Showing posts with label ቅንጭብጭብ. Show all posts
Showing posts with label ቅንጭብጭብ. Show all posts

Friday, December 20, 2019

ሞትን ማሰብ ደጉ


 በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 

10/04/2012


ወገኖቼ ሞትን ማሰብ ደጉ እንዴት መረጋጋትን የሚሰጥ እሳቤን ይሰጠናል መሰላችሁ፡፡  ሞት ደጉን ስታስቡ በዚህ ዓለም የዘመን ቀመር ነገሮችን መቀመር ታቆሙና ነገሮችን በዘለዓለማዊው ዘመን ቀመር ይህም ትናንት ያይደለ ነገም ያልሆነ ለዘለዓለም አሁን ሆኖ በሚኖር ፀሐይ በማትወጣበትና በማትጠልቅበት በአምላክ ጊዜ ውስጥ ሆኖ አሁን አእምሮአችንን ሰቅዘው የያዙትን በሐሳብም፣ በቃልም፣ በተግባርም ያሉ ነገሮችን የምንመዝነበት ስለሆነ ሞት ደጉን አመስግኑት፡፡ እርሱን ማሰብ ባይኖር ኖሮ መች አምላክን መፍራት፣ ማፍቀር፣ መናፈቅ የዚህን ዓለም መከራ መዘንጋት መታገሥ እንዴት ገንዘብ እናደርጋቸው ነበር? ሞት ማሰብ ደጉ ሁሉን የሚያስተካክል፣ ትሑቱን ከፍ ከፍ የሚያደርግ፣ በትዕቢት የታጀረውን ማንም ሳያሰገድደው የሚያዋርድ፣ ባለሥልጣንንና ጦረኛን የሚያርድ ደፋሩን ፊሪ የሚያደርግ እንደ ሞትን ማሰብ ከቶ ምን አለ? ሞትን ማሰብ በስውር በሚያይ አምላክ ፊት በቅድስና ለመኖር አንቀጽ፣ የእውነተኛ ትሕትና እናት፣ የእውነተኛ ጸሎት መፍለቂያ ምንጭ ነው፡፡ ለዚህች መገኛ የገነት አምሳልነና በሯ ጾም ናት፡፡ አቤቱ አምላካችን ሆይ ሁሌም ቢሆን በፊትህ መሆናችንን እንድናስብ እርዳን፤ በሞት ወደ አንተ በጠራኸን ጊዜ እንዳናፍር በአንተ ዘንድ በጎ የሆኑትን ከማሰብ እስከ መፈጸም አብቃን፤ ወደ አንተም ስትጠራን “ኑዑ ኀቤየ ቡርካኑ ለአቡየ" ብለህ ተቀበለን፡፡    

Tuesday, January 29, 2019

አማልክት ዘበጸጋ



ክብር ለእርሱ ለወደደን ይሁንና እርሱ እግዚአብሔር በእርሱ አርአያና አምሳል የፈጠረውን ሰውን ሊያልቀው በወደደ ጊዜ ከድንግል እናቱ ሞት የሚስማማውን የእኛን ባሕርይ ገንዘቡ አድርጎ ሰው ሆኖ ተወለደ፡፡ ከእርሷ የነሣውንም ሥጋና ነፍስ ባሕርይውን ሳይቀይር አምላክ አደረገው፡፡ በእርሱም በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋዌ  በጸጋ እኛ የእግዚአብሔር አብ ልጆች፣ የእርሱ የጌታችን ወንድሞች የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሕፃናት ሆንን፡፡ በእርሱ በጌታችንም አማልክት ተሰኘን፡፡ ይህን ክብራችንን በትሩፋት ሥራዎች ከደከምን በዓይናችን ለማየት እንበቃለን፡፡ አረጋዊ መንፈሳዊ ከጌታ ጋር መዋሐዷ ስለተገለጠላት ትጉህ ነፍስ ሲጽፍልን፡-

