Wednesday, February 27, 2013

የዛሬ ገጠመኜ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
20/06/2005
ዛሬ አንድ የገጠመኝን ገጠመኝ ላውጋችሁ እንዲህ ነው፡- አንድ የልብ ወዳጄለሆነ ጉዳይ እፈልግሃለሁብሎ ወደ እርሱ በታክሲ አመራሁ የሥራ ቦታው ወደ መስቀል ፍራዎል አካባቢ ነበር፡፡ ሄድኩ በፍቅር ተወያየን ለእኔ ጥሩ አሳቢ ነበርና በእርሱ አምላኬን አመሰገንኹት፡፡ ከእርሱ ጋር ውይይቴን ከጨረስኩ በኋላ ከአምባሳደር ዐራት ኪሎ የሚለውን ታክሲ ይዤ ወደ ቤቴ አመራሁ፡፡
በመንገድ ላይ ሳለሁ ግን አንድ ወዳጄ ከክፍለሀገር ደወለልኝ፡፡ ስለ ግል ጉዳያችን ከተጠያየቅን በኋላ ወደ መጨረሻ ላይ ለመሆኑየአብርሃም ርስት ርስታችንየሚለውን ምንባብ ተመለከትከውን? አልኩት ተመልከቼዋለሁ ግን ካነበብኩት ስለቆየሁ እስቲ ትን አስታውሰኝ አለኝ፡፡ እኔምለአብርሃም በራሱ ምሎ በመሐላ መካከል የገባውና በሞቱ ርስቱን ለአብርሃምና የአብርሃምን እምነት ይዘው ላሉት ሊያወርስ ሰው ሆኖ በመስቀል ላይ ራሱን ስለሰዋው እግዚአብሔር ቃል የሚያትት ነው” ብዬ አስታወስኩት፡፡ እርሱም ፈላስፎች የሚያነሡትን ጥያቄ አስታውሶ እንዲህ አለኝ፡- “ክርስቶስ እግዚአብሔር ከሆነ እርሱ ሞቶ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት በከርሰ መቃብር ውስጥ ከነበረ በእነዚህ ሦስት ቀናት ውስጥ ዓለምን የሚመግባት ማን ነበር? ብለው ፈላስፎች ይጠይቃሉና ስለዚህ ምን ትላለህ? ብሎ ጠየቀኝ፡፡ ይህ ጥያቄ እንደው ለእነርሱ ከባድ መስሎአቸው ያነሱት ጥያቄ እንጂ ፍልስፍናን በማወቃቸው የጠየቁት ጥያቄ አይመስለኝም፡፡

Thursday, February 14, 2013

የአብርሃም ርስት ርስታችን




በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
07/06/2005
ቅዱስ ጳውሎስ ርስት እንዴት እንደሚወረስ ሲገልጥልን “ኑዛዜ ያለ እንደሆነ የተናዛዡን ሞት ማርዳት የግድ ነውና፡፡ ሰው ሲሞት ኑዛዛው ይጸናል ተናዛዡ በሕይወት ሲኖር ግን አይጠቅምም” ይለናል፡፡(ዕብ.9፡16-17)ይህ ክርስቶስ እኛን የርስቱ ወራሾች ሊያደርገን እንደ ሞተ ለማስረዳት የተጠቀመበት ኃይለ ቃል ነው፡፡
 ጥንተ ነገሩን ስንመለከት እግዚአብሔር አምላክ ለአብርሃም “በእውነት እየባረክሁ አባርክሃለሁ እያበዛሁ አበዛሃለሁ ብሎ በሌላ በማንም ሊምል ስላልቻለ በራሱ ማለለት፡፡”(ዕብ.6፡13-14) አብርሃም ይህን እግዚአብሔር የማለለትን መሐላ ይዞ ከልጆቹ ጋር በስደት በባዕድ ሀገር ኖረ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህ ሲናገር “አብርሃም የተባለው ርስት አድርጎ ሊቀበለው ወዳለው ስፍራ ለመውጣት  በእምነት ታዘዘ፡፡ ለእንግዶች እንደሚሆን በተስፋ ቃል በተሰጠው አገር በድንኳን ኖረ የተስፋ ቃል አብረውት ከሚወርሱ ከይስሐቅና ከያዕቆብ ጋር እንደ መጻተኛ በእምነት ተቀመጠ፡፡ መሠረት ያላትን እግዚአብሔር የመሠረታትንና የፈጠራትን ከተማ ይጠብቅ ነበርና” ብሎናል፡፡(ዕብ.11፡8-10) ይህ መሐላ የአብርሃምን እምነት ይዘው የርስቱ ወራሾች ሊሆኑ ለተጠሩት ሁሉ የሚሠራ መሓላ ነው፡፡

