Monday, February 27, 2012

ዕንቁ፣ ክርስቶስና ኢትዮጵያ በቅዱስ ኤፍሬም




ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
20/06/2004
መግቢያ
ለቅዱስ ኤፍሬም አንድ ወቅት ደቀመዛሙርቱ ዕንቁ ያመጡለታል፡፡ እርሱም ዕንቁውን በተመለከተ ጊዜ ሰማያዊ ምስጢር ተገለጠለት፡፡ ስለዚህም በዕንቁ ነገረ ሥጋዌውንና በጥምቀት ያገኘነውን ክብር ሰበከ፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም ዕንቁን መሠረት አድርጎ ሰባት መዝሙራትን የደረሰ ሲሆን ከእነዚህ ድርሰቶቹ ውስጥ ለአሁኑ ስለኢትዮጵያና ስለንግሥት ሳባ እንዲሁም ስለኢትዮጵያዊው ጃንደረባ የሚያወሳውን ሦስተኛውን መዝሙር ወደ አማርኛ መልሼዋለሁ፡፡

አንተ ዕንቁ ሆይ! ሰውነትህ ከልብስ የተራቆተ ነውና ራስህን መሰወር እንዴት ይቻልሃል? ነጋዴዎች አንተን ከማፍቀራቸው የተነሣ ከልብስ ተራቆቱ፤ ነገር ግን እነርሱ ከልብስ መራቆታቸው የአንተን ራቁትነት በልብሳቸው ለመክደን ሲሉ አልነበረም፡፡ አንተ ምንም እንኳ ከልብስ የተራቆትክ ብትሆን ከውስጥህ ሚፈልቀው ብርሃን ልብስህ ነው፤ መጎናጸፊያህም የብርሃኑ ነጸብራቅ ነው፡፡ ኦ አንተ ዕንቁ ሆይ! ግሩም የሆነው ባሕርይ እንዴት ድንቅ ነው!!
ከስህተት በፊት ሔዋን በገነት ሳለች ምንም እንኳ ከልበስ የተራቆተች ብትሆንም ልክ እንዳንተው ብርሃንን የተጎናጸፈች ውብ ነበረች፡፡ ከዚህ ልብሱዋ ያራቆትካት አንተ ሰይጣን ሆይ ርጉም ሁን፡፡ ጌታ ሆይ! ዕንቁው ያንተ ምሳሌ ነው ፤ አንተን ግን ይህ ሰይጣን ከዚህ ልብስህ ሊያራቁጥህ አይቻለውም፡፡ አሁን በገነት ሴቶች እንደዚህ ዕንቁ ብርሃንን ተጎናጽፈው የቀድሞዋን ሔዋንን መስለዋታል፡፡



Sunday, February 26, 2012

"ሕይወትም ቢሆን ሞትም ቢሆን..."


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
19/06/2004
እግዚአብሔር አምላካችን የፍጥረት ቁንጮ የሆነውን እኛን በሞትና በሕይወት ምሳሌ ፈጠረን፡፡ አዳምን በሞት ሔዋንን ደግሞ በሕይወት ምሳሌ ፈጠራት፡፡ እኛ ዘር እንሰጥና እሩጫችንን ስናበቃ ሴት ልጅ ግን በአካልዋ ውስጥ ለሰጠናት ዘር ሕይወትን በመስጠት ሕይወትን ትቀጥላታለች፡፡ እኛ ወንዶች ከሴቶች ይልቅ ሞትን ማሰብ በውስጣችን ስላለ የልጆቻችን ቀጣይ ሕይወት ሲያሳስበን ሴትን ልጅ ግን ሕይወት በእጁዋ ስለሆነ  ዕለታዊው የሆነው ነገር ያስጨንቃታል፡፡
 እኛ ወንዶች ዘርን ሰጥተን በሕሊናችን ይህችን ዓለም አሳልፈናት ስንሰናበታት፤ ሴት ልጅ ግን ለዚህች ዓለም ሕይወትን ሰጥታ ሕያዋን ልጆችን በመውለድ ዳግም እኛን በልጆቻችን ሕያዋን በማድረግ ሕይወትን እንድንኖራት ታደርገናለች፡፡ እኛ ሞትን አስበን ራእይን ለልጆቻችን ስናሰንቃቸው፤ ሴት ልጅ ግን ሞት በእርስዋ ውስጥ አይታሰብምና ለእነርሱ በሕይወት መቆየት ትታትራለች፡፡
ሞትና ሕይወት ፈጽመው የሚጣጣሙ ባይሆኑም እግዚአብሔር አምላክ አጣጥሞ ያውም በእኛ ተፈጥሮ ውስጥ ገለጣቸው፡፡ አዳም በሞት አርአያ አንቀላፍቶ ሳለ ሔዋንን አስገኛት፡፡ እርሱዋም ምድሪቱን ከእርሱ ባገኘችው ዘር በሕይወት ሞላቻት፡፡ ክርስቶስ ኢየሱስም በሞቱ ቤተ ክርስቲያንን መሠረታት፤ እርሱዋም ከእርሱ ባገኘችው ዘር መንፈስ ቅዱስ ምድርን በሕያዋን ልጆቿ ከደነቻት፡፡
ጌታችን የሞት ምሳሌ የሆነውን የአዳምን ተፈጥሮ በሞቱ ሲያከብረው የሕይወት ምሳሌ የሆነውን የሴትን ተፈጥሮ ደግሞ በትንሣኤው አከበረው፡፡ ስለዚህም ለእኛ ለክርስቲያኖች ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው በዚህ ምድር መኖራችን  ጥቅም ነው፤ ከዚህ ዓለም ተለይተን ከክርስቶስ ጋር መኖርም ለእኛ እጅግ መልካም ነው፡፡(ፊል.1፡23-24) ለዚህም ይሆናል ይህ ሐዋርያ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች “ሁሉ የእናንተ ነው” ካለ በኋላ “… ዓለምም ቢሆን ሕይወትም ቢሆን ሞትም ቢሆን ያለውም ቢሆን የሚመጣውም ቢሆን ሁሉ የእናንተ ነው እናንተም የክርስቶስ ናችሁ ክርስቶስም የእግዚአብሔር ነው”ማለቱ፡፡(1ቆሮ.3፡22-23)ድንቅ ነው!!!  

