Friday, January 6, 2017

የዕብራውያንን መልእክት እንዲህ እንረዳው? መቅድም

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ቀን 28/04/2009)

ክብር ይግባውና ሥላሴ በፍቅር ሸንጎው ስለ ሰው ልጆች መዳን ምክርን መከረ፡፡ ሰው በድሎአል አሳዝኖናልም ቢሆንም አርዓያችን ነውና ፈጽመን ልንጥለው አይገባንም  አለ። በመቀጠል “አዳም ከእኛ እንደ አንዱ ይሆናል” ለጊዜው ግን ከእኛ ርቆ ይኖራል ብሎ ወሰነ፡፡ ምክራቸውንም እውን ለማድረግ ዘመን የማይቆጠርለት ሥላሴ ቀን ቆረጠ፡፡ በአርዓያውና በአምሳሉ የፈጠረውን የሰውን ልጅ ቤተሰብ ሊያደርግና ከወደቀበት ሊያነሣው እንዲሁም በእሪናው ሊያስቀምጠው ወልድ በፈቃዱ ሰው ሆነ፡፡
እርሱም ከአምላክነት እሪናው ሳይለይ ከቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ተገኘ፤ ሥጋና ነፍስ ነሥቶ ከጸጋ ተጓድሎ ደህይቶና ጎስቁሎ የነበረውን የሰውን ባሕርይ ገንዘቡ በማድረግ ሁሉን ወራሽ አደረገው፡፡ ከሥጋዌ በፊት የአብ የሆነ ሁሉ የወልድ ነበር የወልድ የሆነ ሁሉ የአብ ነበር፡፡ ይህ ሥጋ በመሆኑ የቀረ አልነበረም፡፡ ይልቁኑ የቃል የሆነ ሁሉ የሥጋ በመሆኑ ምክንያት ቃል ሥጋን ሁሉን ወራሽ አደረገው፡፡
በዚህ ግን ቃል ብቻ ሳይሆን አብም መንፈስ ቅዱስም ሥጋን ሁሉን ወራሽ አድርገውታል፡፡ አብ በማጽናት መንፈስ ቅዱስ በመክፈል ወልድ በመዋሐድ እኩል ተሳትፎ ነበራቸው፡፡ ስለዚህ ሥጋን የእግዚአብሔር ቃል የሆነውን ሁሉ ገንዘቡ እንዲያደርግ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ እኩል ሚና ነበራቸው፡፡  ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ አብን ርስት ሰጪ በማድረግ ስለ ክርስቶስ “ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን” ማለቱ፡፡