Monday, August 31, 2015

የተመሰገነችው ድህነት በቅዱስ ኤፍሬም


ትርጉም ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
25/12/2007

ቅዱስ ጳውሎስ "ኑሮዬ ይበቃኛል ለሚለው ግን እግዚአብሔርን መምሰል እጅግ ማትረፊያ ነው፤ ወደ ዓለም ምንም እንኳ አላመጣንምና፥አንዳችንም ልንወስድ አይቻለንም፤ ምግብና ልብስ ከኖረን ግን፥ እርሱ ይበቃናል።"(1ጢሞ.6:6-8) እንዳለው ክርስቶስን በመሰለና ለራስ በቂ በሆነ ሕይወት ውስጥ በመገኘት ናት በቅዱስ ኤፍሬም የተወደደችው ድህነት።
 ይህቺ ድህነት ሙሉ ትኩረትን እግዚአብሔርን ለመምሰል በሚረዱ ተግባራት መኖርን ትጠይቃለች።ይህ ነው ለቅዱስ ኤፍሬም ድህነት የሚለው ቃል ትርጉሙ።  ድህነት የሥጋ ድህነት ማለት አይደለም ለቅዱስ ኤፍሬም ይህ እንዳልሆነ እርሱ ራሱ በቃሉ  "ለሥራ ከመትጋት አትለግም ምንም እንኳ ባለጠጋ ብትሆን፥ ሰነፍ ሰው በሥራ ፈትነቱ  የተነሣ ቁጥሩ የበዛ ኃጢአትን ይፈጽማታልና" ብሎ ይመክራል። ስለዚህ ድህነት ማለት ለቅዱስ ኤፍሬም እንዲህ ከሆነ ድህነት ሳይሆን ድኅነት ነው።

Tuesday, July 14, 2015

እድሜ ይስጥልኝ ብያለሁ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

07/11/2007

እንደ መንፈሳዊ መረዳት ድንቅ የሚለኝና የሥነ ተፈጥሮአችን አንዱና መሠረታዊ ክፍል  ስለሆነው ነገር ልንግራችሁ። ከእናት ማኅጸን ሥጋችን ከነፍሳችን ጋር ተዋሕዳ ከተፈጠረችበት ጊዜ አንስቶ ወደ እርጅናና ሞት ስታዘግም ነፍሳችን ግን እለት እለት እየታደስችና በእውቀት ሙሉ እየሆነች በመምጣት ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው እርሷ በእግዚአብር ዘንድ  እንደታወቀች እስክታውቅ ድረስ ደርሳ ፍጹም ወደ መሆን ታድጋለች። የዛኔ እግዚአብሔር አምላኩዋን አባ አባ ስትለው በፍጹም ልጅነት መንፈስ ሆና ነው። እንዲህ በመሰለ መንፈሳዊ ከፍታ እያደገ የሚመጣው ግን ሰሎሞን "ጥበብ" ያለው  ሲወድቅም ሲነሣ ያልራቀው  የእግዚአብሔር መንፈስ ከእርሱም ጋር የሆነለት ሰው ብቻ  ነው። 

Friday, July 10, 2015

ክርስቶስ የማይታየው አምላክ ምሳሌ የመባሉ ምክንያት



በዲ/ን   ሽመልስ መርጊያ
3/10/2007
ሕዝቅኤል እግዚአብሔር ለእርሱ እንዴት እንደተገለጠለት ሲናገር እንዲህ ብሎ ነበር "በራሳቸውም ላይ ካለው ጠፈር በላይ ድምፅ ተሰማ፤ ሲቆሙም ክንፎቻቸውን ዝቅ ያደርጉ ነበር።  በራሳቸውም በላይ ካለው ጠፈር በላይ የሰንፔር ድንጋይ የሚመስል የዙፋን አምሳያ ነበረ፤ በዙፋኑም አምሳያ ላይ እንደ ሰው መልክ አምሳያ ነበረ። ከወገቡም አምሳያ ወደ ላይ የሚብለጨለጭ የወርቅ ምስያ አየሁ፤ ከወገቡም አምሳያ ወደ ታች እንደ እሳት ምስያ አየሁ፤ በዙሪያውም ፀዳል ነበረ። በዝናብ ቀን በደመና ውስጥ እንደ ቀስተ ደመና አምሳያ፥ እንዲሁ በዙሪያው ያለ ፀዳል አምሳያ ነበረ። የእግዚአብሔር ክብር ምሳሌ መልክ ይህ ነበረ። ባየሁም ጊዜ በግምባሬ ተደፋሁ፥ የሚናገርንም ድምፅ ሰማሁ።"(ሕዝ.1:26-28)