Tuesday, March 21, 2017

ሦስት አጫጭር ጹሑፎች

በዙሪያችን ያሉ መምህራን

አንድ ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ልማር ካለ በዙሪያው የሚያስተምሩት አሉለት። ከዋኖቹና ከማይሳሳቱ ሊሳሳቱ እስከሚችሉት መምህራን በቅደም ተከተል ልንገራችሁ ፥-
የመጀመሪያው መንፈስ ቅዱስ ነው። እርሱ ልጅነትን ከተቀበልንበት ጊዜ አንስቶ መምህራችን ነው። ሁለተኛው ሥጋው ወደሙ ነው። ሥጋው ወደሙን የሚቀብል ሰው ሁሌም ወደላይ ወደ መላእክት ጉባኤ በመነጠቅ ክርስቶስን ወደ ማወቅ ከፍታ እያደገ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ ለሰዎች ሊነገር የማይገባውን ሰምቶ ይመለሳል። ያም ማለት ክርስቶስ ባለበት እርሱ በዚያ ይኖራል። ሌላው ከጠባቂ መላእክት ነው። እነርሱ ከእኛ አይለዩም ስለእኛ በእግዚአብሔር ፊት ይቆማሉ እንድን ዘንድ ያለንን ማስተዋልንንና እውቀትን በመስጠት ይረዱናል። ያዕቆብን በመከራው ጊዜ የተራዳው እርሱ ጠባቂ መልአኩ ነበር። አብርሃምን ያስተማረው ለዳንኤል እውቀትንና ማስተዋልን የሰጠው እርሱ ነው ሌላው  በመንፈስ ቅዱስ መሪነት የተጻፉ መጻሕፍት ናቸው እነዚህ ለአንድ ኦርትዶክስ ክርስቲያን  ከተጠቀመባቸው መምህራኖቹ ናቸው። ከዚያ በኋላ ልንሳሳት የምንችለው እኛ መምህራን እንከተላለን። 
ቢሆንም ግን ክብር ይግባውና የእግዚአብሔርን ድምጽ  እናውቀዋለንና አዲስም ቢሆን ከእግዚአብሔር የሆነውና ያልሆነውን የምንለይበት ሕሊናና መንፈስ ቅዱስ አለን። በዚህ ሁሉ ውስጥ ሆኖ ከእውቀት ባዶ ሆኖ መገኘት ይከብዳል።

Sunday, January 15, 2017

በእውነት ብፅዕት


ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
7/5/2009

ያቺ ቅድስት ብላቴና ንጉሥ እልፍኙ ያደርጋት ዘንድ ሳይፈጥራት ያወቃት፥ ከማኅፀን ሳይሠራት እናቱ ትሆን ዘንድ የነፍሷን ውበት ተመልክቶ የወዳዳት፥ ቤተ መቅደሱ በመሆን የእንስሳት መሥዋዕት የሚሠዋበትን የኦሪቱን ቤተ መቅድስ ልታሳልፍ የ"ቃል" ቤተ መቅድሱ ለመሆን ተመረጠች። በመንፈስ ቅዱስ የከበረች፥ አብ ልጁን ጸንሳ ትወልድ ዘንድ የሚያጸናት ፥ ራሱን ቤተመቅደስ ላለው ቃል ቤተ መቅድሱ ለመሆን የታጨች፥ ወላጅነትን ከአብ ጋር ለመጋራት የተመረጠች፥ መንፈሷ በመንፈስ ቅዱስ በሆነ ደስታ የተሞላ፥ ነፍሷ በአምላኳና በመድኅኒቷ ሐሴት የምታደርግ ፥ በሲኦል ላሉ ነፍሳት  በምድር ላሉ ሙታን የመዳናቸው ተስፋ የነበረችና ናፍቆታቸው የሆነች በእናቷ ሃና እጅ እርጅና ወደ ደቆሳት ቤተመቅድስ ገባች።

