Friday, February 24, 2012

ሠዓሊት በተፈጥሮ


ከዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
16/06/2004

እግዚአብሔር አምላክ ሴትን ልጅ ጥበብን የምትወድ ሠዓሊት አድርጎ ፈጠራት፡፡ ስለዚህም ውስጣዊውንና ውጫዊውን የሰውነት ክፍሎቹዋን እንደ ሸራ በመጠቀም ልታስተላለፍ የምትፈልገውን መልእክት በሰውነቱዋ ሸራ ላይ ትሥልልናለች፡፡ እኛም ወንዶች ደግሞ አድናቂዎቿና ተማሪዎቿ ነን፡፡ ባለን እውቀት ላይ ተጨማሪ እውቀቶችን ከእርሱዋ እንጨምራለን፡፡ እንዲህም ስለሆነ እነርሱ ሁል ጊዜ በሕሊናቸው የሚመላለሰውን በጎም ይሁን ክፉ አሳብ በሰውነታቸው ሸራ ላይ ለመሣል ሲተጉ እኛ ወንዶች ደግሞ ሥዕላቸውን አይተን ለማድነቅና ለመማር እንተጋለን፡፡ እነርሱ ልክ እንደ ሠዓሊ በዝምታ መልእክታቸውን በሰውነታቸው ሸራ ላይ ሲያስተላለፉ፤ እኛ ደግሞ በዝምታ የጥበብ ጥማችንን ስናረካና ከመልእክቶቻቸው ስንማር እንገኛለን፡፡
ይህን ግን ምናልባትም ዘመኑ የተረዳው አይመስለኝም፡፡ ሴትን ልጅ አታጊጪ ብሎ መከልከል አንድ ሠዓሊን አትሣል ብሎ እንደ መከልከል ይቆጠራል፡፡ ሠዓሊን አትሣል ብለን ብሩሹንና ሸራውን ልንቀማው እንችላለን፡፡ ሴትን ልጅ ግን አትሣዪ ብሎ በምን ማቆም እንዴት መከልከል ይቻላል? እርሱዋ ሥዕሉዋን መሣል የምታቆመው ይህችን ዓለም በሞት የተሰናበተቻት እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ለእርሱዋ ብሩሹዋ ማስተዋሉዋ ነው፤ ቀለሞቹዋም በነፍሱዋ ውስጥ ናቸው ሸራዎቹዋም ነፍስና ሥጋዋ ናቸው፡፡ በማስተዋል ብሩሽ፣ በነፍሱዋ ውስጥ ባሉ ቀለማት ነፍሱዋንና ሥጋዋን በውበት ታስጌጣቸዋለች፡፡