Monday, July 6, 2015

የዘፍ.1፡1-4 ልዩ ምልከታ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
29/10/2007

ተወዳጆች ሆይ ሌላም ግሩም የሆነውን በቅዱሳን አባቶች ዘንድ ያለውን ትርጓሜ  ልንገራችሁ፡፡ አባቶች ዘፍ.1፡1-4 ያለው ነቢዩ ሙሴ  ስለክርስትና በምሥጢር የተናገረባት ነው ብለው ይተረጉሙታል፡፡ “ቀንም ሆነ ሌሊትም ሆነ አንድ ቀን” የሚለውም ስምንተኛዋ ቀን ናት ይሏታል፡፡ ይህቺ ቀን ፀሐይና ጨረቃ እንዲሁም ከዋክብት ለምድር ብርሃንን ከመስጠታቸው በፊት የነበረች ቀን ነች፡፡
በእርግጥ እንዲህ ሲሉ አንዳች መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት ሳይዙ አይደለም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይለናል “ በክርስቶስ ፊት የእግዚአብሔርን የክብሩን ብርሃን እንዲሰጥ በልባችን ውስጥ የበራ ፡- በጨለማ ብርሃን ይብራ ያለ እግዚአብሔር ነውና” (2ቆሮ.4፡6፤ዘፍ.1፡3) ይለናል።

Tuesday, May 5, 2015

ወገኖቼ አንድ እውነት ልንገራችሁ



ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

27/08/2007

 እውነቱም ይህ ነው፡- ደስታና እረፍት አይደለም በምድራዊ ሕይወታችን ውስጥ ይቅርና በመንፈሳዊው ምልልሳችን እንኳ ሁሌ የምናገኘው አይደለም፡፡ በምድር የምናጣጥማቸው ደስታና እረፍት መገኛቸው ከእግዚአብሔር ስጦታዎች እንጂ ከሌላ ከምንም አናገኛቸውም። ቢሆንም እነዚህ የሚታወኩበት ጊዜ ስለሚመጣ ያኔ ደስታህና እረፍትህ ለጊዜውም ቢሆን ሊወሰዱብህ ይችላሉ፡፡ እንዲህም ቢሆን ተፈጥሮውያኑ የእግዚአብሔር ስጦታዎች እየተጤኑ ካልሆኑ በቀር ከወይኒ ቤትም በላይ የከፉ የስቃይ እስር ቤት ሊሆኑብህ ይችላሉ፡፡
ስለዚህ ወገኔ በእነዚህ የእግዚአብሔር ስጦታዎች ሙሉ ለሙሉ ባይሆን እንኳ የደስታህና የእረፍትህ እርሾ ከአንተ ፈጽሞ እንዳይወሰድ ከፈለግህ አስቀድመህ ይሉንታን ከራስህ አርቅ ፡፡ ይሉንታ የደስታንና የእረፍትን እርሾ ፈጽሞ ከሰውነትህ የሚያስወግድና በምትኩ የማይጠፋ የቁጭት ፍም አኑሮ የሚያልፍ ነው፡፡ ስለዚህ ወዳጄ ሕሊናህ የሚልህን ስማው ፤ ሕሊና የአንተን ደስታና እረፍት ጠንቅቆ የሚያውቅና የቁጭት ፍምን ከአንተ የሚያርቅ መለኪያህ ነው፡፡
 ወዳጄ እንደ ምሳሌ እናንሣ ብንል እንኳ ተፈጥሮአውያን ስጦታዎች ከሆኑት መካከል አንዱና ዋነኛው ፆታዊ ፍቅር ነው።
  ወገኔ ሆይ ትዳር መልካም ነው፤ ነገር ግን ለትዳር ጓደኝነት ከውጫዊ ቁሳቁሶች በፊት ፍቅርን አስቀድም፡፡ ከዚያ በኋላ በትዳርህ ደስታና እረፍትን ታገኛለህ፡፡ 

Wednesday, April 8, 2015

የጌቴሴማኒው ጸሎት (ቅዱስ ኤፍሬም)



