Monday, May 29, 2017

የነፍስ ወግ ካለፈው የቀጠለ….


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
22/09/2009



እናንተዬ እኔ ረቂቋ ነፍስ ይህን ሁሉ ሳስብ ሐዲስ ኪዳንን ዘንግቼ ብሉይ ኪዳን ውስጥ ያለሁ መሰለኝ፡፡ ለመሆኑ በክርስቶስ ያለኝ ተስፋ ወዴት ሄደ? በርሱስ ያገኘሁት ሕይወት የት ደረሰ?? ክርስቶስን ሳስብ ሚስቴ የሆነችው የሥጋዬ በደል ፈጽሞ ይጠፋል ቀንበሯም ቀሊል ይሆንልኛል፡፡ እንደውም እርሷ ባትኖር ኖሮ እኔ ነፍስ እድን ነበርን? ብዬ ራሴን እጠይቃለሁ፡፡ እረ በፍጹም ሥጋዬ ባትኖር ኖሮ ከአምላክ የመለየትን ትርጉም በምን እረዳው ነበር? ለንስሐስ እንዴት እተጋ ነበረ? እንዴትስ አምላኬን አየው ነበረ? እኔ ብቻ ሳልሆን መላአክትስ ቢሆን ከነርሱ በእጅጉ የሚረቀውን አምላክ ለመመልከት የበቁት በማን  ሆነና?

Thursday, May 25, 2017

ቅድስት እናቱን ለምን ኪዳነ ምህረት እንላታለን?

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
19/09/2009

ክብር ለእርሱ ለወደደን ለኢየሱስ ክርስቶስ ይሁንና ብዙዎች ድንግል እናቱን ኪዳነ ምህረት ስንል ግራ ሲጋቡ አስተውላለሁ። በእርግጥም ግራ ቢጋቡ አይደንቅም ምክንያቱም ለመረዳት መጽሐፍ ቅዱስን ጠንቅቆ መረዳትና የመንፈስ ቅዱስ ድጋፍ ይፈልጋልና። በብሉይ አማናዊው መሥዋዕት ከመሰዋቱ በፊት የቃል ኪዳኑ ታቦት ላይኛው ክፍል “የሥርየት መክደኛ” በእንግሊዘኛው ደግሞ “mercy seat` ይህም ማለት “የምሕረት ዙፋን"  ይባል ነበር። ምክንያቱም እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር ቃል ኪዳን በማድረጉ በታቦቱ  ራስ ላይ ተገልጦ ሙሴን ያነጋገረው ከካህናቱም መሥዋዕት ይቀበል የነበረው በዚህ ሥርየት መክደኛ ላይ ሆኖ ነበርና። ይህ መገለጥ ግን ከሰዎች ልጆች ጋር ፍጹም እርቅ መፈጸሙን የሚያሳይ አልነበረም። ነገር ግን በዚህ ሕዝቡ ይጽናናና ራሱንም ለበለጠ የትንሣኤ ሕይወት ያዘጋጅ ነበር። ምክንያቱም ይህ መገለጥ እግዚአብሔር ለአባታቸው ለአብርሃም የገባውን ቃል ኪዳን እንደማያጥፍ ማሳያ ሆኖአቸዋልና።
 በሰውና በእግዚአብሔር መካከል እርቅ የወረደው ግን ድንግል እናቱን የቃል ኪዳኑ ታቦት አድርጎ ሥጋና ደም ተካፍሎ ሰው ሲሆን ነው። ያኔ በሰውና በእግዚአብሔር በሰውና በመላእክት በሰውና በሰው መካከል የነበረው ጠብ ፍጻሜ አገኘ።  እርቅን ከሰው ጋር በተዋሕዶ ከፈጸመ በኋላ በሰው ልጆች ላይ ሰልጥኖ የነበረውን ዲያብሎስ ከድንግል እናቱ በተካፈለው ሰውነት በመስቀሉ ድል ነሳው። ድል መንሳትንም ለእኛ ሰጠን። ስለዚህ እርቅ የወረደልን ተስፋ መንግሥተ ሰማያት የተሰጠን እርሷንና ሥጋዋን ለራሱ የቃልኪዳን ታቦቱ በማደረግ ስለሆነ ድንግል እናቱን ኪዳነ ምህረት እንላታለን። ምክንያቱም ምህረትና እርቅ ለሰው ልጆች ሁሉ ሆኖአልና። 
እርሱ እግዚአብሔር ቃል ከእርሷ ከድንግል እናቱ ሥጋና ነፍስ ነስቶ ባሕርያችንን ለብሶ በእርሱም ለፍጥረቱ ተገልጦ በእኛ ላይ የተፈረደውን ፍርድ በራሱ ተቀብሎ ዲያብሎስን ድል ነስቶ በእርሱ ያመኑትን እርሱን ተስፋ የሚያደርጉትን ከቅዱሳን መላእክት ጉባኤ ደመራቸው፡፡ ያመኑትንም በጥምቀት እርሱን ለብሰን እንድንነሣ በማድረግ ከቅዱሳን ጉባኤ እንድንደመር አደረገን፡፡ ሰውነታችንን መቅደሱ በማድረግ ሕጉንም በመንፈስ ቅዱስ በልቡናችን ሰሌዳ ላይ ጻፈልን፡፡ እነዚህንና ሌሎች በረከቶችን ሊሰጠን የወደደው ከድንግል እናቱ በነሣው ሥጋና ነፍስ ነበር፡፡ ስለዚህም ድንግል እናቱ መንፈስ ቅዱስ አናግሩዋት “በእኔ ታላቅ ሥራን አድርጎአልና እንግዲህ ትውልድ ሁሉ ብጽዕት ይሉኛል” ብላ ከፍ አድርጋ ተናገረች፡፡ 
ስለዚህ ነው ኪዳነ ምሕረት መባልዋ፤ በእርሷ እርቅ ወርዶአልና። በነቢዩም “ ከዚያ ወራት በኋላ ከእስራኤል ቤት ጋር የምገባው ቃል ኪዳን ይህ ነውና ይላል ጌታ፤ ሕጌን በልቡናቸው አኖራለሁ በልባቸውም እጽፈዋለሁ፤ እኔ አምላክ እሆንላቸዋለሁ እነርሱም ሕዝብ ይሆኑኛል፡፡”(ዕብ.8፡10) የሚለው ቃል በእኛ የተፈጸመው በድንግል ማርያም ነው፡፡ እንዲህም ስለሆነ ቅዱስ ጳውሎስ “እናንተም በሕያው እግዚአብሔር መንፈስ እንጂ በቀለም አይደለም፥ ሥጋ በሆነ በልብ ጽላት እንጂ በድንጋይ ጽላት ያልተጻፈ፥ በእኛም የተገለገለ የክርስቶስ መልእክት እንደ ሆናችሁ የተገለጠ ነው”ብሎ ጽፎልናል፡፡ (2ቆሮ.3፡3)ይህን በማን አገኘነው ብንባል በክርስቶስ ነው፡፡ እርሱ የድንግል እናቱን ሥጋና ደም ሳይካፈል ባይወለድ ኖሮ ይህ የምህረት ቃል ኪዳን በእኛና በክርስቶስ መካከል ባልተፈጸመ ነበር፡፡ እናም አጥርቶ ለመረደት የሚፈለግ ቅድስት እናቱን ኪዳነ ምህረት የማለታችን ዋናው ምክንያት ሰውነቷን የምህረት ቃል ኪዳን ታቦት በማደረግ ከርሷ በነሣው ሥጋ ዓለሙ መዳኑ ነው።

