Saturday, November 1, 2014

ተወዳጆች ሆይ



ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
22/02/2007

ወገኖቼ ሆይ አንድ የልብ ምክር አለኝና አድምጡኝ፡፡ ወዳጄ የቤተሰብ ሓላፊ ከሆንህ - እኔ ለቤተሰቤ እንደ ኢዮብ ካህን ነኝ ስለዚህ በመንፈስ ሁል ጊዜ፤ በአካል ደግሞ እንደ ችሎታዬ መጠን ስለራሴ ምክንያቱም በመልካም ማስተዋል ቤተሰቤን እመራ ዘንድ ስለቤተሰቤ ምክንያቱም ቤተሰቤ በኃጢአት ምክንያት አእምሮው እንዳይቆሽሽ በራስ መተማመን እንዳያጣ በማስተዋልና እግዚአብሔርን በመፍራት እንዲመላለሱ ስለሀገሬ ሰዎች ደግሞ በሰላም ወጥተው በሰላም እንዲገቡ ማስተዋልንና እርስ በእርስ መግባባትን እንዲሰጣቸው ፍቅር እንድትነግሥ ስለዓለሙ ሁሉ ደግሞፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁንእንድንል ጌታ እንዳስተማረን የምንኖርባት ዓለም ፈቃዱን ለማድረግ እንደሚተጉ መላእክት ለመልካም ሥራ እንዲበረቱ በጸሎት መትጋት አለብኝ ብለህ ለልብህ ንገረው፡፡

Sunday, October 19, 2014

ተወዳጆች ሆይ ዓይኖቻችሁ ከወዴት ናቸው?



ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
9/02/2007
ተወዳጆች ሆይ ዓይኖቻችሁ ከወዴት ናቸው?ዓይንን ስናነሣ ግን ሰው ሁለት የነፍሰ ዓይኖች እንዳሉት ቅዱስ ይስሐቅ ወይም ማር ይስሐቅ ይናገራል፡፡ አንዱዋ የነፍሳችን ዐይን ፍጥረትን አፍ እንደተገጠመ ጆሮም ከመስማት እንደተከለከለ ሀሳብም ጌታ ጸጥ እንዳሰኘው የባሕር ማዕበል ከምድራዊ ፍላጎቶች ጸጥ ብላ የፍጥረታዊውን ዓለም ጥንተ ተፈጥሮውን ተመልክታ ፈጣሪዋን ስታደንቅና ግሩም ግብሩ ለእግዚአብሔር ብላ ስታመሰግን ሌላኛይቱ ዓይን ደግሞ በርቀት(በረቂቅነት) በሁሉ ሙሉ ሆኖ የሚኖረውን አምላክ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስን በእምነት ተመልክታ ብርሃናዊውን የመላእክትን ምግብ እርሱም ፍቅሩን እየተመገበች ቅዱስ ዳዊት ዓይኖቼ አንተን በማየት ፈዘዙ እንዳለው በትንግርትና በመደመም ስትመለከተው ትኖራለች፡፡ ያልታደለችው ዓይን ግን ራሱዋን ሳትመለከት የሰውን ጉድለት እያየች ለአእምሮ ሐሜትን እየመገበች ሰውነትን ስታሳድፍ ትኖራለች፡፡