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
30/07/2007

“ነፍሴ እስከሞት ድረስ እጅግ አዘነች” አለ የክብር ጌታ የሆነው ጌታችን፡፡ የተሰማውን እንዲህ ብሎ በግልጥ በመናገሩ የክብር ጌታ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አላፈረም፡፡ ለማስመሰልም ብሎ አይደለም፤ በእውነት ነፍሱ እስከሞት ድረስ አጅግ ስላዘነች እንጂ፡፡ ምክንያቱም በእውነት የእኛን ደካማ የሆነ ሥጋችንን በመልበሱና የሥጋን መከራ ከምትካፈለው ነፍሳችን ጋር አንድ በመሆኑ ነው እንጂ፡፡ እርሱ የተናገረው በሙሉ እውነት ነው፤ እንደ አስመሳይ የሰወረን አንዳች ነገር የለም፡፡ በዚህም አንድ አማኝ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ራሱን እንዳያስታብይና እውነትን እንዳይሰወራት ጌታችን በተግባር አብነት ሆኖት እናገኘዋለን፡፡

Wednesday, March 25, 2015

አንድ ዓለሙን ስላሸበረውና ብዙዎች ብዙ ስላሉለት የካቶሊክ ተረት ልንገራችሁ

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

16/07/2007

ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን  በትርጓሜ አስታካ አንድ ተረት ጽፋ ዓለሙን እያመሰችው ትገኛለች፡፡ ይህን ትርጓሜ ይዘው ያልሆኑትን ሆነናል በማለት ደማችን የተቀዳው ከመላእክት ወገን ከሆኑት በድሮ ጊዜ ኃያላን ከተባሉት ኔፊሊም ወገን ነው የሚሉ ወገኖች ተነሥተዋል ፡፡ 
እነርሱም በአሁኑ ጊዜ ብዙ የሚባልላቸው ራሳቸውን ብሩሃነ አእምሮ የሚሉት ኢሉሚናቴዎች  ናቸው፡፡ የሚደንቀው ግን ይህ ልብ ወለድ እውነት መስሎአቸው የታወኩ ከእኛም ወገን አልጠፉም፡፡ የጸናው መሰረቱን ሳይለቅ ንፋስ እንደሚያላጋው ሸንበቆ በአፍጢሙ እየተደፋ አፈር ልሶ ሲነሣ ሌላ ጊዜ ደግሞ  የእንግልል ከመሬቱ እየተጣጋ መልሶ እየተነሣ ሲቆም እያየን ነው፡፡ ያልጸናው ግን ነፋሱ እንዳነፈሰው ሲነፍስና ከዚያም እልፍ ሲል የነፋሱ አገልጋይ በመሆን በሌሎች ዓይን ላይ አዋራውን እየሞጀረና እያሳወረ ይገኛል፡፡ ባናስተውለው ነው እንጂ ይህ እኔ ክርስቶስ ነኝ ብሎ የሚመጣው ሃሳዊው መሲህ ሰዎችን ሆን ብሎ ለማጥመድ የዘየደው ዘዴ መሆንኑ ማንም በቀላሉ የሚረዳው ነው፡፡ 
እንዴት በሉኝ? መጽሐፍ ቅዱስ አንድም ቦታ ላይ እኔ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ የሚነሣው ተቃዋሚው እኔ ሰይጣን ነኝ እኔን አምልኩኝ እያለ እንደሚመጣ ተጽፎልን አናገኝም፡፡ እርሱም ሆነ ነቢያቱ የሚነሡት በክርስቶስ ስም ነው፡፡ ሲነሡም ራሳቸውን የጽድቅ አገልጋዮች በማድረግ እንጂ የሰይጣን አገልጋዮች ነን በማለት አይደለም፡፡

Tuesday, March 24, 2015

ተወዳጆች ሆይ ጦሙ እንዴት ይዙአችኋል?