አጋፔ (Agape)



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
18/06/2004
(ስብከት ወተግሣጽ ከሚለው መጽሐፌ ተወስዶ የተብራራ)
ቃሉ ግሪክ ቃል ነው፡፡ ትርጉሙም ክርስቲያናዊ ፍቅር ``Charity`` (1ኛ ቆሮ 131-8) ማለት ሲሆን ይህ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀሉ የተገለጠ ፍቅር ነው፡፡ ቅዱስ አግናጥዮስ ዘአንጾኪያ ቅዱስ ሂፖሊተስ አጋፔን ከቅዱስ ቁርባን ጋር አገናኝተው ያስተምሩታል፤ መጽሐፉም ይህንን ይደግፋል፡፡ ይሁዳ ቁ.12 ላይ “በፍቅር ግብዣችሁ”ሲል ክርስቲያናዊ ፍቅርንና ቅዱስ ቁርባኑን በአንድነት አጣምሮ ሲገልጠው ነው፡፡ “ፍቅር” ያለው አጋፔ የተባለው ክርስቲያናዊ ፍቅርን ሲሆን “ግብዣችሁ” የተባለው ቅዱስ ቁርባኑ ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ በእሑድ ወይም በስምንተኛው ቀን ይመሰላል፡፡ የክርስቲያን እሑድ እንደ ስምንተኛው ቀን ይቆጠራል፡፡ ምክንያቱም እሑድ የቀናት መጀመሪያ ናት፡፡ ክርስቲያን ደግሞ በክርስቶስ አዲስ ፍጥረትና በኩር ስለሚሆን ብኩርና ያገኘባት ያች ቀን ለእርሱ እንደ እሑድ ቀን ናት፡፡
ይህ ክርስቲያን በጥምቀቱ ከዚህ ዓለም እያለ በላይ በሰማያት ከትመው ከሚኖሩት ከቅዱሳን ነፍሳትና ቅዱሳን መላእክት ጋር መኖሪያውን ያደርጋል፡፡ እነርሱ ከምድራዊ ሥርዐት ውጪ እንደሆኑና ምድራዊው የሆነው የቀን ቀመር እንደማያገለግላቸው እንዲሁ ለዚህም ክርስቲያንም በአዲስ ተፈጥሮው ከእነርሱ ጋር ማኅበርተኛ ሆኖአልና ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “እንግዲህ የሰንበት ዕረፍት ለእግዚአብሔር ሕዝብ ቀርቶላቸዋል፡፡ ወደ ዕረፍቱ የገባ እግዚአብሔር ከሥራው እንዳረፈ እርሱ ደግሞ ከሥራው አርፎአልና፡፡”(ዕብ.4፡9-10)እንዳለው ለእርሱም የቀን ቀመርና አቆጣጠር አያስፈልጉትም፡፡ ይህን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲያብራራው “ነገር ግን ወደ ጽዮን ተራራና ወደ ሕያው እግዚአብሔር ከተማ ደርሳችኋል፤ ወደ ሰማያዊቱም ኢየሩሳሌም በደስታ ወደ ተሰበሰቡት ወደ አእላፍት መላእክት ፣ በሰማያትም ወደ ተጻፉ ወደ በኩራት ማኅበር የሁሉም ዳኛ ወደሚሆን ወደ እግዚአብሔር ፤ፍጹማንም  ወደ ሆኑት  ወደ ጻድቃን መንፈሶች፤ የአዲስ ኪዳን መካከለኛ ወደሚሆን ወደ ኢየሱስ ከአቤልም ደም ይልቅ የሚሻለውን ወደሚናገረው ወደ መርጨት ደም ደርሳችኋል” ብሎናል፡፡ (ዕብ.11፡22-24)


Friday, February 24, 2012

ሠዓሊት በተፈጥሮ


ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
16/06/2004

እግዚአብሔር አምላክ ሴትን ልጅ ጥበብን የምትወድ ሠዓሊት አድርጎ ፈጠራት፡፡ ስለዚህም ውስጣዊውንና ውጫዊውን የሰውነት ክፍሎቹዋን እንደ ሸራ በመጠቀም ልታስተላለፍ የምትፈልገውን መልእክት በሰውነቱዋ ሸራ ላይ ትሥልልናለች፡፡ እኛም ወንዶች ደግሞ አድናቂዎቿና ተማሪዎቿ ነን፡፡ ባለን እውቀት ላይ ተጨማሪ እውቀቶችን ከእርሱዋ እንጨምራለን፡፡ እንዲህም ስለሆነ እነርሱ ሁል ጊዜ በሕሊናቸው የሚመላለሰውን በጎም ይሁን ክፉ አሳብ በሰውነታቸው ሸራ ላይ ለመሣል ሲተጉ እኛ ወንዶች ደግሞ ሥዕላቸውን አይተን ለማድነቅና ለመማር እንተጋለን፡፡ እነርሱ ልክ እንደ ሠዓሊ በዝምታ መልእክታቸውን በሰውነታቸው ሸራ ላይ ሲያስተላለፉ፤ እኛ ደግሞ በዝምታ የጥበብ ጥማችንን ስናረካና ከመልእክቶቻቸው ስንማር እንገኛለን፡፡
ይህን ግን ምናልባትም ዘመኑ የተረዳው አይመስለኝም፡፡ ሴትን ልጅ አታጊጪ ብሎ መከልከል አንድ ሠዓሊን አትሣል ብሎ እንደ መከልከል ይቆጠራል፡፡ ሠዓሊን አትሣል ብለን ብሩሹንና ሸራውን ልንቀማው እንችላለን፡፡ ሴትን ልጅ ግን አትሣዪ ብሎ በምን ማቆም እንዴት መከልከል ይቻላል? እርሱዋ ሥዕሉዋን መሣል የምታቆመው ይህችን ዓለም በሞት የተሰናበተቻት እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ለእርሱዋ ብሩሹዋ ማስተዋሉዋ ነው፤ ቀለሞቹዋም በነፍሱዋ ውስጥ ናቸው ሸራዎቹዋም ነፍስና ሥጋዋ ናቸው፡፡ በማስተዋል ብሩሽ፣ በነፍሱዋ ውስጥ ባሉ ቀለማት ነፍሱዋንና ሥጋዋን በውበት ታስጌጣቸዋለች፡፡

Wednesday, February 22, 2012

ኑ ቀረብ በሉ!