Monday, March 16, 2015

አራቱ ልደታት

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 

06/07/2007

የክርስቲያን አፈጣጠሩና እድገቱ እጅግ ግሩም ነው። ልደቱ ፍጥረታዊና መንፈሳዊ ብለን ለሁለት ከፍለናቸው ልንመለከታቸው ብንችልም ሁለትም ሦስትም  መንፈሳዊ ልደታት አሉት። ሁሉም ግን መሠረታዊያን ናቸው።
ሰው ከእናትና ከአባቱ አስቀድሞ ሳይፈጠር መንፈሳዊው ልደት ሊፈጸምለት አይችልም። ስለዚህ ፍቅር በሆነው አምላክ በሥጋ ሰው ሆኖ ሊፈጠር ይገባዋል። ይህ ልደት ግን በቂ ነው አይባልም። ሌላ አባ አባ የሚልበትን ልደት ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ በስመ ሥላሴ ሊወለድ ይገባዋል።
ይህም በራሱ ሙሉ አያደርገውምና አዲስ ለተፈጠረበት ተፈጥሮ ክርስቶስን ወደመምሰል ማደግ ይጠበቅበታል። ይህ ክርስቶስን የመምሰል ደረጃ ሦስተኛ ልደት ይባላል። ይህም ክርስቶስን በተግባር ወደ  መምሰል የመምጣት ሂደት ነው። ወደዚህ መንፈሳዊ ከፍታ  የደረሰ ሰው ላይ ክርስቶስ በእርሱ ይገለጣል።  ሰዎች ሁሉ የክርስቶስን መልክ በእርሱ ላይ ይመለከታሉ። ነገር ግን ደግሞ ሌላ አራተኛ ልደት ያስፈልገዋል። እርሱም በትንሣኤ ለድል አድራጊዎቹ ከክርስቶስ የሚሰጥ ልዩና ዘለዓለማዊ ስጦታ ነው። ክርስቶስ በትንሣኤ ሥጋችንን እንደ ራሱ ሥጋ አድርጎ በመለወጥ ልክ በደብረ ታቦር ወደ አሳየን ክብሩ በማሸጋገር የምንወለድበት ልደት ነው። ይህን ዓይነት ልደትን በምሳሌነት አስቀድሞ በሙሴ አሳይቶን ነበር። እውነተኛውን ልደት ግን በትንሣኤ የእርሱን ሥጋ እንዲመስል አድርጎ ሥጋችንን በመለወጥ ይሰጠናል። ይህን አስመልክቶ ጌታችን በቃሉ "እውነት እላችኋለሁ፥ እናንተስ የተከተላችሁኝ፥ በዳግመኛ ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በሚቀመጥበት ጊዜ፥ እናንተ ደግሞ በአሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገድ ስትፈርዱ በአሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ።"(ማቴ.19:28) ብሎናል። በእውነት እርሱ ለዚህ ክብር የፈጠረን ጌታ ፍቅር የሆነውን ሰውነቱን ለብሰን ለዘለዓለም ስናመሰግነው እንድኖር ያብቃን። ለዘለዓለም አሜን።

Saturday, May 25, 2013

የትኛውን በግ ኖት?