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
15/07/2007

መቼም ጦምን ከጸሎት ጋር አስተባብሮ የያዘና ራሱን በእግዚአብሔር ፊት አቁሞ ስለ መተላለፉ በአምላኩ ፊት የሚያነባ ክርስቲያን የንስሐ እንባው የኃጢአት እድፉን ጠርጎ ስለሚያስወግድለት በሰዎች ላይ የማይፈርድ፥ እንደ ግብዝ ጦመኞች ልታይ ልታይ ማለት የሌለበት፥ ለሰው ልጅ ያለው ፍቅር የበዛለት፥ አንደበቱም ይሁን ልቡ ከጸሎትና ከልመና እንዲሁም ከምልጃ የማያርፍ ፥ ቃሉን ማንበብ የሚወድ፥ በቃሉ መመሰጥ የሆነለት፥ የራሱን እንጂ የሰዎችን ነውር ለማየት የማይፈቅድ፥ ስለራሱ ኃጢአት በአምላኩ ፊት በመንፈስ ሆኖ የሰማይን ፊት እንኳ ለማየት የማልበቃ ኃጢአተኛ ነኝ እያለ ደረቱን የሚደቃ ሰው መሆንን ገንዘቡ እንደሚያደርግ ሳይታለም የተፈታ ጉዳይ ነው። 

Monday, March 23, 2015

ቀጣይ መዝ.89 እንደ ቅዱስ ጀሮም

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 

14/07/2007

“የዘመኖቻችን እድሜ ሰባ ዓመት ነው…” አለን…. ግፋ ቢል ሰማንያ ብሎ ጨመረበት  ከሰማንያ ዓመት በላይ ብንኖር ግን ሕይወታችን ሕይወት ተብሎ የሚቆጠር አይሆንም፡፡ እንዲያም ቢሆን በጤና ሰማንያ ብንደርስ እድለኞች ነን፡፡ ከስምንት ዐሥር ዓመታት በኋላ ማን ነው ጤናማ ሆኖ የሚቀጥል?  ግሪካዊያን አንድ አባባል አላቸው፡- “እርጅና በራሱ አንድ የሕመም ዓይነት ነው” ይላሉ። ከሰማንያ ቢበዛ ግን ዳዊት “ድካምና መከራ ነው” እንዳለው ሃዘን ነው፡፡ 
እሰካሁን ድረስ ግን የመዝሙሩን ቀጥተኛ የሆነውን ትርጉም ነው የተመለከትነው፡፡ አሁን ደግሞ የቃሉን ምሥጢር እንመለከተው፡፡ ቢሆንም ሁሉን አንድ በአንድ አንመለከተውም እንዲያ ቢሆን ግን ጊዜ ባልበቃን ነበር፡፡ ስለዚህ ሌሎችን አልፈን ለምን የዘመናችን እድሜ ሰባ ዓመት ነው” አለ የሚለውን መንፈሳዊ ምስጢር ወይም መንፈሳዊ መልእክቱን ማየት እንጀምር፡፡ 
“የዘመናችን እድሜ ሰባ ዓመት ነው” አለ፡፡ ሰባ ቁጥር በሦስት እጥፍ አሥር ዓመታት ላይ አንድ ዐሥር ዓመት ያክላል፡፡ ዐራት እጥፍ ዐሥር ዓመታት ማለት ሰማንያ ዓመት ነው፡፡ ስለዚህ ቃሉ በሰባትና በስምንት ቁጥሮች ላይ ትኩረት መስጠቱን እንመለከታለን። እንዲሁ “አንተ ለትውልድ ሁሉ መጠጊያ ሆንህልን፡፡" ብሎ ትውልድ ያለው ብሉዩንና ሐዲስ ኪዳንን መሆኑን አስቀድመን እንዳስተማረንም ልብ በሉ፡፡ ልጁ ጠቢቡ ሰሎሞን  በመክበቡ “እንጀራህን በውኃ ፊት ጣለው ከብዙ ቀን በኋላ ታገኘዋለህ፡፡