ሴትን ልጅ ውስጣዊውንና ውጫዊውን ሰውነትሽን አታስውቢ ብሎ መቃወም ምናልባትም ከፈጣሪ ጋር መጋጨት ይሆንብናል፡፡ እንዲህ ማለትም ተፈጥሮሽን ተቃወሚው ማለትም ነው፡፡ ብንቃወማትም እርሱዋን በውስጣዊውም በውጫዊውም ሸራዎቹዋ ላይ ሥዕላትን ከመሣል አናቆማትም፡፡ ብዙዎች በተለይ የሃይማኖት ሰዎች ነን የሚሉ ይህንን እውነት አልተረዱትም፡፡ 
ቅዱስ ጳውሎስ ለገላቲያ ክርስቲያኖች “ልጆቼ ሆይ ክርስቶስ በእናንተ እስኪሣል ድረስ ዳግመኛ ስለ እናንተ ምጥ ይዞኛል”(ገላ.4፡19) እንዲል መምህር ሠዓሊ ነው፡፡ ሴት ልጅም ለልጆቿ የመጀመሪያዋ መምህርት ናት፡፡ የፍጥረት ሁሉ የመጀመሪያ መምህርት ሴት ናት፡፡ እንዲህም እንዲሆንም እግዚአብሔር ሴትን ልጅ ሠዓሊት አድርጎ ፈጠራት፡፡ የሴት ልጅ ሠዓሊነት ተፈጥሮአዊ ነውና ሥዕልን በሰውነቷ ሸራ ላይ ለመሣል አትቸገርም፡፡ ነገር ግን ያልበሰለ ሠዓሊና በሳል የሆነ ሠዓሊ በሥዕላቸው ውስጥ በሚያስተላልፉት መልእክት እንዲለያዩ፤ እንዲሁ በሴቶችም ዘንድ የብስለት ልዩነት አለና በአእምሮዋ በሳል ያልሆነች አንዱዋ በሰውነቱዋ ሸራ ላይ የምትሥለው ሥዕል አድናቂዎቹዋን ማርኮ ላይዝላትና ላያስተምርላት ወይም ከሩቅ ሲያዩት የሚያምር መስሎ የሚታይ ሲቀርቡት ግን እዚህ ግባ የማይባል ሊሆን ወይም ልክ እንደ አሻንጉሊት ውበት ብቻ ሆኖ ምንም ዓይነት መልእክት የሌለው ባዶ የሆነ ሥዕል ሊሆን ወይም የውስጥ ሥጋዊ ፈቃዱዋን የገለጠችበት ይሆንና ለዚህ የተጉትን ወደ ራሱዋ በማቅረብ ለእነርሱ መዝናኛ ሆና የምትቀርበት ሥዕል ሊሆን ይችላል፡፡
በሳሉዋ ሠዓሊት ግን እንዲህ አይደለችም፡፡ ይህች በሳል ሴት የእውቀት ባለቤት የሆነውን የአምላክን እውቀት ገንዘቡዋ በማደረግ አድናቂዎቿን በሰውነቱዋ ሸራ ላይ በሣለችው ሥዕል ፈጣሪያቸውን እንዲያስቡና ከጥፋት ተመልሰው እግዚአብሔርን ወደ ማምለክ እንዲመጡ ታደርጋቸዋለች፡፡ በሰውነቱዋ በሣለችው ሥዕለ-አምላክም እግዚአብሔርን የሚወድ ወዳጅን ታፈራለች፤ ዘማዊያን ግን ከእርሰዋ ይሸሻሉ፡፡ አግብታም ከሆነ ባልዋን በውስጣዊውም በውጫዊውም ሥዕሉዋ አስተምራ እርሱንና ልጆቹዋን ታድናለች፡፡ ስለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ “ሴቲቱ ግን በእምነትና በፍቅር በቅድስናም ራሳቸውን እየገዙ ቢኖሩ በመውለድ ትድናለች”ያለው፡፡(1ጢሞ.2፡15)ሴት ልጅ እግዚአብሔርን በማወቅ ልጁዋን ዳግም ካልወለደችው የሥጋ ልደት ብቻውን ምን ሊረባል? ሐዋርያውም “ሴት ልጅ በመውለድ ትድናለች” ሲል ስለሥጋ ልደት እየተናገረ አይደለም፡፡ የወለደ ሁሉ የሚጸድቅ ከሆነማ መካኖች ምን ሊውጣቸው ነው? ይህ ከሆነማ ቅዱስ ጳውሎስ  መውለድን እምነት፣ ፍቅር፣ ቅድስና ከሚሉት ቃላት ጋር አቆራኝቶ መናገር ለምን አስፈለገው? ስለዚህም ነው ቅዱስ ጴጥሮስ ሚስቶችን “ለእናንተ ጠጉርን በመሸረብና ወርቅን በማንጠልጠል ወይም ልብስን በመጎናጸፍ በውጭ የሆነ ሽልማት አይሁንላችሁ፤ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለው ሰው ይሁንላችሁ” ብሎ መምከሩ፡፡ እንዲህ ያለ ሰብእና ያለው ደግሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ክርስቶስን አውቃ እንዲህ ዓይነት ሥዕል በሰውነቱዋ ሸራ ላይ በኋላም በባሏና በልጆቿ ላይ ልክ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ ለመሣል የምትተጋ ሴት በእርግጥም ግሩም ሠዓሊት ናት፡፡ 
