Showing posts with label ምልከታዎቼ. Show all posts
Showing posts with label ምልከታዎቼ. Show all posts

Thursday, May 7, 2020

አማልክት ከምድር ሲወጡ አየን


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
29/08/2012
አዲስ አበባ
አምላኬ ሆይ ዛሬ ለጸሎቴ መልስን ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ፡፡ አውቃለሁ አንተ ርኅሩኅ አምላክ ነህ እንደ ፈቃድህ የሆነን ጸሎት የሚያቀርብን ሰው ትሰማዋለህ፡፡ ነገር ግን ጌታ ሆይ ዛሬ ምሽቱን በምንጣፌ ላይ ዕንቅልፍ ሳይጥለኝ ግን ጋደም ብዬ ወደ መቃብር ሥጋህ መውረዱን አሰብሁ፡፡ ነፍስ ከሥጋ መቃብር ከገባች ፈጥና ትወጣለች እንጂ ከእርሱ ጋር ምድራዊው መቃብር ውስጥ አትገባም፡፡ እንዲያ ቢሆን ግን ሰው ከነሕይወቱ ተቀብሮአል ይባላል እንጂ ነፍስ ወደ መቃብር ወረደች አትባልም፡፡ እንዲያም ቢሆን ሥጋ በነፍስ ኃይል በምድር ልብ ውስጥ መተንፈስ አትችልምና ነፍስ ፈጥና ሥጋን ትለያታለች፡፡ ነፍስም በዝግ መቃብር ሥጋን ተለይታ በአዳም ላይ የተፈረደውን ፍርድ ተቀብላ ወደ ሲኦል ትወርዳለች፡፡ እንዲህ ስል ከክርስቶስ ትንሣኤ በፊት ያለውን ጊዜ መናገሬ ነው፡፡  ጌታችን ግን ነፍሱን ከሥጋው በፈቃዱ ከለያት በኋላ በነፍሱ ወደ ሲኦል ወረደ፡፡ በምድር በጠባብ ደረት በአጭር ቁመት ተወስኖ በግዘፍ ሥጋ ለፍጥረት ሁሉ እንደተገለጠ በነፍሱም ወደ ሲኦል በመውረድ በመጠነ ነፍስ በሲኦል ለነበሩ ነፍሳት ሁሉ ተገለጠ፡፡  “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ብሎ በጌትነቱ ታያቸው፤ ነፍሳት ሁሉ በእርሱ አርአያና አምሳል ተፈጥረዋልና ጌታቸውን ለዩት “ከመንፈስህ ጋራ ብለው” እንደ ዮሐንስ መጥምቅ በደስታ ሰገዱለት፡፡ እነርሱም በቀኝ በኩል ከተሰቀለው ወንበዴ ጋር ወደ ገነት ከጌታ ጋር ገቡ፡፡

Wednesday, December 11, 2019

ዳርዊን ቲዎሪውን ከየት አገኘው ?


በመ/ር ሽመልስ መርጊያ
ቀነን 01/04/2012


ወገኖቼ አንድ ነገር ልብ ብላችሁ አድምጡኝ፡፡ አንድ የካቶሊክ መነኩሴ ዳርዊን እርሱ የጻፈው ግልበጣ(ኩረጃ የራስ አስመስሎ ማቅረብ) መሆኑን ያስተዋለው ሰው ማን ነው? ከየት ብትሉኝ ከመጽሐፍ ቅዱስ ገልብጦ ብላችሁ ምን ትሉኛላችሁ? ግን እርሱ እግዚአብሔር በአርአያውና በአምሳሉ የፈጠረውን የሰው ልጅ ገልብጦ ዝንጀሮ አድርጎ ሴኩላር ቀለም ቀባው፡፡ እስቲ አስተውሉ፤ አዳምን የሠላሳ ዓመት ጎልማሳ ሔዋንን የዐሥራ አምስት ዓመት ኮረዳ አድርጎ የፈጠረ አምላክ ምድርና በውስጧ ያሉትን የቢልዮን ዓመታት ዕድሜ እንዲኖራቸው አድርጎ መፍጠር ይሳነዋል ብላችሁ ታስባላችሁን? እናም ወዳጆቼ ይህን ሐሳብ ከየት ስቦ እንዳመጣው ተገንዘቡ እርሱ መነኩሴ ነበር ማለት ስለመጽሐፍ ቅዱስ ጠንቅቆ ያውቃል ማለት ነው፡፡