መዝ.89 እንደ ቅዱስ ጀሮም ቀጣይ ክፍል


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

12/07/2007

አሁን ወደ መዝሙሩ ቃል እንመለስ፡- የእኛ የሕይወት ዘመን ለምሳሌ የሁላችን አባት የሆነው አዳም 930 ኖሮ ሞተ፡፡ ማቱሳላ ደግሞ 969 ዓመታት በሕይወት ቆይቶ ሞተ፡፡ እኚህ አባቶች አንድ ሺህ ዓመት ኖሩ ብንል እንኳ ለእኛ ከተሰጠን ዘለዓለማዊነት ጋር ሲነጻጸር እጅግ ኢምንት ነው፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ፍጻሜ ያለው ነገር እንዴት ታላቅ ሊባል ይችላል? ኃጢአትን ሳንፈጽም እንድንኖር የተሰጠን 1000 ዓመት በአንተ ዘንድ እንደ አንዲት ቀን ነበረች፡፡  እንደ አንዲት ቀን ብቻ አለን? እንደ ሌሊት ትጋት ናት ብሎ ይበልጥ ኢምነት አደረጋት እንጂ፡፡ ስለሆነም ጌታችን ሆይ በአንተ ዘንድ ዘመኖቻችን የተናቁ ናቸው!! ስለዚህ ጌታ ሆይ ወደ አንተ እናጋጥጣለን፤ ሰውን ወደ ኅሳር አትመልሰው እንልሃለን፤ ጌታ ሆይ እኛን ለማዳን ወደ ምድር መምጣትህን፣  ደምህንም ስለእኛ መዳን ማፍሰስህን አስብ፡፡ ጌታ ሆይ አንተ ራስህ  “እኔ ከምድር ከፍ ከፍ ያልሁ እንደሆነ ሁሉን ወደ እኔ እስባለሁ”(ዮሐ.12፡32) ብለኸናልና  ጌታ ሆይ ! ራስህን ከፍ ከፍ አድርገህ እኛን ወዳንተ ሳብኸን እንጂ ወደ ላይ እንወጣጣ ዘንድ እኛ ወደ አንተ አልቀረብንምና አቤቱ ይህን አስብ፡፡

Monday, March 16, 2015

ክርስትና

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 

06/07/2007

ክርስትና ሰው ሆነን የተፈጠርንበትን ድንቅና ግሩም የሆነውን እግዚአብሔርን የምንመስልበት አቅምን የሚሰጠን መንፈስ ቅዱስን በኃጢአታችን ምክንያት አጥተን ስንባዝን ለነበርነው ክርስቶስ በመስቀሉ ዳግም የሰጠን እውቀት ሳይሆን ሕይወት ነው። ሲጠቃለል ክርስትና ማለት ሰው መሆን ማለት ነው። ሰውን ሰው የሚያሰኙት ተፈጥሮውና ተግባሩ ናቸው። ተፈጥሮው ሲባል ሰው ግሩምና ድንቅ የሆነውን እግዚአብሔርን የሚመስልበት አቅሙን ማለታችን ነው። እግዚአብሔርን የሚመስልበት አቅሙን ግን ወደ ተግባር መልሶ ይሠራበት ዘንድ ግን መምህር የሚሆነው መንፈስ ቅዱስ በውስጡ ያድርበት ዘንድ ግድ ነውና ጌታችን አዳምን ከምድር አፈር ካበጀው በኋላ የሕይወት እስትንፋስን በአፍንጫው እፍ በማለት ሰውነቱን ምድርን በውበት ላስጌጣት መንፈስ ቅዱስ ማደሪያ አደረጋት። ሰው ለዚህ በውስጡ ላደረበት መንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ሲታዘዝ ሰው ተብሎ ወደ መጠራት ይመጣል። ሰው ከሆነ ደግሞ ክርስቲያን ሆነ ማለት ነው። ክርስትና እንግዲህ እንዲህ ናት ወሬ ሳትሆን ሕይወት ናት። ክርስትና ሰው በመሆን ሰው የመሆንን ትርጉም ያሳየንን ክርስቶስን መምሰልን የምትጠይቅ ናት። አቤቱ አምላኬ ሆይ እባክህ ግሩምና ድንቅ ወደሆነው ሰዋዊው ማንነቴ በቃል ሳይሆን በተግባር አድግ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ ለነፍሴ እውቀትና ሕይወት እንዲሁም ብርሃን ሆኖ አንተን እመስል ዘንድ እርዳኝ።  የቀደመውን ኃጢአቴን አታስብብኝ ከኃጢአት ፈቃድም ንጹሕ አድርገኝ። ልቡናዬን ለፍጥረት ሕይወት በሆነው ሕያው ቃልህ ሙላው ። አሜን ለዘለዓለም ይሁን ይደረግልኝ።