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
17/09/2004


አቤል ቅን ሰው ነበር፤ ነገር ግን እንደ በግ ወደ ዱር በገዛ ወንድሙ ቃየን ተነድቶ ተገደለ፡፡ እንደ አቤል በቃየል የተገደሉ ብዙ ወገኖች አሉን፡፡ በአሁኑ ጊዜ ግን እንደ ቀድሞው አቤል መሆን የሚያዋጣ አይደለም፡፡ በአሁኑ ቃየኖች የሚገደሉ አቤሎች ሞታቸው የነፍስ ሞት ነው፡፡ ቃሉም የሚነግረን አሰናካዩም ተሰናካዩም አብረው እንደሚጠፉ ነው፡፡ በግ እንድንሆን የተጠራን ቢሆንም የትኛውን የበግ ዐይነት መሆን እንደሚገባን ግን ልንለይ ይገባናል፡፡ ሁለት ዓይነት በጎች አሉ፡፡ አንደኞቹ በጎች በእውነት ክርስቶስን የመሰሉ በቀኝ የሚቆሙት ቅዱሳን ናቸው፡፡ እነዚህ በየትም አቅጣጫ እንደቀድሞው አቤል ላታላችሁ ብትሉ አይሳካላችሁም፡፡ ምክንያቱም እነርሱ የሚመሩት በመንፈስ ቅዱስ ነውና፡፡ መንፈሳዊውን ሰው ፍጥረታዊው ሰው ሊመረምረው አይችልም፡፡ ፍጥረታዊው ሰው መንፈሳዊው መረዳት የለውም፡፡ መንፈሳዊው ግን ፍጥረታዊውን ያውቀዋል ይመረምረዋል፡፡ እናም የፍጥረታዊውን የቃየንን አመለካከት የሐዲስ ኪዳኑ አቤል፣ ጌታን የለበሰው ከጻድቃን ሕብረት ያለው በግ ፈጥኖ ይረዳዋል፡፡ ነገር ግን እንደው የጥፋትም በጎች አሉ፡፡ ለእነርሱ ልቤ ያዝናል፡፡ ዳዊት ስለእነርሱ
“ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ አያውቅም እንደሚጠፉ እንስሶች መሰለ፡፡ ይህች መንገዳቸው መሰናክላቸው ናት ከእነርሱም በኋላ የሚመጡ በአፋቸው እሺ ይላሉ፡፡ እንደ በጎች ወደ ሲኦል የሚሄዱ ናቸው እረኛቸው ሞት ነው፡፡”(መዝ.48፡12-14) ይላቸዋል፡፡ እነዚህ በጎች ያሳዝኑኛል፡፡ ለነፍሳቸው እረኛው ሞት ነው፤ ሞትም በቁማቸው ይገድላቸዋል፡፡ መሞታቸውን ግን አይረዱትም እነዚህ እንደ ቀድሞውም አቤል በነፍሳቸው ያልተጠቀሙ ከአዲሶችም አቤሎች ኅብረት የሌላቸው እንደው ሞት የነጋራቸውን ሁሉ አሜን ብለው የሚቀበሉ ናቸው፡፡ አቤቱ ሰውን ሁሉ ሞት ወደ ሲኦል የሚመራው በግ አታድርገው፡፡ ይልቅ አንተን መስለው ሰይጣንን ወደ ሲኦል የሚነዱ አድርጋቸው እንጂ፡፡

Wednesday, February 13, 2013

መንፈሳዊ እድገትና ተሃድሶ ይለያያሉ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
07/06/2005
 መንፈሳዊ እድገት ማለት ታድሶ ማለት አይደለም፡፡ እኛ እኮ በክርስቶስ ታድሰን አዲሱን ሰው ክርስቶስን ለብሰናል ወይም ልክ እንደሙሉ ሕጻን አንድ ጊዜ ተወልደናል፡፡ የመጠን ያም ማለት የብስለት ለውጥ እንጂ የመልክ ወይም የማንነት ለውጥ የለንም፡፡ አሁን መልካችን ክርስቶስን መስሎአል በአዲስ ማንነት ደግሞ በሰማያዊ ልደት ተወልደናል፡፡ ከዚህ በኋላ ከእኛ የሚቀረው መንፈስ ቅዱስ በሚሰጠን ማስተዋል እየበሰልን ሙሉ ሰው ክርስቶስን ወደ መምሰል ማደግ ነው፡፡ የቤተክርስቲያንም ድርሻ መንጋዋን ዳግም በክርስቶስ ለተፈጠረበት መንፈሳዊ ከፍታ ማብቃት ነው፡፡ እርሱዋ ለልጆቹዋ እንደ እናት ናት፡፡
በእርሱዋ የተሟላ የሐዋርያትና የነቢያት ትምህርት አለ፡፡ በእነርሱ ውስጥ በጥምቀት ባደረውም መንፈስ ቅዱስ ክርስቶስን መስለው እንዲያድርጉ እንደየእድገታቸው መጠን ትመግባቸዋለች፡፡ መታደስ ማለት ይህን በአዲስ ተፈጥሮ በክርስቶስ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቀን አዲሱን ሰው ለብሰን የተፈጠርንበት ማንነታችን አርጅቶ እንደገና ወደ አዲስ ማምጣት ማለት አይደለም፡፡ እኛ እድሳታችን የተፈጸመው ልክ በመንፈሳዊ ልደት በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቀን የእግዚአብሔር ልጆች ስንሆን ነው፡፡ ልጅ ከሆንን ደግሞ ቀስ በቀስ ማደግ አለብን፡፡ ይህም ከፍጹምነት ወደ ፍጹምነት ማለት ነው፡፡ ወይም ከሚበልጠው ወደ ሚበልጠው የመንፈሳዊ ብስለት ማደግ ነው ለዚህም ማለቂያ የለውም፡፡
 መንፈሳዊ ወተትን የሚጋቱ ሕጻናት አሉ ወተቱ ለእነርሱ መሠረታዊና እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ነገር ግን ጥርስ ባወጡ ጊዜ ጥሬን ወደ መቆርጠም አጥንትን ወደ መጋጥ ሲመጡ ጠንካራውን መንፈሳዊ ምግብምን ሊመገቡ ይገባቸዋል፡፡ በዚህም ውስጥ አንዳች ነውርም የለበትም፡፡ ነገር ግን በዚህ ብቻ አያቆምም በመንፈሳዊ ከፍታ ልንሸመግል ይገባናል፡፡ ያም ማለት ለመንፈሳዊ ትምህርት የመጀመሪያ የሆነውን ትምህርት አውቀን(ወተት) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሰፈሩትን እውነታዎች በጥልቀት ተረድተን(ጠንካራውን ምግብ) ሙሉ ሰው በመሆን በመንፈስ ቅዱስ ወደ መመራት መድረስ መምጣት አለብን፡፡ ይህ ሁሉ ጤናማና በውስጡ አንዳች ነውር የሌለበት አካሉ በራሱ ሙሉ እንደሆነ የሚያድግበት መንፈሳዊ እድገት ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ግን በራሱዋ ሙሉ ናት ልጆቹዋን እነዚህን እየመገበች ታሳድጋቸዋለች፡፡ እንጂ በራሱዋ አትታደስም ቤተክርስቲያን ጥንትም ነበረች አሁንም አለች ወደፊትም ትኖራለች ምክንያቱም መሥራቹዋ ክርስቶስ መጋቢዋም መንፈስ ቅዱስ ዘለዓለማዊያን ናቸውና፡፡   