Friday, February 22, 2019

ተዋሕዶ ኅትመት


 መ/ር ሽመልስ መርጊያ 

ቀን 14/06/2011 ዓ.ም

አምላክ በሕይወት ካቆየኝ አንድ በጎ እና ለቤተ ክርስቲያን ቅናቱ ያለው ሰው ይህን ሐሳብ ከግብ ሊያደርሰው ይችላል ብዬ በማመን  ይህን ሕልሜን ለአንባቢያን ላከፍለው ወደድሁ 
 ስያሜ፡- ተዋሕዶ ኅትመት
የስያሜው ምክንያት፡- ተዋሕዶ ማለት በሁለት አካላት መካከል የተደረገ ፍጹም የሆነ አንድነትን የሚገልጽ ቃል ሲሆን አንዱ አካል እና የአካሉ ባሕርይ የሌላኛውን አካልና ባሕርይ ሳያጠፋ፣ ሳይመጥ፣ ሳይቀይር፣ ሳይቀይጥ፣ ሳይለውጥ ነገር ግን አንዱ አካል ሌላኛውን አካል የራሱ አካልና ባሕርይ በማድረግ አንድ አካል አንድ ባሕርይ በመሆን የሚገለጡበትን ምሥጢር ለማስረዳት ቤተ ክርስቲያናችን በብቸኝነት የምትጠቀምበት ቃል ነው፡፡ ይህ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ሰው ሆኖ በመወለድ የገለጠው ምሥጢር ነው፡፡ እርሱ እግዚአብሔር ቃል ከአብ ጋር በመተካከል ሲኖር ሳለ ሰውን ለማዳን ሲል ከቅድስት ድንግል ማርያም በጽንሰት ሥርዓት ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍሷ ነፍስ በመንሳት ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው ሆኖ በአንድ አካልና በአንድ ባሕርይ ለፍጥረት ሁሉ ተገልጦአል፡፡ ይህን የእግዚአብሔር ቃል ሰው የመሆን ምሥጢር ቤተ ክርስቲያናችን ተዋሕዶ ትለዋለች፡፡ ይህንንም ቃል የራሷ መገለጫ ስም አድርጋም ትጠቀምበታለች፡፡ ይህንንም መጠሪያ ስሟ አድርጋ በመጠቀሟም ከሌሎች የክርስትና የእምነት ተቋማት ሁሉ ትለያለች፡፡  ስለዚህ ተዋሕዶ ስንል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማለት እንደሆነ ማንም በቀላሉ ይገነዘበዋል፡፡ ለዚህም ነው ወደፊት እግዚአብሔር ቢፈቅድ እንዲመሠረት ለምፈልገው የሕትመት ተቋም ተዋሕዶ ኅትመት የሚል ስያሜ መስጠቴ፡፡   

Wednesday, August 2, 2017

የነፍስ ወግ አምስተኛ ክፍል ስለ ሥነ ተፈጥሮዬ


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
27/11/2009

እግዚአብሔር እኔ ነፍስን ልክ እንደ አዳምና ሔዋን ከእኔ ጋር አንድ አድርጎ የፈጠራትን ግዙፏን ሥጋዬን እንድረዳት አድርጎ ፈጠረኝ። ስለዚህ አምላኬ እርሷን እንደሚያውቃት መጠን አይሁን እንጂ ሥጋዬን አውቃታለሁ፡፡ ምድርን በእርሷ ላይና ውስጥ ያሉትን እንደማጥናት እንዲሁ ግዙፋን ሥጋዬን በማጥናት ሁል ጊዜ አዳዲስ የሆኑ ነገሮችን ከእርሷ እያወቅሁ እኖራለው፡፡ ለዕውቀቱ ፍጻሜ የለውም፤ ብቻ እርሷን ለማወቅ ተሰጥቶኛልና ስለእርሷ ማንነት መናገር ብዙም አይቸግረኝም፡፡ የሚደንቀኝ ግን ስለ ራሴን መርምሬ ለማወቅ አለመቻሌ ነው፡፡ ረቂቅ መንፈስ መሆኔን አውቃለሁ ነገር ግን አይቼ ዳስሼ አረጋግጬ አይደለም፡፡ መዓዛዬን፣ ቁመቴን፣ ውፍረቴን፣ ቅጥነቴን ገጽታዬን ጭምር አላውቀውም፡፡ በአጠቃላይ መንፈስ መሆኔን እንጂ ለሌላው ማንነቴ ባይተዋር ነኝ፡፡ የሚደንቀው ግን መላእክት እርሷን ማወቃቸው ነው፡፡

Tuesday, July 11, 2017

አረጋዊው ማን ነው?