አንዲት ሴት እንዲህ የሆነ ረቂቅና ሰዎችን ከጥመታቸው መልሶ ወደ ቀና መንገድ የሚመራቸውን ሥዕል ለመሣል አስቀድማ ክርስቶስንንና ራሳቸውን ለእርሱ ማደሪያነት ያበቁትን ቅዱሳንን በተለይ ቅድስት ድንግል ማርያምን ልታውቅ ይገባታል፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም ገና ከሕፃንነቱዋ ጀምራ ራሱዋን በመንፈሳዊ እውቀት ያስጌጠች፣ “በዘርህ አሕዛብ ይባረካሉ” የሚለውን ለአብርሃም አባቱዋ የተገባውን ቃል ኪዳን በተስፋ የምትጠባበቅ፣ ነፍሱዋ እርሱን ለማየት የምትናፍቅና አምላክን በነፍሱዋ ሥላ የተገኘች ቅድስት ናት፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም ከመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል የምሥራቹን ቃል በሰማችበትም ወቅት እንኳ ቅዱሳት መጻሕፍትን እያነበበች ነበር የተገኘችው፡፡ ይህን ድንቅ የቅድስና ሕይወቱዋን የተመለከተ እግዚአብሔር ወልድ በሥጋ እናቱ ትሆን ዘንድ መረጣት፡፡ የሁሉ ፈጣሪ የሆነው ሰማያዊ ንጉሥ በውበቱዋ ተማርኮ ከእርሱዋ ተፀንሶ ሊወለድ ወደ እርሱዋ መጣ፡፡ ስለዚህም “ልጄ ሆይ ስሚ እዪ ጆሮሽንም አዘንብዪ ወገንሽን ያባትሽንም ቤት እርሺ ንጉሥ ውበትሽን ወድዶአልና” ተብሎ የተነገረው የትንቢት ቃል በእርሱዋ ተፈጸመ፡፡(መዝ.44፡10)
እርሱ እግዚአብሔር ወልድ ሴት ልጅ ለፍጥረት ሁሉ መምህርት እንደሆነች ሊያስተምረን በሥጋ ያለወንድ ዘር ከእርሱዋ ብቻ ተወልዶ ከሥሯ አደገ፡፡ ሴቶችም እርሱዋን አብነት አድርገው ልጆቻቸውን በጥበብና በሞገስ እንዲሁም በቁመት በእግዚአብሔርና በሰው ፊት ያሳድጉዋቸው ዘንድ እንዲገባ ለማስተማር ስለጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ እድገት “ኢየሱስም ደግሞ በጥበብና በቁመት በሞገስም በእግዚአብሔርና በሰው ፊት ያድግ ነበር”(ሉቃ.2፡52)ተብሎ ተጻፈላቸው፡፡
ጥበብ ማለት በተግባራዊ የቅድስና ሕይወት የተገኘ እውቀት ማለት ነው፡፡ እኛም ሴት ልጅ ጥበብን የምትወድ ድንቅ ሠዓሊት ናት ካልን በቅድስና ምልልሱዋ ያገኘችውን ተሞክሮ ለተማሪዎቿ በሚገባ መልኩ በሥዕልም ይሁን በቃል እነርሱን መስላ ወይም በሌላ መንገድ ለማስተማር የምትበቃ ናት ማለታችን ነው፡፡ ባልዋንም ደግሞ በሚታይ የቅድስና ሕይወት፣ ከአንደበቱዋ በሚወጡ የታረሙ ንግግሮች፣ በትሕትናዋ፣ በእርጋታዋ በውስጡዋ ቤተመቅደስ የሚኖረውን ክርስቶስን በሰውነቷ ሸራ ላይ በመሣል ባልዋ ለቅድስና ሕይወት እንዲማረክ ወደ እርሱዋም እንዲሳብ ማድረግ የሚቻላት ናት ማለታችን ነው፡፡ በዚህም ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “እናንት ሚስቶች ሆይ ከባሎቻችሁ አንዳንዱ ለትምህርት የማይታዘዙ ቢኖሩ በፍርሃት ያለውን ንጹሑን ኑሮአችሁን እየተመከቱ ያለ ትምህርት በሚስቶቻቸው ኑሮ እንዲገኙ ተገዙላቸው”ብሎ ያስተማረው ቃል ይፈጸማል ማለት ነው፡፡(1ጴጥ.3፡1) ባሏ እግዚአብሔርን የሚፈራ ከሆነ ደግሞ ከባሏ ዘንድ “መልካም ያደረጉ ብዙ ሴቶች አሉ አንቺ ግን ከሁሉ ትበልጫለሽ፡፡ ውበት ሀሰት ነው ደም ግባትም ከንቱ ነው እግዚአብሔርን የምትፈራ ሴት ግን እርሱዋ ትመሰገናለች፡፡ ከእጅዋ ፍሬ ስጡአት ሥራዎችዋም በሸንጎ ያመሰግኑአታል” የሚል ውዳሴ ይቀርብላታል፡፡(ምሳ.31፡30-31)  እስቲ አምላክ ይህን ማስተዋል ለሁላችንም ያድለን!!! 