Saturday, May 20, 2017

ምጽዋትና ጥቅሟ በሊቃውንት አባቶቻችን

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
12/09/2009Oዓ.ም

እባካችሁ ከዚህ ጽሑፍ የታዘባችሁትን ጻፉልንኝ

(ከፍትሐ ነገሥት ላይ የተወሰደ)

ምጽዋትስ ከርኅራኄ ወገን ነው፡፡ ይኸውም ሰው በገንዘቡ ምጽዋትን ለሚሹት ሰዎች የሚያደርገው ርኅራኄ ነው፡፡ ከእነርሱ ዘንድ ትርፍ ሳይሻ ጌታችን “ገንዘባችሁን ሽጣችሁ ለድሆች ምጽዋት ስጡ” ብሎ ስላዘዘ ነው “የማይጠፋ ኮረጆ አድርጉ የማይጠፋ የማያልፍ ሰማያዊ ድልብ አከማቹ”(ሉቃ.12፡23) እንዲሁም ዳግመኛም ጌታችን ምጽዋትን ስጡ ሁሉም ንጹሕ ይሆንላችኋል አለ፡፡
ሰው በምጽዋት በሚቻለው መጠን ፈጣሪውን ይመስለዋል፡፡ ምጽዋትና መራራት ከአምላክ የተገኘ ባሕርይ ነውና፡፡ ጌታችንም “እንደ ሰማያዊ አባታችሁ የምትራሩ ሁኑ አለ”(ማቴ.5፡48) ምጽዋትሰ አምላካዊት ብድር ናት፡፡ ይህችውም የታመነችና የምትረባ አምላካዊት ንግድ ናት፡፡ ይህችውም ዳግመኛ ወዶ እስኪወስዳት ድረስ ብልህ ሰው ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያኖራት አደራ ናት፡፡ ይህችውም ዳግመኛ በነባቢት መቅደስ ዘንድ ተቀባይነት ያላት ቁርባን ናት፡፡ እግዚአብሔርም ስም አጠራሩ ከፍ ከፍ ይበልና መሥዋዕትን ያይደለ ምጽዋትን እሻለሁ” አለ”(ሆሴዕ.6፡6፤ማቴ.9፡13) ዳግመኛም ከእርሱዋ ጋር ጾም ተቀባይነት ያለው ይሆናል፡፡ ነቢዩ እንደተናገረ(ኢሳ.58፡6-7)ጸሎትን ከርሷ ጋር ይቀበላል፤ በቆርነሌዎስ እንደተነገረ፡፡ ያለርሷ ድንግልናም አትጠቅምም በአምስቱ ሰነፎች ደናግል እንደ ተጻፈ”(ማቴ.25፡11-12)

