Saturday, March 31, 2012

ለአንድ ክርስቲያን የሰንበት ትርጉም


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
23/07/2004
አንድ ቅዱስ ሰንበትን ግርዘት ብሎ ይጠራታል፡፡ አንድ ጊዜ የተገረዘ ሰው ድጋሚ መገረዝ እንደማያስፈልገው እንዲሁ አንድ ጊዜ የተጠመቀም ድጋሚ መጠመቅ አያስፈልገውም፡፡ ስለዚህ ግርዘት የጥምቀትም ጥላ ነው ማለት ነው፡፡ በእርግጥ ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህ ሲያስረዳ “የሥጋን ሰውነት በመግፈፍ በክርስቶስ መገረዝ በእጅ ባልተደረገ መገረዝ በእርሱ ሆናችሁ ደግሞ ተገረዛችሁ”(ቆላ.2፡11)ይለናል፡፡
የተጠመቀ ደግሞ ከክርስቶስ ጋር በሞቱ በመተባበር የቀድሞውን አዳም ቀብሮ ዳግማዊውን አዳም ክርስቶስን ለብሶ ይነሣል፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው ሲጠመቅ “የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሊለብስ ይገባዋል” የሚለው የሐዋርያው ቃል በእርሱ ተፈጸመ ማለት ነው፡፡(1ቆሮ.15፡45፣52) ትንሣኤአችን ግን የሚተገበረው እኛ በዚህ ምድር ሳለን እንደ ክርስቶስ ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ ሕያዋን ሆነን የተመላለስን እንደሆነ ብቻ ነው፡፡