Monday, January 14, 2013

ክርስትና ለእኔ እና እኔ አልስማማም እንዲሁም….



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
07/05/2005
ለእኔ ክርስትና ማለት ምን ማለት ነው ቢሉኝራስ መሆንብዬ እመልሳለሁ፡፡ በምን ሲባል ከኃጢአት በቀር በሁሉ ብዬ እመልሳለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ዕረፍት አለን፡፡ ክርስትና ድህነት ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን ስለፍቅርና ስለቅንነት እኛ ያለንን እንደ ችሎታችን የጠየቁንን ስለምንሰጥ ለሥጋዊው ድህነት የቀረብን ነን፡፡ ቢሆንም በሥራ ያን ጉድለት እንደፍነውና ለምጽዋት እጃችንን እንዘጋለን፡፡ ነገር ግን ለሁሉ ማለትም ለምድራዊውም ለሰማያዊውም ሀብታችን ምንጩዋ ቤተክርስቲያን ብትሆን መልካም ነበር፡፡ በእርሱዋ በኢኮኖሚም ሆነ በሥነ ልቡና የደከሙት ተጠነካክረው ለዓለም እንደ ብርሃን በመሆን በእነርሱ መልካም ሥራ የእግዚአብሔር ስም ሊመሰገን ይገባው ነበር፡፡

Sunday, January 6, 2013

“በአፉ መሳም ይሳመኝ”



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
28/04/2005
በአፉ መሳም ይሳመኝ ፍቅርህ ከወይን ጠጅ ይልቅ መልካም ነውና፡፡”(ማኃ.1፡1) የሚለው ቃል በይሁዳ ቤተልሔም እነሆ ተፈጸመ፡፡ ይህ ቃል ከእግዚአብሔር ዘንድ ለሰዎች የሚሰጠውን  ሰላምና ፍቅር እንዲሁም እርቅ የሚናፍቁ የነቢያትና የቅዱሳን የናፍቆት ቃል ነበር፡፡ “በአፉ” ሲል “በእግዚአብሔር ቃል” ሲለን ሲሆን “ይሳመኝ” ሲልም የእግዚአብሔር ቃልን ሰው መሆን መናፈቃቸውን የሚናገር ነው፡፡ እንዲህ ካልሆነ እንዴት በአፉ ሊስመን ይቻለው ነበር? ይህ ቃል እርቅ በሰዎችና በእግዚአብሔር መካከል መፈጸሙ የማይቀር መሆኑን የሚያውጅ የናፍቆት ቃል ነው፡፡