2 comments:

  1. ሃና በመንፈሳዊው ዓለም ሴት ልጅ ላስተዋላት ከገነትም ይልቅ የምትረቅ ናት፡፡ እኔ ስለሴት ልጅ ሳስብ በአግርሞት እሞላለሁ፡፡ አንድ ወቅት እግዚአብሔርን እንዲህ ብዬ ጠየቅሁት፡፡ ስለምን ነፍስን ለብቻዋ አልፈጠርካትም ? ስለምን ሥጋን ማኅደሯ አደረግኸት ? ብዬ ጠየቅሁት፡፡ ለካ የነፍስ መዳኗና አምላኩዋን በዐይኑዋ ማየቷ በሥጋዋ በኩል ነው!!! ይህም የተፈጸመው በሴት ልጅ ነው፡፡ የክርስቶስ የአጥንቱ አጥንት የሥጋው ሥጋ የሆነችው ሴት የተባለችውም ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፡፡ ሴት ማለት ደግሞ ክፋዬ ማለት ነው፡፡ እርሱ የእርሱዋ ክፋይ ሆኖ እኛን ክፋዩ አደረገን፡፡ እናንተ በሔዋን ሴት ስትባሉ፡፡ እኛ ወንዶች ደግሞ በአቤል ምትክ በተወለደው ሴት ሴት ተባልን፡፡ ስለዚህ ስለምን ሴት ልጅ ከነስሙዋ ድንቅ የሆነች ፍጥረት አትሆንም ሃና? ጥበብን የሚወድ እግዚአብሔር ሴት ልጅ የፍጥረት ጉልላት አድርጎ ፈጠራት፡፡በእርሱዋም ስሙ ጥበብ የሆነውን ክርስቶስን ተመለከትነው፡፡ በእርሱዋም እኛ ክርስቲያኖች ከአጥንቱ አጥንት ከሥጋው ሥጋ የሆንን የአካል ክፍሎቹ ሆንን፡፡(because we are members of His body of His flesh and His bones) ታዲያ ይህን የተረዳ እንዴት በሴት ልጅ ተፈጥሮ አይገረም!!!

    ReplyDelete
  2. Amen kale hiwot yasemaln tsegawn yabzalh edmi na tina yistiln yagelglot zemenh yarzmlh yibarklh .legam anbben endnreda tibebun yigletsln. wedmachinm yakoyiln...

    ReplyDelete