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
4/11/2009
መቼም ስለ ዕድሜ ሲነገር ቆጠራው ከጽንሰት ከተጀመረ እንደ ጻድቁ ኢዮብከሴት የተወለደ ሰው የሕይወቱ ዘመን ጥቂት ቀን ነው፥ መከራም ይሞላዋል”(ኢዮ.141) ማለታችን ግድ ነው፡፡ ከጽንሰት የምንጀምራት ዕድሜአችን እንደ ጠዋት ጤዛ ወይም እንደ ሳር አበባ ናት፡፡ ባንድ ቀን ለምልማ በአንድ ቀን የምትረግፍ አበባ ማለት ይህቺ ምድራዊዋ ዘመናችን ናት፡፡ ቢሆንም ዋጋ ያላትም ይህቺው ዕድሜአችን ናት፡፡ በዚህች ዕድሜአችን በሰውነት ሕዋሳቶቻችን ሁሉ መልካምን ካልሠራንባቸው ዕዳዋ ዘለዓለማዊ ሆኖ ይሠፈርብናል፡፡ ከሠራን ደግሞ የተጠቀጠቀና የተጨቆነ ብድራትን ከአምላክ ዘንድ እናገኝባታለን፡፡ ግን ደግሞ ዕድሜአችንን በአምላክ ሕሊና ከመታሰባችን ጊዜ አንስቶ እንደ ንጉሥ ዳዊትአቤቱያልተሠራ አካሌን ዓይኖችህ አዩኝ የተፈጠሩ ቀኖቼ ሁሉ አን ስንኳ ሳይኖር በመጽሐፍህ ተጻፉ”(መዝ.13816) ብለን የቆጠርን እንደሆነ ዕድሜአችን የትናለሌ ሊሆን ነው፡፡ ከመቼ ጀምሮ በአምላክ ሕሊና እንደታሰብን በጭራሽ አናውቀውም ግን ደግሞ አምላክ እንደ ሰው አያስብምና መነሻ አለው ማለት አይቻለንም፡፡ እርሱ ያሰበው ከዘለዓለም ያሰበው ነው፤ እንዲያስብ ምክንያቶች አያስፈልጉትም፡፡ የማያውቀው ወደፊት የሚያውቀው ነገር የለውም፡፡ ስለዚህ ዕድሜአችንን በእግዚአብሔር ሕሊና ከመታሰባችን አንስቶ ከቆጠርነው ሳንወለድም በፊት አረጋውያን ነን ምክንያቱም ሳይሠራን በሕሊናው ነበርን ሳንፈጠርም ቀኖቻቸችን በእርሱ ሕሊና የታወቁ ናቸውና፡፡
አደራ ግን ይህ ቃል ስለ ዳዊት ብቻ የተነገረ ነው እንዳትሉኝ ምክንያቱም አምላክ ሳያስበው የሚፈጥረው ነገር የለምና፡፡ አይደለም እርሱ እኛ እንኳ ያላሰብነውን አንተገብርም፡፡ በሕሊናችን የጨረስነውን በተግባር እንፈጽመዋለን፡፡ ስለዚህ ቃሉ ያለጥርጥር ለዳዊት ብቻ የሚሠራ ሳይሆን ለእኛም ይሠራል፡፡ እንዲህ ከሆነ ታዲያ ዕድሜአችን ስንት ነው? እንጃ እርሱ እግዚአብሔር ያውቀዋል እኛ ልናውቅ የምንችለው ቢኖር በሥጋ ተጸንሰን በዚህ ምድር የተመላለስንባትን ዕድሜ ብቻ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ዕድሜ የለም ከዚያም በኋላ በትንሣኤ ዕድሜ አይኖርም፡፡ ከእነዚህ አንጻር በሥጋ የምንኖርባት ይህቺ ዕድሜ ስትሰላ እንደ ጠዋት ጤዛ ጠዋት ታይታ ፀሐይ ሲተኩስ የምትጠፋ ወይም እንደ ምድር አበባ በአንድ ቀን አብባ በአንድ ቀን የምትከስም እንደሆነች እንረዳለን፡፡

Sunday, June 11, 2017

የነፍስ ወግ (በእንተ ደናግላን)


እንደ ጢሞቴዎስ ከልጅነት ጀምሮ ከቅዱሳን መጻሕፍትና ከመንፈስ ቅዱስ እንዲሁም ከትርምት ሕይወት ስለእግዚአብሔር የተማረ፤ የልቡናውን ደጅ በመዝጋት ከሕግ መምህር ትምህርቱን የቀዳ ክርስቲያን ለእርሱ ከትዳር ሕይወት ይልቅ የድንግልና ሕይወት እንዴት የተመረጠ ሕይወት አይሆነው? ይህ ሰው ማዕረጉ ከመላእክት ወገን ነውና የሥጋ ፍትወት የራቀለት በትንሣኤ ሕይወት የሚኖር እግዚአብሔር ሳይመርጥ ኃጥኡንም ጻድቁንም እንዲወድ ሁሉን የሚወድ በአንዲት ብላቴና ፍቅር ታሥሮ እርሱዋን አስቀድሞ ሌላውን አስከትሎ መውደድ የማይቻለው፣ እንደ አምላኩ ሁሉን አስተካክሎ የሚወድ በትዳር ውስጥ ያሉቱ ጥንዶች በትንሣኤ የሚያገኙት ሙሉዕ የሆነ ፍቅር አግኝቶ የሚኖር ሰው ነው፡፡

