Monday, April 2, 2012

ጦምን እንዲህ ብንረዳውስ?


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
25/07/2004
ምግብ ለሰው ልጆች በሕይወት መቆየት መሠረታዊ ነገር ሆኖ መቆጠር የጀመረው ከውድቀት በኋላ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ግን እንዲያ  አልነበረም፡፡ የቀደመው የአዳምና የሔዋን ሕይወት ምን ይመስል እንደነበር በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መረዳት እንችላለን፡፡ እርሱ ምንም እንኳ የእኛን ተፈጥሮ ገንዘቡ ያደረገ ቢሆንም እንዲያ በመሆኑ ምክንያት ልክ እንደ እኛ በሕይወት ለመቆየት ምግብ አላስፈለገውም፡፡ እንዲህ ስል ግን የእርሱን አምላክነት ዘንግቼው ሳይሆን የአዳምና የሔዋን በገነት የነበራቸውን ሕይወት ለማስረዳት ከእርሱ የተሻለ ማሳያ ስለሌለ ነው፡፡
አዳምና ሔዋን ከውድቀት በፊት በገነት ሳሉ በገነት ካሉ ፍራፍሬዎች ይመገቡ ነበር እንጂ በሕይወት መቆየታቸው በእነርሱ ላይ የተመሠረተ አልነበረም፡፡ ነገር ግን ከውድቀት በኋላ ሕይወታችን ከሆነው በአፍንጫችን እፍ ተብሎ ከተሰጠን መንፈስ ቅዱስ ስለተለየን መጽናናታችንና በሕይወት መቆየታችን በምግብ ላይ ተመሠረተ ሆነ፡፡