Sunday, July 6, 2014

ቤተ ኦርቶዶክስ


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
29/10/2006 ዓ.ም

ኦርቶዶክስ ስንል በክርስቶስ መሠረትነት፣ የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ተብላ፣ በመንፈስ ቅዱስ አስተማሪነት፣ ለሐዋርያትና ለነቢያት በተሰጠው ፍጹም በሆነው በማይናወጥና ፍጻሜ በሌለው ግን መሠረት ባለው እግዚአብሔራዊ አስተምህሮ ላይ የተመሠረተችውን፣ በሰዎች ፖለቲካዊ ጥማት ቤተ ክርስቲያን በሚባል ሽፋን ብዙ የእምነት ድርጅቶች ሳይመሠረቱ በፊት፣ ያለች በተለይ 451 በፊት ያለውን የቤተክርስቲያን አስተምህሮ ይዛ የቆየች እምነት ማለታችን  ነው፡፡ በዚህ መሠረት ክርስቶስ ዓለምን ለማዳን እንደመጣ መንግሥቱ የሆነች ቤተ ክርስቲያንን የሰው ሁሉ መዳን የምታገለግል አድርጎ በደሙ እንደ መሠረታት መጠን ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ዓለማቀፋዊት ናት፡፡ በእርሱዋ ውስጥ ግሪካዊ አይሁዳዊ የሚል የዘር ልዩነት ሴት ወንድ ብሎ የጾታ ልዩነት የሌለባት በጥምቀት ከክርስቶስ ጋር በመቀበርና በአዲስ ሕይወት በመነሣት ሕያው በሆነው መንፈስ ቅዱስ  የምትመራ በልዕልና የሚኖርባት እምነት ናት፡፡
ከዚህ የተነሣ ኦርቶዶክስ ስንል መሠረቱዋ መጻሕፍትን ያጻፈው መንፈስ ቅዱስ ሆኖ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያልተብራሩትንና የታወቁትን ግን ያልተገለጡትን እውነታዎች በሰውነታችን ባደረው ሕያው በሆነው መንፈስ ቅዱስ በሚሰጣት ማስተዋል የምትረዳና መጽሐፍ ቅዱስን እንደ ሁለተኛ የእውቀት ምንጭ አድርጋ የምትቀበል ናት፡፡

Sunday, April 27, 2014

ዘኬዎስ


ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
19/08/2006

ቅዱስ ኤፍሬም ዘኬዎስ ጌታን ሲቀበል የነበረውን ምናባዊ በሆነ መንገድ እንዲህ ብሎ ጽፎልናል፡፡ በነገራችን ላይ እንዲህ ዓይነት ስዕላዊ አጻጻፍ ስልት የሴማዊያን የአጻጻፍ ስልት ነው፡፡
ዘኬዎስ በልቡ“ ይህን ጻድቅ ሰው በእንግድነት በቤቱ የተቀበለ ሰው ብፁዕ ነው” ብሎ በልቡ ጸለየ፡፡ ልብ ያሰበውን ኩላሊት ያመላለሰውን የሚያውቅ ጌታ ደግሞ የልቡን ጸሎት ሰምቶ “ዘኬዎስ ሆይ ዛሬ በቤትህ እውል ዘንድ ይገባኛልና ፈጥነህ ውረድ” አለው፡፡ ዘኬዎስም በልቡ ሲያመላልስ የነበረውን ጌታ እንዳወቀበት ተረድቶ “ይህ ያሰብሁትን ያወቀ የሠራሁትንስ ሁሉ እንዴት አያውቅ? በማለት ለጌታችን መልሶ “ጌታ ሆይ ካለኝ ሁሉ እኩሌታውን ለድሆች እሰጣለሁ ማንንም በሃሰት ከስሼ ብሆን ዐራት እጥፍ እመልሳለሁ” አለ፡፡ ጌታውም “ፈጥነህ ውረድ በቤትህ እውል ዘንድ ይገባኛልና ብሎ መለሰለት፡፡” በኋለኛው የበለስ ተክል ምክንያት በአዳም በለስ ምክንያት የሚታወሰው በለስ ተረሣ፡፡ ዘኬዎስ በበደሉ ምክንያት “ጌታ ሆይ ካለኝ ሁሉ እኩሌታውን ለድሆች አሰጣለሁ ማንንም በሃሰት ከስሼ ብሆን ዐራት እጥፍ እመልሳለሁ” በማለቱ ለዚህ ቤት መዳን ሆነለት፡፡
ተቃዋሚዎች በዚህ ሰው እውነተኛ ደቀ መዝሙርነት  ይደነቁ፡፡ አስቀድሞ ሌባ የነበረ አሁን ግን መጽዋቾች ሆነ አስቀድሞ ቀራጭ የነበረ ዛሬ ግን የክርስቶስ ደቀ መዝሙር ሆነ፡፡ ዘኬዎስ ቅን የሆነውን ሕግ ወደ ኋላ ትቶ ተምሳሌታዊ በሆነ መንገድ ላለመስማቱ ምልክት ወደሆነችው ወደማትሰማውና ወደማትለማው ዛፍ ተወጣጣ፡፡