Tuesday, January 1, 2013

የፍጥረት ሁሉ ናፍቆት እነሆ ከሴት ብቻ ተወለደ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
24/04/2005
የፍጥረት ሁሉ ናፍቆት የሆነውን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በዐይነ ሥጋ ለማየት ዘመነ ዘመናት ተቆጥረው ለልደቱ 15 ዓመታት ሲቀሩት በቅድስት ድንግል ማርያም እድሜ የልደቱ ዘመን ተካቶ ተቆጠረ፡፡ የሰው ልጆች ሁሉ የድኀነትን ቀን ናፍቀው ዐይኖቻቸው በዚህች ድንግል ብላቴና መወለድና ማደግ ላይ ትኩረታቸውን አድርገው ነበር፡፡
እነሆ ከላይ ከአርያም የምስራቹ ቃል በመልእክተኛው በመልአኩ በቅዱስ ገብርኤል ወደ ቅድስት ድንግል ማርያም መጣ፡፡ እርሱዋም “እነሆኝ የጌታዬ ባሪያ እንደ ቃልህ ይደረግልኝ” ብላ በድንግልና ጸንሳ ዘጠኝ ወር በማኅፀኗ ተሸክማ በድንግልና ወለደችው፡፡ እረኞች የእረኞችን አለቃ ተመልከተው ደስ አላቸው፡፡ ሰብአ ሰግል በደስታ ለአምላክ የሚቀርበውን ወርቅ እጣን ከርቤ አቀረቡለት በፊቱም ወድቀው ሰገዱለት፡፡ መላእክትም “ስብሐት ለእግዚአብሔር ሰማያት ወሰላም በምድር ስምረቱ ለሰብእ” እያሉ አመሰገኑ ሰማያውያን ከምድራውያን ጋር ምስጋናን አቀረቡ፡፡ ፍጥረት ሁሉ በደስታ ሰከረ፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያምም በቀደሞይቱ ሔዋን ምትክ የሕያዋን ሁሉ እናት ሆነችልን፡፡ እኛም በጥምቀት እርሱን በመልበስ የእርሱ ወንድሞችና እኅቶች ተባልን፡፡ በእርሱም የቅድስት ድንግል ማርያም ልጆች ተሰኘን፡፡ ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ስምረቱ ለሰብእ ሃሌ ሉያ!!!

Thursday, September 6, 2012

women's Image and likeness



by shimelis mergia
1/13/2004
Let us always see ourselves in the mirror of Christ and, walk under the guidance of His will that we have learned from His face. His face is love, purity, holiness, kindness, justice and merciful. Purify your entire personality, in the image of Him. Don't look at others mortal face, which introduces all carnal things.
If you always look to His face, you do not Judge on others but, you love them and give an honor as your elder brothers, sisters, father and mother.
Do you know that women are the representative figures of God's Especially, for God the Word Oh women! . We Christian were born from Him. He feeds us from his breast, the milk of Spirituality and  like hen which protects her chickens from eagle by hiding with its wing, He also protects us from the eagle of devil hiding in His merciful wings.

Tuesday, August 14, 2012

እናንተስ ምን ትላላችሁ?

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

08/12/2004

አንባቢው እዚህ ላይ እንዲያስተዋልልኝ የምፈልገው ነገር ቢኖር በሐዲስ ኪዳን ክብር ይግባውና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንዴ በመስቀሉ በፈጸመው የድኅነት ሥራ እኛ በጥምቀት ስንተባበርና የተሰጠንን የልጅነት ጸጋችንን ጠብቀን ስንገኝ የምንድን መሆናችንን ነው፡፡ ድኅነቱ አሁን ተሰጥቶናል፡፡ የመዳንና ያለመዳን ምርጫው የተያዘው በእኛው እጅ ነው፡፡  ስለዚህም አንዴ በተቋጨና በተደመደመ ጉዳይ ዙሪያ ነው የምንነጋገረው፡፡ በመሆኑም ይህን ጽሑፍ ሳቀርብም ለእውቀት ያህል ብቻ እንደሆነ አንባቢው እንዲረዳኝ በትሕትና እጠይቃለሁ፡፡    


