞት እችላለሁ ብዬ አስባለሁ፡፡ ስለዚሀ እንደ አንድ የሞት ፍርዱን እንደሚጠባበቅ ሰው ቀኑን ሙሉ አምላኬን ስዘክርና ሳመልከው አሳልፋለሁ፡፡
ሲመሽም ነገን ላያት አልችልም ብዬ በሕሊናዬ አስብና ጎህ እስኪቀድ ድረስ በፍጹም ልቤ በጸሎት ከአምላኬ ጋር ስነጋገር አድር ነበር" ይላል፡፡
ራሱንም በቤተ ክርስቲያን መስሎም፡-
ሰውነቴን የክርስቶስ ቤተክርቲያን መሆኗን እያሰብኹ በሰውነቴ ቤተ ክርስቲያን መዓዛው መልካም እንደሆነ የዕጣን መዓዛ የሰውነት ሕዋሳቶቼን ለአምላኬ አቀርባለሁ፡፡ ስለ እርሱ የማስባትን ሐሳቤንም መሠዊያ በማድረግ ራሴን ነውር እንደሌለበት በግ መሥዋዕት አድርጌ በፊቱ አቀርብ ነበር" ይላል፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም እንደ ሰው ሰውነቱን በውኃ አዘውትሮ መታጠብንም አይፈቅድም ነበር፡፡ ነገር ግን በነፍሱ ሁል ጊዜ ጌታ በመስቀል ላይ ሳለ ከጎኑ ባፈሰሰው ቅዱስ ውኃ መታጠቡንና ንጹሕ እንዳደረገው ማሰብን ይመርጥ ነበር፡፡ እንዲህም ስለሆነ -
ሰውነቴን በውኃ አዘውትሬ መታጠብን አልፈቅድም፡፡ ምክንያቱም ጌታዬ በመስቀል ላይ ሳለ በጎኑ ባፈሰሰው ውኃ አጥቦ ንጹሕ አድርጎኛልና፡፡ይላል፡፡
ቅዱስ ቁርባንንም ቅዱስ አፍሬም በእሳት መስሎ ያስተምራል፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም ሁለት እሳቶች እንዳሉ ጽፎልን እናገኛለን፡፡ ለቅዱሱ ቅዱስ ቁርባን ማለት የኃጢአት አረምን ከሰውነቱ አቃጥሎ የሚያጠፋ መለኮታዊ እሳት ነው፡፡ ኃጢአትንም በእሳት መስሎ ያስተምራል፡፡ ይህችም እሳት የምታጠፋ እሳት ናት፡፡ ከዚህች ከምታጠፋ እሳት መለኮታዊ እሳት የሆነው ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ እንደሚታደገን እንዲህ ይላል፡-
"ከመለኮታዊው እሳት ከቅዱስ ቁርባን በተቀበልኩ ጊዜአት ሁሉ የእኔ ጸሎት በሰውነቴ ሕዋሳት ውስጥ በቅለው ያሉትን የኃጢአት አረሞች አቃጥሎ ያጠፋልኝ ዘንድ ነበር፡፡ ወንድሞቼ ሆይ!! በሰውነቴ ሕዋሳት ውስጥ ያለውን የኃጢአት እሳት በአምላክ ክቡር ደም አጠፋሁት፡፡ ይህ የጌታዬ ክቡር ደም ሰውነቴን የኃጢአት እሳት እንዳያጠፋት ጠበቀው፡፡
ጨምሮም፡-
ከመሠዊያው(ከታቦቱ) የምቀበለው የጌታችን ክቡር ሥጋ ሰውነቴን ሰይጣን ከሚያመጣብኝ ክፋት ሁሉ ይጠብቀዋል፡፡"
በሌሊትም የሰይጣን ጾር ስለሚበረታ ሰይጣንንና ፈቃዱን ለማራቅ ሲል ቅዱስ ኤፍሬም መላ ሰውነቱንና አካባቢውን ሁሉ በትምርተ መስቀል ያማትብ ነበር፡፡ እንዲህ ስለማድረጉም፡-
 
"
በሌሊት ወደ እኔ በመቅረብ ንጽሕናዬን ገፎ እንዳይጥለው በሕዋሳቶቼ ሁሉ ላይ ሦስቱን የሥላሴን ስሞች እየጠራሁ በጌታዬ በመድኀኒቴ በኢየሱስ ትምርተ መስቀል አማትብባቸዋለሁ፡፡ ጌታዬ ሆይ ክብር ላንተ ይሁን የሥላሴ የስሙ ኃይልና ብርታት እንዴት ታላቅ ነው! አንተ በእርግናዬ ብርታት ሆንኸኝ፡፡ በዕድሜ ሁሉ ጽኑ ግንብ ሆንኸኝ፡፡" ብሎአል፡፡
የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ክብሩ ሁሌም ከፍ ከፍ ይበል ቅዱስ ኤፍሬም ስለ እኛ መዳን በመስቀል ላይ በተሠዋው በጌታችን ፍቅር የታሠረ ቅዱስ ነበር በሕሊናው መስቀሉን ሥሎ እርሱን በመዘከር ይኖር ነበር፡-
"በጾምና በትግሃ ሌሊት ጌታዬ ሆይ ገጽታዬ ወደ አረንጓዴነት እስኪቀየር ድረስ አንተን ስናፍቅ አድራለሁ፡፡ እንዲህም ማድረጌ ነቢዩ ሙሴ ክብርህን ለማየት እንደበቃ እኔም ክብርህን በትንሣኤ አይ ዘንድ በመናፈቄ ነው፡፡ ጌታዬ ሆይ ዕርቃንህን ሆነህ በመስቀል ላይ ተሰቅለህ አየሁ፡፡ ስለዚህ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ የአንተን መምጣት በመጠባበቅ ማቅ ለብሼ መኖርን መረጥሁ፡፡

ጨምሮም ቅዱስ ኤፍሬም እንዲህ ይለናል፡-
"ሰማያዊው ሙሽራ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በፊቴ በሰማያት የምለብሰውን የሰርግ ልብስ አይቼ መብልን መብላትን ውኃም መጠጣትን ዘነጋሁይላል፡፡

 
ይህን ካነበብኩ በኋላ ደረቴን እየደቃሁ አነባው ወየው ለእኔ ወየው ለእኔ …