Thursday, November 29, 2012

በድንግል ማርያም እናትነት ወንድምነትና እኅትነት ለእኛም



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
21/03/2005

አንዳንዶች ባይረዱት ነው እንጂ ቅድስት ድንግል ማርያም ለምድራዊቱ ቤተክርስቲያን ወይም ቤተክርስቲያን ለተሰኘነው ለእኛ አብነት የሆነች አማናዊቱ ቤተክርስቲያን ናት፡፡እኛም በእርሱዋ ተመስለን ለክርስቶስ ሙሽሪትም፣ እናቱም፣ ወንድምና እኅቱም፣ አገልጋዩም፣ ልጁም ተብለናል፡፡(ማቴ.12፡50) በእርሱዋም ለጌታ የታጨን እናቶች፣ ወንድሞችና እኅቶች እንዲሁም አገልጋዮችና ልጆች ስለሆንን ጠላት ዲያብሎስ ሁሌም ያሳድደናል፡፡ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለክርስቶስ እንዲሁ ናት፡፡እርሱዋ ለእርሱ እናቱ ብቻ አልነበረችም ሰውነቱዋን ለእርሱ ማደሪያነት ያጭች እኅቱም፣ አገልጋዩም፣ ልጁም ነበረች፡፡ እርሱዋ የቤተክርስቲያን አማናይቱ ምሳሌ ናት፡፡ እኛም በክርስቶስ ቤተክርስቲያን ተሰኝተናል፡፡ ስለዚህም ሰይጣን “በአንተና በሴቲቱ መካከል በዘሩዋና በዘርህ መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ”(ዘፍ.3፡15) የሚለው ቃል በእኛ ላይም ተፈጽሞ ጠላት ዲያብሎስ ዘምቶብናል፡፡



እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ታቦተ ጽዮን



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ኅዳር 20/2004 በማኅበረ ቅዱሳን ድኅረ ገጽ የተለቀቀ ጽሑፍ

እግዚአብሔር አምላክ ሕዝበ እስራኤልን ከግብጽ ባርነት ካወጣቸው በኋላ የአምልኮ ሥርዐታትን ይፈጽሙበት ዘንድ የምስክሩን ድንኳን፣ የቃል ኪዳኗ ታቦትንና ለአምልኮ ሥርዐቱ ማከናወኛ የሚያገለግሉ ልዩ ልዩ ንዋያተ ቅድሳትን እንዲሠሩ በሙሴ በኩል አዝዞአቸው ነበር፡፡ ከቃል ኪዳኗ ታቦት ውስጥም በእግዚአብሔር ጣት ዐሥርቱ ትእዛዛት የተጻፉበት የሕጉ ጽላት፣ አርባ ዓመት ሙሉ እስራኤላውያን በሲና ምድረ በዳ የተመገቡትን መና የያዘች መሶበ-ወርቅ፣ አሮን ለክህነት አገልግሎት ስለመመረጡ ምስክር የሆነችው ለምልማና ፍሬ አፍርታ የተገኘችው የአሮን በትር ይገኙባታል፡፡(ዕብ.9፡4)