Thursday, June 8, 2017

የነፍስ ወግ ሦስተኛ ክፍል በእንተ ትዳር

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
02/10/2009
ትዳር መልካም ነው፡፡ የትዳርን ትርጉም ከዚህ በፊት እንደጻፍኹላችሁ በገዛ ሰውነታችን ውስጥ በምሳሌነት እናገኘዋለን፡፡  ይህ ደግሞ የሚደንቅ ነው፡፡ ይህንንም በልጆቻችን እንመለከተዋለን፡፡ እነርሱ የአንድነታችን ውጤቶች ናቸው፡፡ ቢሆንም ከዚህ በፊት በዚህ ጉዳይ ላይ ሰፊ ትንታኔ የሰጠሁ ስለመሰለኝ ለዛሬ በዚህ ላይ ብዙ አልልም፡፡ ልብ እንድትሉ የምፈልገው ነገር ግን በነፍስና በሥጋ መካከል ያለው ተዋሕዶ የትዳር አምሳያ መሆኑን ነው፡፡ እረ እንደውም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቃል ከሥጋና ነፍስ ጋር በማኅፀን በተዋሕዶ አንድ መሆኑ የትዳር አምሳል እንደሆነ ያስተምረናል፡፡ እናም ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው ገና በጽንሰት ጊዜ መለኮትና ሥጋ አንድ በሆኑበት ቅጽበት ነበር፡፡ ስለዚህም በዚህ የሥጋው መጋረጃ በኩል ወደ ቅድስት መግባትን አግኝተናል:: እርሱም ከእናቱ ከቅድሰት ድንግል ማርያም የነሣው ሥጋ ነው፡፡ ይህ ሰውነቱ የገነት አምሳያ ስለሆነ ቅዱስ ኤፍሬም በተወጋው ጎኑ በኩል ወደ ገነት መግባትን አገኘን ብሎ ያስተምራል፡፡ በእርግጥም ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ ነጽተን ከጎኑ በፈሰሰው ደም ተዋጅተን በእኛ ችሎታ ሳይሆን በእርሱ ቸርነት የክርስቶስ የአካል ሕዋሳት ለመሆን በቅተናል፡፡ ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን በሆነችው ሰውነቱ በኩል መዳናችን ተፈጸመ፡፡ ሁሉ የእርሱ ከእርሱ ለእርሱ በእርሱ የሆነው ይህ ምስጢር እንዴት ድንቅ ነው!!

Friday, April 14, 2017

የነፍስ ወግ

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
6/08/2009

ረቂቅ የሆነ እርሱ ፈጣሪዬ በእርሱ ፊት ምንም ግዙፍ ብሆን ሚስቴ ላደረጋት ከምድር አፈር ለፈጠራት ሥጋዬ በእርግጥም ረቂቅ ነኝ፡፡ እርሱ የፈጠረኝ አምላክ በእርሱ አርአያና አምሳል የፈጠረኝ ቢሆንም እንደርሱ ረቂቅ ስለሆንኹ ረቂቃኑ መላእክትም ግዙፋኑ ፍጥረታትም የእርሱን አርአያ በግዘፍ እንዲያዩ አምለክ ሥጋ ሚስቴን ግዙፍ አድርጎ ፈጠራት፡፡
 ከመላእክት እኔ የምለየው ከሥጋ ጋር አንድ አካል መሆን ስለሚቻለኝ ነው፡፡ በሌላ ተፈጥሮዬ ግን ከእነርሱ ጋር አንድ ነኝ፡፡ ቢሆንም ለእኔ ከውድቀት በፊት የነበረው የሥጋ ተፈጥሮ በእጅጉ ይስማማኝ ነበር፡፡ ምክንያቱም በገነት ለሥጋ የተሰጡ መብላት ሥጋን በሕይወት እንድትቆይ ምንም ዓይነት ሚና የላቸውምና ሥጋን በሕይወት ለማቆየት ስል ምንም ድካም የለብኝም ነበርና፡፡ ከውድቀት በኋላ ግን ከመላእክት ጉባኤ በልዩ ተፈጥሮ ሆኜ የአምላኬን ፍቅር እየተመገብሁ ከምኖርበት መኖሪያዬ ገነት በራሴው ጥፋት የክፋት ምክንያት የሆነውን ሞትን በሥጋዬ ላይ ሹሜ፥ ፍቅርን አጥፍቼ ፥ ፍርሃትን አንግሼ ከመላእክት ጉባኤ ተለየሁ፡፡