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
15/04/2004
ፍቅር የሆነ አምላካችን ምን ያህል እኛን እንዳከበረን እስቲ ለአንድ አፍታ ቆም ብልን እናስበው፡፡ አፍቃሪያችን አስቀድሞ በራሱ አርአያና አምሳል ፈጠረን ስለዚህም ክብራችን በመላእክት ዘንድ እጅግ ታላቅ ሆነ፡፡ የእግዚአብሔር መልክ አለንና እጅግ አከበሩን፡፡ ስለዚህም እርሱን እንዳገለገሉት ቆጥረው ቅዱሳን መላእክት እኛን አገለገሉን፡፡ ይህን አስመልክቶ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ አለን “እግዚአብሔር አምላክን በላይ በሰማይ የሚያገለግሉት ቅዱሳን መላእክት እኛን አገለገሉን፡፡ ይህ እግዚአብሔር አምላክ እኛን ምን ያህል እንዳከበረን የሚያሳየን ነው፡፡” ይህ በእርግጥ ድንቅ ነው፡፡
አክብሮ የፈጠረውን ሰብእናችንን በኃጢአት በማዋረዳችን ምክንያት ፈጣሪያችን ተመርሮብን ለዘለዓለም ቆርጦ አልጣለንም፡፡ ነገር ግን ፍቅሩ አገብሮት እኛን እጅግ ሊያከብረንና ሰይጣን ከማይደርስበት ከፍታ ከፍ ከፍ ሊያደርገን ሰማይና ምድርን የፈጠረ አምላክ ከድንግል ቅድስት እናታችን ማኅፀን ተወሰነ፡፡ ሥጋና ነፍስን ከእርሱዋ በመንሳትም ተወለደ፡፡ በዚህም ባሕርያችንን አምላክ አደረገው፡፡ ቅድስት እናታችንንም ሰማይ አደረጋት፡፡ አሁን እኛ ክርስቲያኖች “አባታችን ሆይ በሰማይ የምትኖር” ስንል እነሆ እርሱዋን ሰማይ አድርገን ነው፡፡ ምክንያቱም ወልድ ባለበት አብም መንፈስ ቅዱስም አሉና፡፡ እንዲህ አድርገህ እጅግ ያከበርከንና ያፈቀርከን ፈጣሪያችን ሆይ ላንተ ምን አንደበት ነው ምስጋናን ማቅረብ የሚቻለው? 
እርሱ በዚህ ድንቅ ቸርነቱ ብቻ አላበቃም እኛንም እንደ እናቱ ለራሱ ማደሪያ በማድረግ ሰማይ አደርጎናልና እናመሰግነዋለን፡፡ እርሱ በቃሉ“ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ እርሱ በእኔ ይኖራል እኔም በእርሱ እኖራለሁ" ”(ዮሐ.6፡56)አለን፡፡ ስለዚህም ሥጋውን ስንበላ ደሙንም ስንጠጣ ከድንግል ማኅፀን ተፀንሶ የነበረው ጌታ በእኛም ሰውነት ውስጥ ያድራል፡፡ በመሆኑም እኛም እንደ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በአማን ሰማዩ ሆንን፡፡ ድንግል ሆይ ራስሽን ለፈጣሪያችን ሰማይ በማድረግ እኛም ለእርሱ ሰማይ እንድንሆን ስላበቃሽን እናመሰግንሻለን፡፡ አሁን “አባታችን ሆይ በሰማይ የምትኖር” ስንል የእኛን ሰውነት ሰማይ አድገህ የምትኖር አክባሪያችን ሆይ ስምህ ይቀደስ እያልነው ነው፡፡ ለዚህ ድንቅ ቸርነትህ ምን ዐይነት ምስጋናን ማቅረብ ይቻለን ይሆን?

Sunday, February 19, 2012

ያልታወቀው የጦም ጥቅም



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ 
12/06/2004



ብዙዎቻችን የጦም ጥቅሙ ከምግብ ተከልክለን ራሳችንን ከእግዚአብሔር ፊት በማዋረድ ከእርሱ ዘንድ ሰማያዊ ጸጋን ማግኘታችን ነው፤ ብለን እናስባለን፡፡ ይህ ፍጹም ትክክል ነው፤ ነገር ግን ክብር ለእርሱ ይሁንና ሌላ እኛ የማናውቀው በጦም የኖሩ ቅዱሳን የሚያውቁት አንድ ልዩና ግሩም የሆነ ጥቅም አለው፡፡ እንዲህ ሲባል “ከእኛ ምን ተሰውሮ! በጦም ነፍሳችን ለሥጋ ከመትጋት ወጥታ ከእግዚአብሔር ጋር በተመስጦ በመኖሯ ነፍሳችንም ሥጋችም የሚጠቀሙት ጥቅም አላቸው፡፡” ብላችሁ ትመልሱልኝ ይሆናል፡፡ እንዲህ የመለሳችሁ እንደሆነ እኔ ልገልጠው ያሰብኩትን ጭብጥ አላገኛችሁትምና ሌላ ሞክሩ፡፡ ወይም "ከጤና አኳያ ሰውነታችንን ከምግብ በከለከልናት ጊዜ አካላችን በራሱ የአሠራር ሥርዐት በሰውነት የተከማቸውን ስብ ወደ መጠቀም ስለሚመጣ የስብ ክምችታችን ይቀነሳል፤ ስለዚህም በስብ ክምችት ምክንያት ከሚመጡ ሪህ፤ ደም ግፊትና ስኳር እንዲሁም እነዚህን ከመሰሉ ሕመሞች ይጠብቀናል፡፡ ስለዚህም ሰውነታችንን ጤናማ በማድረግ ያለምንም የጤና መጓደል መንፈሳዊ የሆኑ ተግባራትን ለማከናወን ስለሚያገለግለን ነው” ብላችሁ ልትመልሱ ትችላላችሁ፡፡ እኔ ግን መልሱን አላገኛችሁትም ነው መልሴ፡፡ “እሺ ይህ ካልሆነ እኛ ጌታችንን መስለን በመጦም ሰይጣንን ድል መንሳታችን ነው ጥቅሙ” ትሉኝ ይሆናል፡፡ እርሱም ጥሩ መልስ ነው፡፡ ምክንያቱም ጦም ነፍስን እንደ መልአክ ስለሚያደርጋት ወይም የሥጋ ሥራ ስለሚቀልላት ዐይኖቹዋ በጦም ሰዓት አጥርተው ይመለከታሉና በቀላሉ ሰይጣን ድል ሊነሳት አይቻለውምና ነው፡፡ ነገር ግን ከላይ የመለሳችኋቸው ሁሉ ትክክለኛ መልሶች ቢሆኑም እኔ ልል የፈለግሁትን ግን አላገኛችሁትም፡፡ "እሺ ከእነዚህ ውጪ ምን ልዩ የሆነ መልስ ሊኖር ይችላል? ብላችሁ ጽምፃችሁን አሰምታችሁ ልትናገሩኝና የእኔንም መልስ ጆሮአችሁን አቀቅራችሁ ልትጠባበቁኝ ትችላላችሁ፡፡





Saturday, February 18, 2012

ጸሎት ዘቅዱስ ኤፍሬም (በዐቢይ ጾም የሚጸለይ)


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
11/06/2004
“የሕይወቴ ገዢ የሆንክ ጌታዬ ሆይ! ከስልቹነትና ከተስፋ መቁረጥ መንፈስ እንዲሁም ከንቱ ከሆነ ልፍለፋ ጠብቀኝ፡፡ ከዚህ ይልቅ  መንፈሳዊ ሙላትን ፣ ትሕትናን ፣ ትእግሥትን ፣ ፍቅርን አድለኝ፡፡ ንጉሤና አምላኬ ሆይ በወንድሜ ላይ በከንቱ ከመፍረድ ተከልክዬ የራሴን ኃጢአት ብቻ የማስተውልበትን ጸጋህን አድለኝ፡፡ ለአንተ ክብር ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን !!  