አራቱ ልደታት

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 

06/07/2007

የክርስቲያን አፈጣጠሩና እድገቱ እጅግ ግሩም ነው። ልደቱ ፍጥረታዊና መንፈሳዊ ብለን ለሁለት ከፍለናቸው ልንመለከታቸው ብንችልም ሁለትም ሦስትም  መንፈሳዊ ልደታት አሉት። ሁሉም ግን መሠረታዊያን ናቸው።
ሰው ከእናትና ከአባቱ አስቀድሞ ሳይፈጠር መንፈሳዊው ልደት ሊፈጸምለት አይችልም። ስለዚህ ፍቅር በሆነው አምላክ በሥጋ ሰው ሆኖ ሊፈጠር ይገባዋል። ይህ ልደት ግን በቂ ነው አይባልም። ሌላ አባ አባ የሚልበትን ልደት ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ በስመ ሥላሴ ሊወለድ ይገባዋል።
ይህም በራሱ ሙሉ አያደርገውምና አዲስ ለተፈጠረበት ተፈጥሮ ክርስቶስን ወደመምሰል ማደግ ይጠበቅበታል። ይህ ክርስቶስን የመምሰል ደረጃ ሦስተኛ ልደት ይባላል። ይህም ክርስቶስን በተግባር ወደ  መምሰል የመምጣት ሂደት ነው። ወደዚህ መንፈሳዊ ከፍታ  የደረሰ ሰው ላይ ክርስቶስ በእርሱ ይገለጣል።  ሰዎች ሁሉ የክርስቶስን መልክ በእርሱ ላይ ይመለከታሉ። ነገር ግን ደግሞ ሌላ አራተኛ ልደት ያስፈልገዋል። እርሱም በትንሣኤ ለድል አድራጊዎቹ ከክርስቶስ የሚሰጥ ልዩና ዘለዓለማዊ ስጦታ ነው። ክርስቶስ በትንሣኤ ሥጋችንን እንደ ራሱ ሥጋ አድርጎ በመለወጥ ልክ በደብረ ታቦር ወደ አሳየን ክብሩ በማሸጋገር የምንወለድበት ልደት ነው። ይህን ዓይነት ልደትን በምሳሌነት አስቀድሞ በሙሴ አሳይቶን ነበር። እውነተኛውን ልደት ግን በትንሣኤ የእርሱን ሥጋ እንዲመስል አድርጎ ሥጋችንን በመለወጥ ይሰጠናል። ይህን አስመልክቶ ጌታችን በቃሉ "እውነት እላችኋለሁ፥ እናንተስ የተከተላችሁኝ፥ በዳግመኛ ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በሚቀመጥበት ጊዜ፥ እናንተ ደግሞ በአሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገድ ስትፈርዱ በአሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ።"(ማቴ.19:28) ብሎናል። በእውነት እርሱ ለዚህ ክብር የፈጠረን ጌታ ፍቅር የሆነውን ሰውነቱን ለብሰን ለዘለዓለም ስናመሰግነው እንድኖር ያብቃን። ለዘለዓለም አሜን።

መዝሙር 89 በቅዱስ ጀሮም

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
06/07/2007

በመዝሙሩ መግቢያ ላይ የእግዚአብሔር ሰው የሙሴ ጸሎት የሚል ተጽፎ እናገኛለን፡፡  .....
“አቤቱ አንተ ለትውልድ ሁሉ መጠጊያ ሆነህልን” ብሎ መዝሙረኛው መዝሙሩን ይጀመራል፡፡ መጠጊያ የሚፈልግ ሰው ከሚግለበለብ እሳት ወይም ወላፈን ወይም ከክፉ አውሬ ወይም ነፍሱን ከሚፈላለጋት ጠላቱ ከሚታደገው ዘንድ ነው መጠጊያውን የሚያደርገው፡፡ እኛም እንዲሁ ከዚህ ዓለም የኃጢአት እሳትና ወላፈን ወይም ደግሞ እኛን ከሚያድነን  አውሬ ዲያብሎስ  ያደነን ዘንድ “የምትገዛልህን ነፍስ ለአራዊት አትስጣት የችግረኞችህን ነፍስ ለዘወትር አትርሳ”(መዝ.73፡19) እያልን ወደ መጠጊያችን እግዚአብሔር  ዘወትር እናንጋጥጣለን፡፡ ጠላቶቻችን በእኛ ላይ በርትተውብናልና በክንፎችህ ጥላ ሰውረን ብለን እንማጸነዋለን ምክንያቱም እርሱ መጠጊያችን ነውና፡፡