Thursday, January 5, 2017

ዐይንተ አልባቢነ


ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
27/04/2009
መጽሐፍ ቅዱስ ሥጋንም ነፍስንም በተናጠል ሰውነት ይላቸዋል፡፡ ግዙፉን አካል ሰውነት እንዲለው አንዲሁ ቅዱስ ጳውሎስ “በመንፈሱ በውስጥ ሰውነታችሁ በኃይል እንድትጠነክሩ ክርስቶስም በልባችሁ በእምነት እንዲኖር እንደ ክብሩ ባለ ጠግነት መጠን ይስጣችሁ፤ የእናንተ መሠረት በፍቅር ይጸና ዘንድ”(ኤፌ.3፡16-17) ብሎ እንደጻፈልን ረቂቋንም ነፍስ ውስጣዊ ሰውነት ይላታል፡፡ ይህ የተዋሕዶን ምሥጢር ለማስረዳት  ትልቅ ቁልፍ ቃል ነው፡፡ ምንም እንኳ መጽሐፍ ሥጋንና ነፍስን በተናጠል ሰውነት ይበላቸው እንጂ ሰውነታችን አንድ ነው፤ ሁለት አይደለም፡፡ ሰውነት ስንል ደግሞ በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ የሥጋና የነፍስ አንድነት ስያሜ ነው፡፡ ሥጋና ነፍስ ፍጹም በሆነ ተዋሕዶ አንድ ሆነዋል፡፡ ነገር ግን የየራሳቸው ግብር አላቸው ቢሆንም በተናጠል አይደለም፡፡
በክርስቶስም የምናየው ይህንን ነው፡፡ እርሱ “እንግዲህ የሰው ልጀ አስቀድሞ ወደ ነበረበት ሲወጣ ብታዩ እንዴት ይሆናል?” በሚለው ቃሉ ለሰው ልጅነቱ ቅድምና ሰጥቶ መናገሩን እናስተውላለን፡፡ “በሁሉ ወንድሞቹን ሊመስል ተገባው”(ዕብ.2፡17) የሚለው ደግሞ ሰዋዊ ማንነቱ እንዳልተለወጠ ያስገነዝበናል፡፡ በዚህ ማነንቱ ሆኖ አምልኮ ለእርሱ ለእግዚአብሔር በግ ቀረበለት፡፡ ጌታ ተወለደልን ተባለ፤ ሕፃን ሳለ አምልኮን ከሰብአ ሰገል ተቀበለ፡፡ አንድያ የአግዚብሔር ልጅ፣ አምላክ፣ እግዚአብሔርም ተባለ፤ በደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ” ተብሎ”ደሙ" የእግዚአብሔር ደም ተባለ፡፡ በዚህም መለኮታዊ ልዕልናውን የሰው ልጅ ሲል እኛንም በመምሰሉ ራሱን የሰው ልጅ ብሎአል፡፡ ለሁለቱም ማንነቱ አንድ "የሰው ልጅ" የሚለውን ስያሜ ተጠቀመ፡፡ ይህም ከድንግል የተካፈለውን ሰውነት ከመለኮታዊ ልዕልናው መለኮታዊ ልዕልናውን ከሰውነቱ ነጣጥሎ እንዳላስተማረን በተረዳ ነገር ታወቀ፡፡ በዚህ ጥቅስና በሌሎችም ጥቅሶች ጌታችን የተዋሕዶውን ምሥጢር ገለጸልን፡፡

Tuesday, July 14, 2015

እድሜ ይስጥልኝ ብያለሁ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

07/11/2007

እንደ መንፈሳዊ መረዳት ድንቅ የሚለኝና የሥነ ተፈጥሮአችን አንዱና መሠረታዊ ክፍል  ስለሆነው ነገር ልንግራችሁ። ከእናት ማኅጸን ሥጋችን ከነፍሳችን ጋር ተዋሕዳ ከተፈጠረችበት ጊዜ አንስቶ ወደ እርጅናና ሞት ስታዘግም ነፍሳችን ግን እለት እለት እየታደስችና በእውቀት ሙሉ እየሆነች በመምጣት ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው እርሷ በእግዚአብር ዘንድ  እንደታወቀች እስክታውቅ ድረስ ደርሳ ፍጹም ወደ መሆን ታድጋለች። የዛኔ እግዚአብሔር አምላኩዋን አባ አባ ስትለው በፍጹም ልጅነት መንፈስ ሆና ነው። እንዲህ በመሰለ መንፈሳዊ ከፍታ እያደገ የሚመጣው ግን ሰሎሞን "ጥበብ" ያለው  ሲወድቅም ሲነሣ ያልራቀው  የእግዚአብሔር መንፈስ ከእርሱም ጋር የሆነለት ሰው ብቻ  ነው። 