ጦምን አስመልክቶ የቅዱሳን አባቶች አስተምህሮ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
10/06/2004
“በጦም ወቅት አንድ ክርስቲያን  በፈቃደኝነት አንድ በጎ ሥራን  ጎን ለጎን ቢፈጽም መልካም ነው፡፡ ነገር ግን ከሰዎች ምስጋናን ወይም አንዳችን ነገር ሽቶ የሚጦም ከሆነ ግን ጦሙ በእግዚአብሔር ዘንድ የማይወደድ ጦም ይሆንበታል፡፡ ማንኛውም በጎ ሥራ ስንሠራ ለእግዚአብሔር አምላካችን ካለን ፍቅር የመነጨ ይሁን፡፡ እንዲያ ካልሆነ ግን እግዚአብሔርን ደስ ልናሰኝ አይቻለንም፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስን ጌታችን በመንጎቹ ላይ ሲሾመው ለእርሱ ያለውን ፍቅር ተመልከቶ ነበር፡፡ እግዚአብሔርን የሚያፈቅር ሰው የሚፈጽማቸው የትኞቹም በጎ ምግባራት በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደዱለት ይሆኑለታል፡፡ ፍጹማንም ናቸው፡፡ ስለዚህም ማንኛውንም በጎ ሥራዎቻችንን ስንሠራ እርሱን በማፍቀር ላይ የተመሠረተ ይሁን፡፡”
“አንድ ሰው ምንም እንኳ መላ የሕይወት ዘመኑን በትህርምት ሕይወት መምራት ያለበት ቢሆንም በዚህ በዐቢይ ጦም ግን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ኃጢአቱን  ለካህን ተናዝዞ ለድሆች ምጽዋትን በማድረግ በአግባቡ ሊጦም ይገባዋል፡፡ እነዚህን ዐርባ የጦም ቀናት በአግባቡ በጎ ሥራዎች አክለንባቸው የጦምናቸው እንደሆነ ቸሩ ፈጣሪያችን ዓመት ሙሉ ባለማወቅ የፈጸምናቸውን ኃጢአቶቻችንን ይደመስስልናል፡፡ (ዮሐንስ አፈወርቅ )

"በአረጀ አቁማዳ አዲስ የወይን ጠጅ የሚያኖር የለም"(ካለፈው የቀጠለ)


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
10/06/2004
ይህ እንዲሆንም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ስለመንጎቹ በመስቀል ላይ ሠዋ፡፡ ሙሽሪት ምዕመናንንም በደሙ ገዛት፡፡ ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ አንጽቶ ከጎኑ በፈሰሰውም ደሙ ቀድሶ የራሱ አደረጋት፡፡ እንዲያም ስለሆነ ለሰማያዊው ንጉሥ ሰማያዊት ሙሽራው ሆነችው፡፡ ሙሽሪት የተባልነው እኛ ነን፡፡ አሁን እኛ በክርስቶስ አምላክነት አምነን በሥላሴ ስም የተጠመቅን ክርስቲያኖች በመንፈስ ቅዱስ የታደሰ ሰማያዊ ሰብእናን ገንዘባችን በማድረጋችን የእግዚአብሔር ልጆች ተሰኝተናል፡፡ስለዚህም የእግዚአብሔርን ጥልቅ የሆነ አሳብን እንኳ በመንፈስ ቅዱስ ታግዘን ለመረዳት እንችላለን፡፡ እንደ መንፈስ ቅዱስም ፈቃድ በመመላለስ ሰይጣንን ድል የምንነሣበትን የጽድቅ ጥሩርን ለብሰናል፡፡
አሁን አባታችን አዳም ሳይሆን እግዚአብሔር ሆኖአል፡፡ እንዲህም ስለተደረገልን አባ ብለን እርሱን ለመጥራት አናፍርም፡፡  ሆኖም የእግዚአብሔር ልጅነትን ሥልጣን በማግኘታችን ተረጋግተንና ተዛንተን መኖርን አግኝተናል ማለት ግን አንችልም፡፡ ምክንያቱም የአዳምን ንጽሐ ጠባይን ያልወደደውና ከክብሩ ያዋረደው ሰይጣን በቅናት ተነሣስቶ እኛን ለማሰናክል  መትጋቱ አይቀሬ ነውና፡፡ ይህም እንዲገለጥ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ በሰይጣን ይፈተን ዘንድ ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ሄደ፡፡ ይህ የሚስተምረን ነገር አለ፡፡ እርሱም እኛ በጥምቀት የእግዚአብሔር ልጅነት ሥልጣን በማግኘታችን ዲያብሎስ በጠላትነት እንደሚነሣብንና ከልጅነት ክብራችን ለማሳነስ እንደሚተጋ ነው፡፡ ስለዚህም አባ አባ የምንልበትን የልጅነት መንፈስ በጥምቀት በማግኘታችን እኛን ለማሰናከል በእጅጉ እንደሚተጋ አውቀን እኛም በጦምና በጸሎት ጌታችንን መስለን ሰይጣንን ድል ልንነሣው ይገባናል፡፡ ነገር ግን እንዳው በልማድ ለምን እንደምንጦም ሳንረዳ የምንጦም ከሆነ በአዲሱ አቁማዳ አሮጌውን የወይን ጠጅ እንደመጨመር ይቆጠርብናል፡፡ እነዚህ እርስ በእርሳቸው አይጠባበቁምና አቁማዳው ይፈነዳል ወይኑም ይፈሳል፡፡ ስለሆነም ከጦማችን አንዳች ጥቅም ሳናገኝ የሰይጣን መሳለቂያ ሆነን እንቀራለን፡፡ እንዲያ እንዳይሆን መጪው የጦም ወቅታችን ራስን መግዛት የምንለማመድበትና የእግዚአብሔርን አሳብና ፈቃድ የምናቅበት ጦም እንዲሆን እንትጋ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ መጪውን ጦም እንዳው በልማድ ሳይሆን ሰይጣንን እንዴት ድል መንሳት እንደምንችል የምንማርበት ጦም ያደርግልን ዘንድ ፈቃዱ ይሁን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡  

Friday, February 17, 2012

“በአረጀ አቁማዳ አዲስ የወይን ጠጅ የሚያኖር የለም”(ዮሐ.9፡17)


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
10/06/2004

ፍቅር የሆነው አምላካችን ስለእርሱ የመከራ ወቅትና ትንሣኤ በአስተማረን ወቅት “ሙሽራው ከእነርሱ ጋር ሳለ ሚዜዎች ሊያዝኑ ይገባቸዋልን? ነገር ግን ሙሽራው ከእነርሱ የሚወሰድበት ቀን ይመጣል፡፡ በዚያን ጊዜ ሚዜዎች ይጦማሉ” ብሎ ነበር፡፡ ጌታችን የእርሱን ልደትና የስብከት ዘመንን የሙሽርነት ወቅት ይላቸዋል፡፡ በእውነትም ልደትህ በአንተ ያመኑትን ለአንተ ታደርጋቸው ዘንድ በእነርሱ አርአያ ለተገለጥከውና የሰዎች ልጆች መዳን ደስ ለሚያሰኝህ ላንተ ለጌታችን የደስታ ቀን ናት፡፡ ጌታ ሆይ ላንተ ከነፍሱዋ ትገዛልህ ለነበረችውም ለቅድስት ድንግል ማርያምም የአንተ ከፅንሰት እስከ ልደት ያሉት ቀናት የደስታ ቀናቶቹዋ ናቸው፡፡ የስብከትም ዘመን ለአንተ ራሳቸውን ለማጨት የፈቀዱ ሐዋርያት ወደ አንተ የቀረቡበት ወቅት ነውና በእርግጥም የደሰታ ቀን ነው፡፡