ታቦተ ጽዮን በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትመሰላለች፡፡ ይህን ለመረዳት ግን ስለ ታቦተ ጽዮን አሠራርና መንፈሳዊ ትርጉም አስቀድመን ልንረዳ ይገባናል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ታቦተ ጽዮንን እንዲሠራ ብልሃትን፣ ጥበብን፣ ማስተዋልን፣ ዕውቀትን ይለይ ዘንድ መንፈሱን ያሳደረበትን ከይሁዳ ወገን የሆነውን ባስልኤልን መረጠ ፡፡(ዘፀ.25፡9) እርሱም እግዚአብሔር በሰጠው ማስተዋል ከማይነቅዝ እንጨት ርዝመቷ ሁለት ክንድ ተኩል፤ ወርዱዋም አንድ ክንድ ተኩል፣ ቁመቷም አንድ ክንድ ተኩል እንዲኖራት አድርጎ ታቦቷን ሠራት፡፡ በመቀጠል በውስጥም በውጪም በጥሩ ወርቅ ለበጣት፣ ከታቦቷም ዙሪያ የወርቅ አክሊልን አደረገላት፡፡ ካህናት ታቦተ ጽዮንን ለመሸከም እንዲረዳቸውም በአራቱም መዓዘናት በወርቅ የተሠሩ ቀለበቶችንና በእነርሱም ውስጥ የሚገቡ ሁለት መሎጊያዎችን ሠራ፡፡ ከጥሩ ወርቅም የስርየት መክደኛውን በቃል ኪዳን ታቦቷ ላይ በርዝመቷና በወርደዋ ልክ ሠራ፡፡ የስርየት መክደኛውን እንዲጋርዱት አድርጎም ጥሩ ከሆነ ከተቀጠቀጠ ወርቅ ኪሩቤልን ሠራ፤ በስርየት መክደኛው ግራና ቀኝም አደረጋቸው፡፡ እነዚህ በጥሩ ወርቅ የተሠሩት ሁለቱ ኪሩቤል ፊታቸው ወደ ስርየት መክደኛው ሆኖ እርስ በእርሳቸው የሚተያዩ ተደርገው የተሠሩ ናቸው ፡፡ በዚህ በስርየት መክደኛው በሁለቱ ኪሩቤል መካከል  እግዚአብሔር ለሙሴ በመገለጥ ሰው ከባልንጀራው እንደሚነጋገር ያነጋግረው ነበር፤ ለሕዝቡ በደመና አምድ ይታያቸው ነበር፡፡(ዘፀ.25፡22፤33፡8-11)

Wednesday, November 28, 2012

በቤተክርስቲያን የሚታየው የሥላሴ መልክ



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
19/03/2005

እያንዳንዱ ሰው በሦስትነቱ በሚመለከው እግዚአብሔር አርዓያና አምሳል እንደተፈጠረ ቤተክርስቲያን ደግሞ በሥላሴ ውስጥ ባለ ልዩነትና አንድነት አምሳል ልጆችን በመውለዱዋ ሥላሴን ትመስለዋለች፡፡ እግዚአብሔር ምንም በአካልና በግብር ሦስት ብንለውም አንድ እግዚአብሔር ብለን እንደምንጠራውና አካለቱም በየራሳቸው ሕልዋን እንደሆኑ ቤተክርስቲያንም እያንዳንዱ አማኝ ክርስቲያን በአንድ ክርስቶስ አካል አንድ ሲሆን አንዱ ካንዱ የሚለይበት የየራሱ አካል አለው፡፡ እግዚአብሔር በሦስነቱ ሳይነጣጠል በሰው ሰውነት ውስጥ እንዲያድር እንዲሁ የቤተክርስቲያን አባላት የሆኑ ሁሉ አንዱን የእግዚአብሔርን መንግሥት ይወርሳሉ፡፡ በቤተክርስቲያን ስልጣንና ነጻ ፈቃድን በተመለከተ ምንም ጠብ እንደሌለ ሁሉ ፍጹም አንድነትም አለ፡፡ በቤተክርስቲያን አንዱ ሁሉን ጠቅልሎ መያዝ ፈጽሞ የለም፡፡ እንደ ኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ “ቤተክርስቲያን ዓለማቀፋዊት ናት” ሲል ብዙሃን በልዩነታቸው አንድ የሚሆኑበትን በሥላሴ የሚታየውን ታላቅ የሆነውን ምሥጢር ታሳቢ በማድረግ ነው፡፡