Tuesday, May 5, 2015

ወገኖቼ አንድ እውነት ልንገራችሁ



ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

27/08/2007

 እውነቱም ይህ ነው፡- ደስታና እረፍት አይደለም በምድራዊ ሕይወታችን ውስጥ ይቅርና በመንፈሳዊው ምልልሳችን እንኳ ሁሌ የምናገኘው አይደለም፡፡ በምድር የምናጣጥማቸው ደስታና እረፍት መገኛቸው ከእግዚአብሔር ስጦታዎች እንጂ ከሌላ ከምንም አናገኛቸውም። ቢሆንም እነዚህ የሚታወኩበት ጊዜ ስለሚመጣ ያኔ ደስታህና እረፍትህ ለጊዜውም ቢሆን ሊወሰዱብህ ይችላሉ፡፡ እንዲህም ቢሆን ተፈጥሮውያኑ የእግዚአብሔር ስጦታዎች እየተጤኑ ካልሆኑ በቀር ከወይኒ ቤትም በላይ የከፉ የስቃይ እስር ቤት ሊሆኑብህ ይችላሉ፡፡
ስለዚህ ወገኔ በእነዚህ የእግዚአብሔር ስጦታዎች ሙሉ ለሙሉ ባይሆን እንኳ የደስታህና የእረፍትህ እርሾ ከአንተ ፈጽሞ እንዳይወሰድ ከፈለግህ አስቀድመህ ይሉንታን ከራስህ አርቅ ፡፡ ይሉንታ የደስታንና የእረፍትን እርሾ ፈጽሞ ከሰውነትህ የሚያስወግድና በምትኩ የማይጠፋ የቁጭት ፍም አኑሮ የሚያልፍ ነው፡፡ ስለዚህ ወዳጄ ሕሊናህ የሚልህን ስማው ፤ ሕሊና የአንተን ደስታና እረፍት ጠንቅቆ የሚያውቅና የቁጭት ፍምን ከአንተ የሚያርቅ መለኪያህ ነው፡፡
 ወዳጄ እንደ ምሳሌ እናንሣ ብንል እንኳ ተፈጥሮአውያን ስጦታዎች ከሆኑት መካከል አንዱና ዋነኛው ፆታዊ ፍቅር ነው።
  ወገኔ ሆይ ትዳር መልካም ነው፤ ነገር ግን ለትዳር ጓደኝነት ከውጫዊ ቁሳቁሶች በፊት ፍቅርን አስቀድም፡፡ ከዚያ በኋላ በትዳርህ ደስታና እረፍትን ታገኛለህ፡፡ 

Monday, March 16, 2015

ክርስትና

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 

06/07/2007

ክርስትና ሰው ሆነን የተፈጠርንበትን ድንቅና ግሩም የሆነውን እግዚአብሔርን የምንመስልበት አቅምን የሚሰጠን መንፈስ ቅዱስን በኃጢአታችን ምክንያት አጥተን ስንባዝን ለነበርነው ክርስቶስ በመስቀሉ ዳግም የሰጠን እውቀት ሳይሆን ሕይወት ነው። ሲጠቃለል ክርስትና ማለት ሰው መሆን ማለት ነው። ሰውን ሰው የሚያሰኙት ተፈጥሮውና ተግባሩ ናቸው። ተፈጥሮው ሲባል ሰው ግሩምና ድንቅ የሆነውን እግዚአብሔርን የሚመስልበት አቅሙን ማለታችን ነው። እግዚአብሔርን የሚመስልበት አቅሙን ግን ወደ ተግባር መልሶ ይሠራበት ዘንድ ግን መምህር የሚሆነው መንፈስ ቅዱስ በውስጡ ያድርበት ዘንድ ግድ ነውና ጌታችን አዳምን ከምድር አፈር ካበጀው በኋላ የሕይወት እስትንፋስን በአፍንጫው እፍ በማለት ሰውነቱን ምድርን በውበት ላስጌጣት መንፈስ ቅዱስ ማደሪያ አደረጋት። ሰው ለዚህ በውስጡ ላደረበት መንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ሲታዘዝ ሰው ተብሎ ወደ መጠራት ይመጣል። ሰው ከሆነ ደግሞ ክርስቲያን ሆነ ማለት ነው። ክርስትና እንግዲህ እንዲህ ናት ወሬ ሳትሆን ሕይወት ናት። ክርስትና ሰው በመሆን ሰው የመሆንን ትርጉም ያሳየንን ክርስቶስን መምሰልን የምትጠይቅ ናት። አቤቱ አምላኬ ሆይ እባክህ ግሩምና ድንቅ ወደሆነው ሰዋዊው ማንነቴ በቃል ሳይሆን በተግባር አድግ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ ለነፍሴ እውቀትና ሕይወት እንዲሁም ብርሃን ሆኖ አንተን እመስል ዘንድ እርዳኝ።  የቀደመውን ኃጢአቴን አታስብብኝ ከኃጢአት ፈቃድም ንጹሕ አድርገኝ። ልቡናዬን ለፍጥረት ሕይወት በሆነው ሕያው ቃልህ ሙላው ። አሜን ለዘለዓለም ይሁን ይደረግልኝ።