Wednesday, February 15, 2012

“እኔ በእርሱ እኔነት ውስጥ”



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
08/06/2004
ይገርማል!! እኔ እምላትን አካል የሥጋዬን ታኽል እንኳ ባለማወቄ ይደንቀኛል፡፡ እኛ  ቅዱስ ጳውሎስ “ዛሬስ በመስታወት በድንግዝግዝ እንደምናይ ነን” (1ቆሮ.13፡12) እንዳለው ያህል እንኳ ያላየናት እኔ የምንላት መንፈሳዊት ረቂቅ አካል  አለችን ፡፡ ነፍሴ ምን እንደምትመስል እንደማላቃት እንዲሁ እኔ የምላት አካሌን አለማወቄ እንዴት የሚያሳፍር ነገር ነው ጃል!! ነገር ግን እኔ ያመጣሁት ሳይሆን እግዚአብሔር አምላክ በድንቅ ቸርነቱ ከእኔ የሰወራት ናት፡፡ በዚህ ምድር በቅድስና ለመኖር ከተጋሁ በመንፈስ ቅዱስ መነጽርነት ልክ መላእክትን እንደማየት ላያትና ቅዱስ ጳውሎስ “በዚያን ጊዜ ግን ፊት ለፊት እናያለን ዛሬ ከእውቀት ከፍዬ አውቃለሁ በዚያን ጊዜ ግን እኔ ደግሞ እንደታወቅሁ አውቃለሁ”(1ቆሮ.13፡12) እንዳለው አያታለሁ!!
እኛ በቅድስና የተጋን እንደሆነ በዚህ ምድር ሳለን እንደ ቅዱስ ጳውሎስ እኔነታችንን በድንግዝግዝታ ልንመለከታት እንችላለን፡፡ ነገር ግን ካልተጋን ልክ እንደባለ ጠጋው ነዌ በሲኦል ሳለን ማየታችን አይቀሬ ነው፡፡ ነገር ግን እነዚህ እውቀቶች የተለያዩ እውቀቶች ናቸው፡፡ በቅድስና ተግተን በመኖራችን እኔነታችንን ማወቃችን ለእኛ ለክብር ሲሆን ላልተጉቱ ግን ለኩነኔ ነው፡፡ እነርሱ በዚያን ጊዜ የሚመለከቱት እኔ የሚሉዋት ረቅቅ አካላቸው ሰይጣንን መስላ ነው፡፡ እኛ ግን እኔነታችንን የምናገኛት ክብር ይግባውና ክርስቶስን መስላ ነው፡፡

ጸሎትና ጽሙና(ከሶርያ ቅዱሳን አንዱ)


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
07/06/2004   
ወንድሜ ሆይ ጸሎት ሲባል የጸሎት ቃላትን ብቻ መድገም አድርገህ አንዳታስበው ፤ ወይም የጸሎት ቃላትን በማጥናት የሚማሩት አድርገህ እንዳትቆጥረው ፡፡ እውነታው ይህ አይደለም ፤ ተገቢ የሆነ ጸሎት በመማር ወይም የጸሎት ቃላትን በመድገም የምታገኘው እንዳልሆነ እንድትረዳ እፈልጋለሁ ፡፡ እርሱ ቃሎችን አሳክተህና አሳምረህ ልመና የምታቀርብለት ሹም አይደለምና ፡፡ ጸሎት የሚቀርብለት እርሱ መንፈስ ነው ፡፡ ስለዚህም እርሱ መንፈስ ነውና ጸሎትህ መቅረብ ያለበት በመንፈስ ነው ፡፡
እግዚአብሔር የሚፈቅደውን ጸሎት ለመፈጸም ድምፅ ማውጣት የሚጠበቅበት የተለየ ቦታ የለም ፡፡ ጌታችንም ስለዚህ ሲያስተምር “በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል ፡፡” ሲል እንዲሁም  ወደ እርሱ ለመጸለይ የተለየ ስፍራ እንደማያስፈልግ ሲያረጋግጥ “በእውነት የሚሰግዱ ለአብ በመንፈስና በእውነት የሚሰግዱበት ጊዜ ይመጣል አሁንም ሆኖአል ፡፡” ብሎአል(ዮሐ.፬፥፳፩) ስለምን እኛ በመንፈስ መጸለይ እንደሚገባንም ሲያስረዳ “እግዚአብሔር መንፈስ ነው” ብሎ ገልጾልናል ፡፡ (ዮሐ. ፬፥፳፬)ለእርሱ የሚቀርብለት ምስጋና በመንፈስ የሚቀርብ መንፈሳዊ መሆን አለበት ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም መንፈሳዊ ጸሎትንና መዝሙራትን በተመለከት እንዴት መፈጸም እንዳለባቸው ሲያስተምር “እንግዲህ ምንድን ነው? በመንፈስ እጸልያለሁ በአእምሮም እጸልያለሁ ፤ በመንፈስ እዘምራለሁ በአእምሮም እዘምራለሁ ፡፡”(፩ቆሮ.፲፬፥፲፭)ብሎናል ፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው ወደ እግዚአብሔር ጸሎትና ልመናን በሚያቀርብበት ጊዜ በመንፈስና በአእምሮ መሆን እንዳለበት አስገንዝቦ ጽፎልናል፡፡

Tuesday, February 14, 2012

እግዚአብሔርን ከማወቅ ጋር ፆታዊ ፍቅር ጣፋጭ!!!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
06/06/2004


ፆታዊ ፍቅር ክርስቶስን በማወቅ ላይ የተመሠረተ እንደሆነ እጅግ ጣፋጭና ማራኪ ይሆንልናል፡፡ እንዲያ ከሆነ ባል በሚስቱ ተፈጥሮ በኩል የጌታውን እናት ቅድስት ድንግል ማርያምን፣ እኛን መንፈሳዊያን ያደረገንን መንፈስ ቅዱስን እንዲሁም ቤተክርስቲያንን ይመለከትባታል፡፡ ሚስትም በባሎዋ መስታወትነት ለሔዋን እናትም አባትም የሆነውን ቀዳማዊ አዳምንና እርሱዋን ከጎኑ በፈሰሰው መለኮታዊ ውኃ አንጽቶ ከጎኑ በፈሰሰው ክቡር ደሙ ተቤዥቶ የወለዳትን ዳግማዊውን አዳም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትመለከተዋለች፡፡ በሚወልዱአቸው ልጆቻቸው ውስጥም በሥጋ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም እቅፍ የነበረውን፣ እንደ እግዚአብሔር የባሕርይ ልጅነቱ ግን ከአባቱ እቅፍ የሆነውን ሕፃኑ ኢየሱስ ክርስቶስን በአንድነት በልጆቻቸው ይመለከቱታል፡፡