ነቢዩ ዳዊት ኃጢአት ከእናት ማኅፀን እንደሚጀመር ሲጽፍልን “ኃጥአን ከማኅፀን ጀምረው ተለዩ፤ ከሆድም ጀምረው ሳቱ፤ ሐሰትንም ተናገሩ፡፡”ሲለን(መዝ.57፡3-4) ኢዮብ ደግሞ ሕፃናት ገና ከማኅፀን ሳሉ ጽድቅን እንደሚጀምሩ ሲናገር “ደሃውን ከልመና ከልክዬ፣ የመበለቲቱን ዓይን አጨልሜ እንደሆነ፤ እንጀራዬን ለብቻዬ በልቼ እንደ ሆነ፣ ደሃ አደጉም ደግሞ ከእርሱ ሳይበላ ቀርቶ እንደ ሆነ፤ እርሱን ግን ከታናሽነቱ ጀምሬ እንደ አባቱ ከእኔ ጋር አሳድጌው ነበር፡፡ እርሱዋንም ከእናቴ መኅፀን ጀምሮ መራኋት”አለን፡፡(ኢዮ.31፡16-18)


Saturday, August 11, 2012

ግሩም ድንቅ የሆነው ተፈጥሮ!!!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊ
06/12/2004
በመንፈሳዊው ዓለም ሴት ልጅ ላስተዋላት ከገነትም ይልቅ የምትረቅ ናት፡፡ እኔ ስለሴት ልጅ ሳስብ በአግርሞት እሞላለሁ፡፡ አንድ ወቅት እግዚአብሔርን እንዲህ ብዬ ጠየቅሁት፡- ስለምን ነፍስን ለብቻዋ አልፈጠርካትም ? ስለምን ሥጋን ማኅደሯ አድርገኽ ፈጠርካት ?አልኹት፡፡ ለካ የነፍስ መዳኗና አምላኩዋን የማየቱዋ ምክንያት ሥጋ ነበረች!!! ይህም የተፈጸመው በሴት ልጅ በኩል ነው፡፡ ከእርሱዋ ክርስቶስ ከአጥንቱዋ አጥንት ከሥጋዋም ሥጋ  ሆኖ በአካል ተገለጠ፡፡ ስለዚህም ለእርሱ ከአጥንቱ አጥንት ከሥጋው ሥጋ ስለሆነች ሴት ተባለች፡፡ ሴት ማለት ደግሞ ክፋዬ ማለት ነው፡፡ ክርስቶስ ከቅድስት ድንግል ማርያም የአዳምን ባሕርይ ነስቶ በመወለድ የእርሱዋ ክፋይ(ልጅ) ሲባል እኛ ደግሞ ከእርሱ ከክርስቶስ ከአጥንቱ አጥንት ከሥጋው ሥጋው በመሆን የእርሱ ክፋዮች(ልጆች) እንባል ዘንድ በጥምቀት ከሞቱ ጋር ተባበርን፡፡ 
ሴቶች በሔዋን ሴት ሲባሉ፡፡ እኛ ወንዶች ደግሞ በክርስቶስ በተመሰለውና የአቤል ምትክ በሆነው ሴት በኩል ሴት ተባልን፡፡ ይህ ደግሞ ድንቅ ነው!!! 
ታዲያ ስለምን ሴት ልጅ ከነስሙዋ ድንቅ የሆነች ፍጥረት አትባል? ጥበብን የሚወድ እግዚአብሔር ሴት ልጅን የፍጥረት ጉልላት አድርጎ ፈጠራት፡፡ ከእርሱዋም ስሙ ጥበብ የሆነ ክርስቶስ ተወለደ፡፡ በክርስቶስም እኛ ክርስቲያኖች በጥምቀት ከአጥንቱ አጥንት ከሥጋው ሥጋ በመሆን ተወለድን፡፡ 
አዲሱም አፈጣጠራችን ሔዋን ከአዳም የተገኘችበትን አፈጣጠር ይመስላል፡፡ አዳም አንቀላፍቶ ሳለ ሔዋን ከጎኑ አጥንት ተገኘች፡፡ እንዲሁ እኛም ክርስቶስ በሞት እንቅልፍ አንቀላፍቶ ሳለ ከጎኑ በፈሰሰው ደም ተዋጅተን ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ ነጽተን ዳግም ተፈጠርን (because we are members of His body of His flesh and His bones) እንዲል፡፡(1ቆሮ.12፡27) ታዲያ በመንፈሳዊ መረዳት ውስጥ ያለ ሰው እንዴት በሴት ልጅ ተፈጥሮ  አይደነቅ?