Tuesday, May 2, 2017

የሕይወታችን ሁለቱ ጫፎች


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
25/08/2009

በሕይወታችን ጫፍና ጫፍ ያሉ ጊዜአትንና ተፈጥሮአዊ ባሕርያቸውን ሳስባቸው ግርም ድንቅ ይለኛል፡፡ መመሳሰላቸውንም ሳስብ ደግሞ ይበልጥ እደነቃለሁ፡፡ እነርሱም ሕፃንነትና አረጋዊነት ናቸው፡፡ ሁለቱም ከሌላ አካል አካላዊ ድጋፍን የሚሹ ናቸው፡፡ የሁለቱም ፆታ አገልግሎት አይሰጥም፡፡ አንዱ በተፈጥሮ ስላልተዘጋጀ ሌላኛው ግን ተፈጥሮ ራሷ ከአገልግሎት ስላወጣችው ነው፡፡ እናም ሁለቱም በመላእክት ሥርዓት የሚኖሩ ናቸው፡፡ ሁለቱም የእኛ ፈቃድ ሳይጠየቅ በአምላክ የሚፈጸሙ ናቸው፡፡ ነገር ግን አንዱ ወደዚህ ዓለም የሚያስገባ በር ሲሆን ሌላኛው ወደማታልፈው ዓለም የሚያሸጋግር መውጫ  ነው፡፡ ጎዳናቸው ግን አንድ ነው፡፡ አንተ አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ እንዲል ከምድር አፈር ከተበጀ አካል ተወልደን ወደ ቀደምት የአያታችን ማኅጸን ወደ ሆነች ምድር እንገባለን፡፡ ከእርሷም በትንሣኤ ተወልደን ለፍርድ በአምላክ ፊት እንቆማለን፡፡ በሥጋ ከወላጆቻችን ተወልደን በየሰከንዷ በሞት ጎዳና እንጓዛለን፡፡ አንዱ ይቀበላል ሌላኛው ይሸኛል፡፡ አንዱ በባሕርይው ያልተዳደፈ ንጹሕ ሲሆን ሌላኛው ግን ንጽሕናውና ቅድስናው እንደ ግብሩ ይወሰናል፡፡ ዕድሜችንን ሙሉ መልካምን በመሥራት ካሳለፍን በንጽሕናና በክብር ከሕፃንነት እንበልጣለን፡፡ አንዱ ለአዲስ ሕይወት የተዘጋጀ ሲሆን ብዙ ፈተናዎች ከፊቱ ይጠብቁታል፡፡ ሌላኛው ግን በዚህ ዓለም መኖርን አስረጅቷት የሰማያዊውን ሕይወት ጣዕም ማጣጣም የሚጀምርባት ሲሆን የኖረባትም ምድር እርሱን ከአገልግሎት ጡረታ የምታወጣበት ዕድሜ ነው፡፡ እግዚአብሔር ፈቅዶ ለእርጅና ከበቃን  የሞትን ጣዕም በእርጅናችን ማጣጣም እንጀምራለን፡፡ ሞት በአካላችን ሥራውን መሥራት ስለሚጀምር ጉልበታችን ይከዳናል፤ ዓይናችን ይፈዛል፤ ጆሮችን ይደነግዛል፤ አካላችን ይቀዘቅዛል፤ ጠጉራችን ይሸብታል ወይም ይመለጣል፤ ቆዳችን ከአጥንታችን ጋር ይጣጋል፤ ወዛችን ይረግፋል፤ መዓዛችን ይለወጣል፡፡  ያኔ መልካምን ሠርተን እንደሆነ አምላክ ቶሎ ወደ እርሱ እንዲወስደን እንለምነዋለን፡፡ ካልሆነ ግን በነፍስም በሥጋም ስቃያችን ይጨምራል፡፡ ወገኖቼ በእርጅና ሲኦልን በሚመስል ሕይወት ውስጥ ከመኖር ይጠብቀን፡፡