Monday, February 13, 2012

ለእኛስ የፍቅረኞች ቀን ይኖረን ይሆንን?(ቀጣይ ጽሑፍ)


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/06/2004
... ከእዚህ መንደርደሪያ አሳብ ተነሥተን ጾታዊ ፍቅር የተገለጠው መቼ ነው ብለን ብንጠይቅ ሔዋን ከአዳም የግራ ጎን ከተገኘች በኋላ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ በዚያን ጊዜ አባታችን አዳም እግዚአብሔር ከጎኑ አጥንት የፈጠራትን ሴት በተመለከተ ጊዜ “ይህች አጥንት ከአጥንቴ ናት ሥጋዋም ከሥጋዬ ናት” በማለት ለእርሱዋ ያለውን ፍቅር ለአምላኩ ገለጠ፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር በገነት በአዳምና በሔዋን መካከል ትዳርን መሠረተ፡፡እግዚአብሔርም "ሰው አባትና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይጣበቃል(ይተባበራል)" አለ፡፡ ስለዚህም ለአዳምና ለሔዋን እቺ ዕለት የደስታቸው ቀን ናትና መቼም ቢሆን የሚረሱዋት ቀን አይደለችም፡፡
ይህ በሰማያት የተሠራው ሰማያዊ ሥርዐት ከውድቀትም በኋላም ቀጥሎአል፡፡ ስለዚህም በዚህ ፍቅር እርስ በእርሳችን እንሳሳባለን በትዳርም እንታሰራለን፡፡ ሥርዐቱም ሰማያዊ ነውና ፍቺ ፈጽሞ አይፈቅድም፡፡ ፍቺ ተፈጸመ ማለት ትዳሩ ከሰማያዊው ሥርዐት ወጣ እንስሳዊ ሆነ  ቅድስናውን አጣ ማለት ነው፡፡ ያም ማለት ምን ማለት መሰላችሁ በሥላሴ ውስጥ ያለው አንድነትና ሦስትነት መልኩን አጣ ከተፈጠርንበት ዓላማ ወጣን ማለት ነው፡፡


Sunday, February 12, 2012

ለእኛስ የፍቅረኞች ቀን ይኖረን ይሆንን?



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/06/2004
ዘመኑ በሦስተኛው ክፍለ ዘመን ነው፡፡ አንድ ቫላንታይን የሚባል ቅዱስ እንደሆነ የሚነገርለትና በሰማዕትነት ያረፈ ቄስ ነበር፡፡ በእርሱ ስምም በአውሮፓ ፌብሯሪ ዐሥራ ዐራት ቀን በእኛ አቆጣጠር የካቲት ስድስት የፍቅረኞች ቀን ተብሎ ይከበር ነበር፡፡ ነገር ግን የኋላ ኋላ ይህ በዓል በሮም ካቶሊክ ቤተክርስቲያን አንዳይከበር ታገደ፡፡ ነገር ግን አንደገና ይህ በዓል ሕይወት ዘርቶ በአውሮፓውያን ዘንድ ይከበር ያዘ ፡፡ ቀስ በቀስም በዓሉ የአውሮፓውያን መሆኑ ቀርቶ የመላው ዓለም ሆነ፡፡ በሀገራችንም የፍቅረኞች ቀን መከበር ከጀመረ ሰነባብቶአል፡፡ ይህን እስከዚህ ካልኩ ይበቃኛል፡፡ ምክንያቱም ከእኛ ትውፊት ጋር ፈጽሞ የማይዛመድ ስለሆነ ትቼዋለሁ፡፡ ነገር ግን አልነቅፍም፤ ዓላማዬም ይህ አይደለም የኔ ትኩረት ይህን አጋጣሚ ተጠቅሞ ክቡር ስለሆነው ጾታዊ ፍቅር አንድ ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ጾታዊ ፍቅር ሰማያዊ፣ ድንቅና ግሩም ነውና፡፡

Friday, February 10, 2012

ነፍስ ለሥጋ ያቀረበችው ምስጋና



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
02/06/2004 

ነፍስ እንዲህ ብላ ሥጋን አመሰገነቻት፡፡ ሥጋዬ ሆይ እኔ ብቻ ሳልሆን መላእክትም አንቺን እጅግ ያከብሩሻል ያፈቅሩሻል፡፡ ምክንያቱም ባንቺ ነውና እነርሱ እርሱን መመልከታቸው፡፡ አስቀድሞ ግን ምንም እንኳ እነርሱ ረቂቃን ቢሆኑ ረቂቅ የሆነውን  እግዚአብሔርን ለማየት  አልተቻላቸውም ነበር፡፡ ስለዚህም በሰው አምሳል ተገልጦ ይታያቸው ነበር፡፡ አሁን ግን ከእናታችን የነሳውን ሰውነት ገንዘቡ አድርጎአልና እርሱን ለማየት በቁ፡፡ ስለዚህም ሥጋዬ ሆይ መላእክት አንቺን ያፈቅሩሻል ያመሰግኑሻል፡፡ እንደዲያማ ባይሆን እግዚአብሔርን እንዴት ሊያዩት ይችሉ ነበር? እኛም በእርሱ አባቱን ልንመለከት፣ መንፈስ ቅዱስም ሕይወታችን ሊሆን እንዴት ይችል ነበር? ሕመምተኞችስ እንዴት ወደ እርሱ ቀርበው የልብሱን ዘርፍ በመዳሰስ  ከሕመማቸው ይፈወሱ ነበር? እኛስ እንዴት የእርሱ የአካሉ ሕዋሳት ልንሆን እንችል ነበር? እንዲህ ባይሆን ኖሮ ይህ ሁሉ ባልተፈጸመልን ነበር፤ ምክንያቱም እርሱ እሳት ልብሱም እሳት ነውና፡፡ እርሱ የማይጨበጥና የማይዳሰስ ረቂቅ እንዲሁም ማንም በማይደርስበት ብርሃን ውስጥ የሚኖር ነውና፡፡ ወደ እርሱስ መቅረብ የሚቻለው ማን ነበር? እርሱ  የሚባላ እሳት ነውና፡፡ 