ከ20 በላይ የሆኑ መንፈሳዊ ጉራማይሌ አጫጭር ጽሑፎች




በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/12/2004
(እነዚህ ጽሑፎች በተለያዩ ጊዜአት ፖስት ያደረጉኋቸው ናቸው)
ክርስትናና ፍቅር የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች
ፍቅርን የማያውቃት ክርስትናንም አያውቃትም ፡፡ ፍቅርን ሳያውቃት ክርስትናን አውቃታለሁ የሚል ሰው በእውነት እርሱ ሐሰተኛ ነው፡፡ በፍቅር ውስጥ ላለ ሰው ክርስትና ትፈቀራለች እንጂ አትከብድም፡፡ ክርስትና በፍቅር ውስጥ በሚገኝ ማስተዋል የምትመራ፣ የማታሰለች፣ ሁሌም ጥበበኛ የሆነች፣ ርኅሪት፣ ታጋሽ፣ አዛኝ፣ ሰው በሰው ማንነት ውስጥ ሆኖ ሰውነቱን እንዲያጣጥም የምትረዳ፣ ውስጡዋ ሰላም፣ ፍስሐ፣ ፍጹም ፍቅር የሞላባት፣ በተመስጦ የምታኖር የሰው ሰውነት ትርጉም ናት፡፡So let's build our faith on these, let's open our eyes with love and see all human beings with kindness. Don’t judge on others but appreciate their good deeds. Help each other without reward. In order to have pure mind, excellent thinking and healthy perspective, let us know God our lover and love all human beings on the eyes of God and love each other sincerely. Not in word but in deed.

ብሔርተኝነት
ክርስትና ዓለማቀፋዊት ናት ማንም በየትም ሀገር ይሁን ወደ እውነተኛይቱ የእግዚአብሔር መንግሥት በጥምቀት ከገባ በኋላ ክርስቲያን እንጂ የዚህ ሀገር የዚያ ሀገር አይባልም፡፡የተጠመቀ ሁሉ አንድ አካል ሆኖአል፡፡ የአንድ ሰማያዊት ሀገር ዜጋ ነው፡፡ለክርስቶስ ደግም አንዱ የአካል ክፍል ነው፡፡ይህን ቅዱስ ጳውሎስ ሀገራችን በሰማይ ነው ብሎ ይገልጽልናል፡፡ እጅ የምትሠራውን እግር አይሠራውም ዐይን የምትሠራውን ጆሮ አትሠራውም፡፡ ነገር ግን የአንዱ የአካል ክፍል ተግባር ሌሎችን የአካል ክፍሎች በአግባቡ እንዲኖሩ ያደርጋቸዋል፡፡ ስለዚህ ብሔርተኝነት በክርስትና አይሠራም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ነው ያስተማረን፡፡ በአንድ እምነት ውስጥ ካለን የሌሎች እውቀትና ልምድ ለእኛ የጎደለንን ሲሞላልን የእኛ ደግሞ የሌሎችን ጉድለት ይሞላል፡፡ ስለሆንም በዓለም አቀፍ ደረጃ በአንድ እምነት ሥር ያለን እርስ በእርሳችን ካልተመጋገብን ክርስትናን ኖርናት አያስብለንም አካለ ጎደሎዎች ነን እንጂ፡፡ ወገኖቼ ሆይ ብሔርተኞች አንሁን(Nationalist) ክርስትና ዓለማቀፋዊት ናት፡፡ ዓለማቀፋዊት የሆነችውን ብሔራዊት የምናደርጋት ከሆነ ራሳችንን ብንጎዳ እንጂ አንጠቀምም፡፡ ምክንያቱም ብሔርተኝነት በራሱ ምንፍቅና ነውና፡፡