Wednesday, February 13, 2013

መንፈሳዊ እድገትና ተሃድሶ ይለያያሉ



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
07/06/2005
 መንፈሳዊ እድገት ማለት ታድሶ ማለት አይደለም፡፡ እኛ እኮ በክርስቶስ ታድሰን አዲሱን ሰው ክርስቶስን ለብሰናል ወይም ልክ እንደሙሉ ሕጻን አንድ ጊዜ ተወልደናል፡፡ የመጠን ያም ማለት የብስለት ለውጥ እንጂ የመልክ ወይም የማንነት ለውጥ የለንም፡፡ አሁን መልካችን ክርስቶስን መስሎአል በአዲስ ማንነት ደግሞ በሰማያዊ ልደት ተወልደናል፡፡ ከዚህ በኋላ ከእኛ የሚቀረው መንፈስ ቅዱስ በሚሰጠን ማስተዋል እየበሰልን ሙሉ ሰው ክርስቶስን ወደ መምሰል ማደግ ነው፡፡ የቤተክርስቲያንም ድርሻ መንጋዋን ዳግም በክርስቶስ ለተፈጠረበት መንፈሳዊ ከፍታ ማብቃት ነው፡፡ እርሱዋ ለልጆቹዋ እንደ እናት ናት፡፡
በእርሱዋ የተሟላ የሐዋርያትና የነቢያት ትምህርት አለ፡፡ በእነርሱ ውስጥ በጥምቀት ባደረውም መንፈስ ቅዱስ ክርስቶስን መስለው እንዲያድርጉ እንደየእድገታቸው መጠን ትመግባቸዋለች፡፡ መታደስ ማለት ይህን በአዲስ ተፈጥሮ በክርስቶስ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቀን አዲሱን ሰው ለብሰን የተፈጠርንበት ማንነታችን አርጅቶ እንደገና ወደ አዲስ ማምጣት ማለት አይደለም፡፡ እኛ እድሳታችን የተፈጸመው ልክ በመንፈሳዊ ልደት በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቀን የእግዚአብሔር ልጆች ስንሆን ነው፡፡ ልጅ ከሆንን ደግሞ ቀስ በቀስ ማደግ አለብን፡፡ ይህም ከፍጹምነት ወደ ፍጹምነት ማለት ነው፡፡ ወይም ከሚበልጠው ወደ ሚበልጠው የመንፈሳዊ ብስለት ማደግ ነው ለዚህም ማለቂያ የለውም፡፡
 መንፈሳዊ ወተትን የሚጋቱ ሕጻናት አሉ ወተቱ ለእነርሱ መሠረታዊና እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ነገር ግን ጥርስ ባወጡ ጊዜ ጥሬን ወደ መቆርጠም አጥንትን ወደ መጋጥ ሲመጡ ጠንካራውን መንፈሳዊ ምግብምን ሊመገቡ ይገባቸዋል፡፡ በዚህም ውስጥ አንዳች ነውርም የለበትም፡፡ ነገር ግን በዚህ ብቻ አያቆምም በመንፈሳዊ ከፍታ ልንሸመግል ይገባናል፡፡ ያም ማለት ለመንፈሳዊ ትምህርት የመጀመሪያ የሆነውን ትምህርት አውቀን(ወተት) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሰፈሩትን እውነታዎች በጥልቀት ተረድተን(ጠንካራውን ምግብ) ሙሉ ሰው በመሆን በመንፈስ ቅዱስ ወደ መመራት መድረስ መምጣት አለብን፡፡ ይህ ሁሉ ጤናማና በውስጡ አንዳች ነውር የሌለበት አካሉ በራሱ ሙሉ እንደሆነ የሚያድግበት መንፈሳዊ እድገት ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ግን በራሱዋ ሙሉ ናት ልጆቹዋን እነዚህን እየመገበች ታሳድጋቸዋለች፡፡ እንጂ በራሱዋ አትታደስም ቤተክርስቲያን ጥንትም ነበረች አሁንም አለች ወደፊትም ትኖራለች ምክንያቱም መሥራቹዋ ክርስቶስ መጋቢዋም መንፈስ ቅዱስ ዘለዓለማዊያን ናቸውና፡፡