Wednesday, October 16, 2013

ምንኩስናና ትዳር የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች


05/02/2006
በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ


ክርስትና ለሰይጣን ይገዛ ከነበረ ዓለም ወጥቶ እርሱ የጽድቅ ጸሐይ የሆነው ክርስቶስ ብርሃን ሆኖት በቀን እንጂ በጨለማ የማንመላለስበት የቀን ልጅ ተሁኖ የሚኖርበት ሕይወት ነው፡፡ ክርስትና ከክርስቶስ ጋር ተሰቅለን ነፍስ በምትሰጠው ሕይወት ሳይሆን ለዘለዓለም አባ አባ ብለን የምንጠራበትን መንፈስ በሰጠን በመንፈስ ቅዱስ ሕያዋን ሆነን የምንኖርበት ሕይወት ነው፡፡ ስለዚህም ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር ራሳችንን ለጽድቅ ሥራ ያጨን ደናግላን ነን፡፡ አገባንም አላገባንም ለክርስቶስ የታጨን በመሆናችን ደናግላን ነን፡፡ ይህ ድንግልና የሚጠፋው ክርስቶስን ክደን በሰይጣን ሕያዋን ሆነን የኖርን ሰዓት ነው፡፡ቢሆንም ግን ይህም ቢሆን በንሥሐ የሚታደስ ድንግልና ነው፡፡ ጌታ ጠፍተን እንድንቀር የማይወድ ከኃጢአታችን ይልቅ መጥፋታችን የሚያሳዝነው በንስሐ በተመለስን ጊዜም በደስታ እጆቹን ዘርግቶ በፍቅር የሚቀበለን አምላክ ነው፡፡

Friday, December 28, 2012

እኔ ከመጽሐፍ ቅዱስ ይልቅ ራሱ መንፈሱ የእምነት ምንጭ ነው እላለሁ



ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
19/04/2005
በመጽሐፍ ብቻ የሚለው አመለካከት ለእኔ  ትክክል አይመስለኝም፡፡ ከመጽሐፍ ይልቅ በልብ ሰሌዳ በመንፈሱ የተጻፈ የመንፈስ ቅዱስ መልእክት አለ፡፡ መንፈሱ ያደረበት ሰው የማይመረመረውንና የማያልቀውን የእግዚአብሔርን ሃሳብና ፈቃድ ወደ መረዳት ይመጣል ሁሌም መንፈስ ቅዱስ ሰማያዊ የሆኑ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ያልሰፈሩ ወይም ያልተብራሩ እውነታዎች ይገልጥለታል፡፡
 በብሉይም በሐዲስም የእግዚአብሔር ፈቃድና ሃሳብ በወረቀት ላይ በብዕር ቀለም መጻፍ ያስፈለገበት ምክንያት ሰዎች አስቀድሞ እግዚአብሔር በመንፈሱ በልባቸው ጽላት ላይ የጻፈውን ፈቃዱንና ሕጉን በኃጢአት ምክንያት ፈጽመው በመዘንጋታቸው ነው፡፡ ስለዚህም መጽሐፍ ቅዱስ ሰዎች ፈቃዱን አውቀው በጽድቅ ይመላለሱ ዘንድ የተሰጠ ሁለተኛው እድል ነው፡፡ ለዚህ ማሳያው ከአዳም እስከ ሙሴ ድረስ ያሉ ቅዱሳንና ሐዋርያት እንዲሁም ሐዲስ ኪዳን ሳይጻፍላቸው በሐዋርያት ትምህርት ይኖሩ የነበሩ ቅዱሳን ክርስቲያኖች ናቸው፡፡

Monday, December 24, 2012

ወንድሞቼና እኅቶቼ በጋብቻ መነኩሳት ትሆኑ ዘንድ ምኞቴ ነው!!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
15/04/2005
ፍጹም አንድ መሆን፡፡ የራስን አካል የሚያውቁትን ያህል ማወቅ ምንኩስና የሚለውን ቃል ፍቺ ይሰጠናል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ መንፈሳዊ ጋብቻ የሚለው በመለኮትና በሥጋ መካከል የተፈጸመውንና በልደት የተገለጠውን ተዋሕዶን ነው፡፡ ይህን ጋብቻ ይለዋል፡፡ አንድ ክርስቶስ፣ አንድ ኢየሱስ፣ አንድ የእግዚአብሔር ልጅ፣ እርሱ የመለኮትና የሥጋ ተዋሕዶ ውጤት ነው ይህን ለሰው ልጆች ካለው ፍቅር የተነሣ በገዛ ሥልጣኑ አደረገው ፡፡ ፍጹም የተዋሐዱ ፈጽሞ የማይለያዩ አንድ አካል ብቻ የሆነ፡፡ መነኮስ ማለትም አንድ ብቻ፤ ብቸኛ ማለት ነው፡፡ሁለቱ አንድ ይሆናሉ” የሚለው ቃል ሲፈጸም አንድብቸኞች ይሆናሉ ግን ሙሉ ናቸው፡