Thursday, February 9, 2012

ብርህት ዐይን



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
01/06/2004 
ውስጣዊ የሆነችው የነፍሳችን ዐይን መመልከት የምትችለው በእምነት ነው፡፡ በእምነት ዐይናችን እግዚአብሔር በመጽሐፍ እና በዐይን በሚታየው በዚህ ዓለም ሰውሮ ያስቀመጣቸውን ምሳሌዎችን መረዳት እንችላለን፡፡ ውጫዊዋ ዐይናችን በፀሐይ ብርሃን ታግዛ መመልከት እንድትችል ውስጣዊዋ  የነፍስ ዐይናችንም በእምነት ብርሃን  ታግዛ መንፈሳዊውን ዓለም ትመረምራለች ትመለከታለች፡፡ ነገር ግን ይህች የነፍስ ዐይናችን በኃጢአት ምክንያት ልትታወር ትችላለች፡፡ ውስጣዊዋ ዐይናችን በደንብ መመልከት እንድትችል ለማድረግ ንሕትና ጥርት ያለች መሆን አለባት፤ እርሱም ከኃጢአት ነው፡፡ ውስጣዊዋ ዐይናችን ንጽሕትና ጥርት ያለች ስትሆን ቅዱስ ኤፍሬም እንደሚለው “ብርህት ዐይን” ተብላ ትጠራለች፡፡ ይህች ቃል በቅዱስ ኤፍሬምና በሌሎችም የሶርያ ቅዱሳን አባቶች ዘንድ የምትዘወተር ቃል ናት፡፡
ውስጣዊው የነፍሳችን ዐይኖች የበሩ እንደሆነ ብቻ ነው የእግዚአብሔርን ሥራና ፈቃድ ማስተዋልና በሥነፍጥረትና በመጽሐፍ ቅዱስ ያሉትን ምሳሌዎችን መረዳት የምንችለው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍት ፊታችንን እንደምንመለከትባቸው መስታወቶች ናቸው፡፡ ዐይኖቹ ብሩሃን የሆኑለት ሰው በእነርሱ ውስጥ እርሱ በእግዚአብሔር አርዓያና አምሳል እንደተፈጠረ ይረዳባችኋል፡፡” (ቅዱስ ኤፍሬም)
የማየት ብቃታችንም ሊያድግ የሚችለው እምነታችን ያደገና የጨመረ እንደሆነ ነው፡፡ የነፍስ ዐይናችን በጣም ብርህት በሆነች ቁጥር እግዚአብሔራዊ እውነታዎችን በይበልጥ እየተረዳን እንመጣለን፡፡ አንዲት ነፍስ አንድን እግዚአብሔራዊ እውነት በተለያየ አቅጣጫ መረዳት የቻለች እንደሆነ የዚህች ነፍስ ዐይኖች ብሩሃን ናቸው ማለት ነው፡፡

“አንዲት አጥንት”



ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
01/06/2004
ከዛሬ ስድስት ዓመት በፊት የተጻፈ 


 “ከአዳም የጎን አጥንት የተፈጠረችው ሴት ከራስ ቅሉ አጥንት አለመፈጠርዋ በእርሱ ላይ እንዳትሰለጥን ነው ከእግሩም አጥንት ከአንዱ አለመፈጠሯ እርሷን መበደልም ይሁን መጨቆን እንዳይገባው ለማስተማር ነው፡፡ ነገር ግን ከጎን አጥንቱ ፈጠራት በክብር እኩል መሆናቸውን ለማሳየት፡፡ ይህ የጎን አጥንት ከክርኑ አካባቢ መሆኑ ሚስቱን ከጥቃት ሁሉ ይጠብቃት ዘንድ የባል ሚና መሆኑን ለማስገንዘብ ነው፡፡ እንዲሁም ከልቡም አጠገብ መፈጠሩዋ እርሷን ከልቡ ሊያፈቅራት እንዲገባው ለማመልከት ነው፡፡”(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቅዱስ ያዕቆብ ዘስሩግ)
ቅዱሳን እንዳስተማሩን እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ማዕከላዊ አድርጎ መፍጠሩ በዐይን የማይታዩትን መናፍስትንና የሚታዩ ፍጥረታትን ሁሉ እርሱ እንደፈጠረና ግዢያቸው እንደሆነ ምስክር እንዲሆነው ነው ይላሉ፡፡ ባጠቃላይ ሰው /Human beings/ የእግዚአብሔር የገዢነቱ ምልክት ነው፡፡
ስለዚህም አዳም በነፍስ ተፈጥሮው መልአካዊ ባሕርይ ሲኖርው በሥጋው ባሕርይው ደግሞ እንስሳዊ ባሕርይ ይንጸባረቅበታል፡፡ በዚህም መሠረት አዳም በሥጋው ባሕርይው ምክንያት ልክ እንደ እንስሳት ለመኖር መሠረታዊና አስፈላጊ ነገሮች የተባሉት ሁሉ ለእርሱ የተገቡ ሆኑ፡፡

Tuesday, February 7, 2012

“ራስን የመግዛት ጥበብ”



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
30/04/2004
ቅዱስ ዮሐንስ ዘደማስቆ “ፍልስፍና ማለት ጥበብን ማፍቀር ማለት ነው፤ ጥበብ ደግሞ እግዚአብሔር ነው፤ ስለዚህም ፍልስፍና ማለት እግዚአብሔርን ማፍቀር ማለት ነው”ብሎ ያስተምራል፡፡ እኛም በበኩላችን እግዚአብሔር ፍቅር ነው፤ ሰውም በእግዚአብሔር አርዓያና አምሳል የተፈጠረ ስለሆነ ሰው ፍቅር የሚገዛው ፍጥረት ሆነ እንላለን፡፡ አንድ ጸሐፊ ስለ ሰው ተፈጥሮ ሲያስተምር፡- “እግዚአብሔር ሰውን ከፍቅር አፈር አበጀው፡፡ ስለዚህም ሰው ፍቅር የሚገዛው ፍጥረት ሆነ፤ ስለዚህም ሰው ፍቅር ሲያጣ እንደ በድን ሬሳ ሲቆጠር በፍቅር ውስጥ ካለ ሕያው ነው፡፡ ሕይወቱም እግዚአብሔር ነው፤ እግዚአብሔርም ፍቅር ነው፡፡” ስለዚህም ክርስቲያናዊ ፍልስፍና ፍቅርን መሠረት ያደርጋል፡፡ ነገር ግን ለፍልስፍና ትምህርታችን መንደርደሪያ የሚሆነን ፍቅር የሆነውን ተፈጥሮአችንን በሚገባ ማወቃችንና መረዳታችን ነው፡፡
  ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ የተፈጠረውን ሰውን ትንሹ ዓለም ይለዋል፡፡ እንዲህም ያለበት ምክንያት ሰማያዊና ምድራዊ ተፈጥሮ ያለው በመሆኑ ነው፡፡ ረቂቅ በሆነችው የነፍስ ተፈጥሮው በኩል ረቂቃን ከሆኑ መናፍስት ጋር አኗኗሩን ሲያደርግ፤ ግዙፍ በሆነችው ሥጋዊ ተፈጥሮው በኩል ደግሞ በምድር ፍጥረታት ላይ ገዢ ሆኖ ጠቅሟቸውም ተጠቅሞባቸውም ይኖራል፡፡ ስለዚህም ነው ሰው በሁለት ዓለማት እኩል የሚኖር ፍጥረት ነው መባሉ፡፡ ወይም ሰው የሁለት አካላት ውሕደት ውጤት ነው፡፡