Saturday, December 15, 2012

የሞቴ ማስታወሻ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
06/04/2005
ሰው ማለት እንደ እግዚአብሔር ነው፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ ከንቱ የሆነች አንዲትም ሰከንድ የለችም፡፡ ሰውም እንዲሁ ዘመኑን ሁሉ በጥንቃቄና ያለዝንጋዔ እግዚአብሔርን መስሎ ሊኖር ተፈጠረ፡፡ የሰው ደስታው እውነት፣ ጽድቅ፣ ቅን ፈራጅነት፣ ከእውቀት ያልተለየ ፍቅር ናቸው፡፡ እነዚህን በተመለከተ አዳም አባታችን፣ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና እርሱን በቅርበት ያወቁት ሐዋርያት ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡ ከጌታችንና ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትም የምናስተውለው ሰው ሊጸድቅ የሚችለው ልቡን በቃሉ ሞልቶ የሥነ ምግባራችን ቁልፍ በሆነው ማስተዋል የተመላለሰ  እንደሆነ ነው፡፡ ይህን ግን ምናልባት በቀን ውስጥ ሁለት ደቂቃ ግፋ ቢል አምስት ደቂቃ ሰጥተን ብናስበው ነው፡፡ ይህም የሚሆነው ስለእግዚአብሔር እውቀቱ ካለው ነው፡፡ የሌለው ግን ዘመኑን ሁሉ እንደ ነዌ ያሳልፈዋል፤ አንድም ሰከንድ እንኳ እግዚአብሔርን የሚያስብበት ጊዜ የለውም፡፡ ከዚያ ይልቅ በዝንጋዔ ሆኖ በስሜቶቹ ፈቃድ እየተነዳ በኃጢአት ሲንቧቸር ይኖራል፡፡ ይህ የአብዛኞቻችን ሕይወት ነው፡፡

Wednesday, December 12, 2012

ክብርት ስለሆነችው ሥጋችንና በእርሱዋ የእግዚአብሔር ፈቃድ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
04/04/2005 ዓ.ም
ሥጋ ክብርት ናት፡፡ ገናም ከአፈጣጠሩዋ በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ የተፈጠረች ናት፡፡(ዘፍ.9፡6) የማይታየው የእግዚአብሔር መልክና ባሕርይ የሚታየው በሚታየው በሥጋ ተፈጥሮአችን በኩል ነው፡፡ የእግዚአብሔርን መልክና ክብር በክርስቶስ አይተነዋል፡፡ እኛንም ማዳኑ በሥጋው ሰውነቱ ነው፡፡ ተወለደ፣ በየጥቂቱ አደገ፣ ደከመ፣ አንቀላፋ፣ ታመመ፣ ተጨነቀ፣ ተሰቃየ፣ ሞተ መባሉ በሥጋው ነው፡፡
ሰውነታችን ከምድር አፈር መፈጠሯም በራሱ ሥጋን ቢያልቃት እንጂ የሚያሳንሳት አይደለም፡፡ ምድር በመኅፀኑዋ ሕይወትን፣ ኃይልን፣ ውበትን፣ መድኀኒትን፣ ለፍጥረት ሁሉ ምግብ የሆኑ በዓይነትና በብዛት እንዲሁም በይዘት እጅግ ብዙ ንጥረ ነገሮችን ሰውራና አቅፋ የያዘች ናት፡፡ እነዚህ ንጥረ ነገሮች ከሰማይ በሚወርደው ዝናብ ምክንያት ተብላልተውና ተስማምተው በእግዚአብሔር ጥበብ ለፍጥረት ሁሉ ምግብን፣ ፈውስን፣ ውበትና ኃይልን ሲሰጡ ይኖራሉ፡፡ ይህን አስመለክቶ እግዚአብሔር “በዚያ ቀን እመልሳለሁ ይላል እግዚአብሔር፤ ለሰማይ እመልሳለሁ ሰማይም ለምድር ይመልሳል ምድርም ለእህልና ለወይን ጠጅ ለዘይትም ትመልሳለች፡፡”(ሆሴዕ.2፡23)ይለናል፡፡