Monday, February 6, 2012

ነነዌ እና ቅዱስ ኤፍሬም



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
28/05/2004
ከምንባብ በፊት የእኔ መልእክት
የቅዱስ ኤፍሬም ሥራዎችን ማስተዋወቄ ብዙዎቻችን ቅዱስ ኤፍሬምን ከውዳሴ ማርያም ውጪ በሌሎች ሥራዎቹ ስለማናቀው ነው፡፡ ስለዚህም ጥቂት የቅዱስ ኤፍሬም ሥራዎችን ለማቅረብ እየሞከርኩ እገኛለሁ፡፡ ወደ ፊትም እግዚአብሔር ቢፈቅድ የቅዱስ ኤፍሬምን ሥራዎች ለማስተዋወቅ ምኞቴ ነው፡፡

ቅዱስ ኤፍሬም በቅኔያዊ መዝሙራቱ የነቢዩ ዮናስ በዓሣ አንባሪ ሆድ ውስጥ ሦስት ሌሊት ሦስት መዓልት መሆኑን በተለያየ መንገድ የተለያዩ አሳቦቹን ለመግለጽ ይጠቀምበታል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ጥቂቶቹን እነሆ ብያለሁ፡፡

v ሌጌዎን ማለት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንደተገለጠው በቁጥር 2000 የሚደርሱ የአጋንንት ሠራዊት ማለት ነው፡ እነዚህ አንድ ሰው ላይ ከትመው ይኖሩ ነበር፡፡ ጌታችንም እነዚህ አጋንንት ወደ ሰፈሩበት ሰው መንደር በመምጣት ይህን ሰው ከእነዚህ አጋንንት ቁራኛነት አላቆታል፡፡ ይህን ቅዱስ ኤፍሬም ከዮናስ ወደ ባሕር መጣል ጋር አቆራኝቶ “ክፉ የተባለው ሰይጣን እንዲህ አለ" እያለ በሰዎች መዳን የሰይጣንን ቁጭት ይገልጥልናል፡-

“ክፋት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን “ዛሬ ከቀደመው ይልቅ ታላቅ የሆነ ክፋትን ሠራህብኝ፡፡ እኛን ማዋረድህ ሳያንስህ በነቢዩ ዮናስ ላይ የፈጸምከውን በእኛ ላይ ልትደግም መጣህ፡፡ ሌጌዎንን ወደ ባሕር ጥልቅ በመጣልም ተበቀልከን፡፡ ዮናስ ከሦስት ቀን በኋላ ሕያው ሆኖ ከባሕር ውስጥ ቢወጣም ሌጌዎን ግን በባሕር ውስጥ ወዳለው ጥልቅ ሰጥሞ እንዲቀር አደረግህብን፡፡…

Sunday, February 5, 2012

ከጾም የሚቀድመው ጉዳይ (በቅዱስ ኤፍሬም)


አንተ ሰው የበደለህን ይቅር ሳትል ወደ ጾም አትግባ፡፡ አንተን በበደለህ ሰው ላይ በቁጣ እያለህ የምትጾመው ጾም ከንቱ ነው፤ እግዚአብሔርም አይቀበለውም፡፡ ጾምህን በፍቅርና እርሱን ተስፋ በማድረግ በእምነት ካላደረግኸው አንተን ፈጽሞ ሊረዳህ አይችልም፡፡ በጠብ ሆኖና በውስጡ ጠላትነትን አንግሦ የሚጾም ጸዋሚ እግዚአብሔርን ይጠላዋል፤ ከመዳንም ፈጽሞ የራቀ ነው፡፡ (ቅዱስ ኤፍሬም) 

Saturday, February 4, 2012

መድኀኒዓለም



ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
(ስብከት ወተግሣጽ ለሚባለው መጽሐፌ መታሰቢያ የተጻፈ)
27/07/2003 ተጻፈ
ጌታ ሆይ አንተ የመንፈሳውያንና የምድራውያን ፍጥረታት ገዢ እንደሆንኽ በሰማይም በምድር ያሉ ፍጥረታት ሁሉ ተገንዝበው ለአንተ እንደ ችሎታቸው መጠን በፍቅር በመሆን ምስጋናን ያቀርቡ ዘንድ ሰውን ሰማያዊና ምድራዊ አካል እንዲኖረው አድርገህ በመፍጠር የገዢነትህ ምልክት አደረግኸው ፡፡
 ምድራውያን ለአንተ አርዓያና አምሳል ለሆነው ሰው ሲገዙለት አንተን የሚያገለግሉህ ሰማያውያን መላእክት ደግሞ በፍቅር አገለገሉት ፡፡ ለማይታየው አምላክ ምሳሌ በሆነው በአዳም ተፈጥሮ በኩል መላእክት አንተን አይተው ደስ ተሰኙ ፡፡ እነርሱ በላይ በሰማይ የአንተን ፍቅር እየተመገቡ ፍጹም በሆነ ደስታ ይኖራሉና አርዓያህና አምሳልህ የሆነውን አዳምን ባዩት ጊዜ በደስታ ዘመሩ ፡፡
  መላእክት የፈጣሪነትህና የማንነትህ መለያ የሆነውን በአርዓያህና በአምሳልህ በተፈጠረው ሰው ባሕርይ ውስጥ አይተው ሦስትነትህንና አንድነትህን ተማሩ ፡፡ ጌታ ሆይ “ሰውን በአርዓያችንና በአምሳላችን እንፍጠር” አልኽ ፡፡ “ወንድና ሴት አድርገህም ፈጠርካቸው”፡፡ በአካል የተገለጠው ግን አንድ አዳም ነበር ፡፡ ሔዋን ግን በአካሉ ውስጥ ነበረች ፡፡  በኋላም ከአዳም እርሱዋን በመለየት ገለጥካት፡፡
 በዚህም አብ በመውለዱ፣ ወልድም በመወለዱ፣ ምክንያት በመካከላቸው መቀዳደም እንደሌለ አርዓያህና አምሳልህ በሆነው በሰው ተፈጥሮ በኩል ለመላእክት አስተማርካቸው ፡፡ መንፈስ ቅዱስም ከአብ ቢሰርጽም በአብም በወልድም ሕልው እንደሆነ እንዲሁ አዳምና ሔዋንም በአንድ አካል በነበሩበት ወቅት አንዲት ነፍስ ነበረቻቸው፡፡ በዚህም መላእክት መንፈስ ቅዱስ ለአብና ለወልድ ሕይወታቸው እንደሆነ ተረዱ ፡፡ ስለዚህም መላእክት ሥላሴን በምሳሌው አይተውታልና  ሰውን የፈጠረውን እርሱን እጅግ ወደዱት ፡፡