Tuesday, November 27, 2012

መስቀሉን ባሰብኩ ቁጥር



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
18/03/2005
የመስቀሉን ነገር ሳስብ እጅግ ድንቅ ግርምም ይለኛል፡፡ በጥምቀት በዚህ መስቀል ላይ ከክርስቶስ ጋር ተሰቀልን፡፡ በዚሁ መስቀል ላይ እርሱን ለበስነው፡፡ በዚሁ መስቀል ላይ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ በመሆን አባ አባ የምንልበትን የልጅነትን መንፈስ ተቀበልን፡፡ ስለዚህ ዲያቆን እስጢፋኖስ ክርስቶስን መስሎ “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያቁምና ይቅር በላቸው” ብሎ ጸለየ፡፡ በመስቀሉ ገነት ወደ ተባለው ክርስቶስ ገባን፡፡ ወደ ውስጥ ስንዘልቅ አማናዊው ዕፀ ሕይወት ወደ ተባለው ጎኑ በመቅረብ  ከፈሰሰው ክቡር ደሙ ጠጣን፤ መሥዋዕት አድርጎ ካቀረበው ሥጋውም በልተን ዘለዓለማዊ ሕይወትን አገኘንበት፡፡
 ትንሣኤአችንም የሚፈጸመው በቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ነው፡፡(ዮሐ.6፡54) በዚህም ወደ መንግሥቱ ለዘለዓለም እንኖር ዘንድ ገባን፡፡ ቢሆንም አሁን ወደ መንግሥቱ መግባታችን ላይታወቀን ይችላል አልተገለጠምና፡፡ ሲገለጥ ግን ሕይወታችን ከእርሱ ጋር እንደሆነች እናስተውላለን፡፡(2ቆላ.3፡3) በተጠመቅንና ከቅዱስ ሥጋውና ከክቡር ደሙ በበላን ጊዜ ከእርሱ ጋር እንደተነሣን ያኔ እንረዳለን፡፡ ሕይወታችን እርሱ አብ ነው፣ ሕይወታችን እርሱ ክርስቶስ ነው፣ ሕይወታችን እርሱ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡እርሱን እኛ ስናመልከው እርሱ ደግሞ በእኛ ላይ ያድራል፡፡(ራእ.7፡15)

Tuesday, November 20, 2012

በዓለ ሲመቱ ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ኅዳር 11/2005
(ከዚህ በፊት በማኅበረ ቅዱሳን ድኅረ ገጽ የተለቀቀ)
የሰው ልጅ በገነት እንደ ቅዱሳን መላእክት በቅድስና አምላኩን በማመስገን በደስታ ይኖር ነበር፡፡ ነገር ግንክፉና ደጉን ከምታሳውቀው ዕፀ በለስ እንዳትበላተብሎ የተሰጠውን ትእዛዝ በመተላለፉ ምክንያት ከአምላኩ ተለየ(ዘፍ.36)፡፡እግዚአብሔር በአርአያውና በአምሳሉ የፈጠረው ሰው ክብሩን አጣ፣ ጸጋው ተገፈፈ፣ ፈጣሪውንም አሳዘነ፡፡ ቅዱሳን መላእክትም በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ የተፈጠረው ሰው ከክብሩ ተዋርዶ ሲመለከቱ ተከዙ፡፡

የሰው ልጅ ጠፍቶ እንዲቀር ያልወደደው እግዚአብሔር ወልድ ሰውን ለማዳን ራሱን ዝቅ አድርጎ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሱዋ ነፍስ ነስቶ ተወለደ፡፡ቅዱሳን መላእክትም ከላይ ከአርያም ከአባቱ ሳይለይ እግዚአብሔር ወልድ ሰውን ለማዳን ሲል በግዕዘ ሕፃናት ተወልዶ፣ በእናቱም እቅፍ ሆኖ፤ እንስሳት እስትንፋሳቸውንእያሟሟቁት በማየታቸው ተደነቁ፡፡ ሰውን ለማዳን ሲል ራሱን ዝቅ በማድረግ የባርያውን አርአያ እንደነሣ አስተውለውስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት፣ ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ” (ሉቃ.214) ብለው አመሰገኑት፡፡

Friday, November 9, 2012

ከእነዚህ የወጣ ማንኛውም ትምህርት ኦርቶዶክሳዊ አይደለም!!!!



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
1/03/2005
ማንም ሊገነዘብ የሚገባው እውነት ይህ ነው፡፡ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን(oriental church) ትምህርት በሦስት መሠረታዊ እውነታዎች ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ እነዚህም በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ፣እግዚአብሔር በገለጣቸው እውነታዎች ላይ(በመንፈስ ቅዱስ)፣ ቤተክርስቲያን በተቀበለቻቸው በተለይ 1-5 ክ/ዘመን በተነሡ ቅዱሳን አባቶች ትምህርት ላይ ነው፡፡ ወይም በዐራት ሕግጋት ላይ የተመሠረቱ ናቸው እነዚህም 1. በተፈጥሮአዊ ሕግ (1ቆሮ.11፡14፤15) 2. በሕሊናዊ ሕግ ላ(ሮሜ.2፡14) 3. በመጽሐፋዊ ሕግና በመንፈሳዊ ሕግ ላይ(God revelation.1ቆሮ.2፡12-16፤)ናቸው፡፡
አንድ ኦርቶዶክሳዊ ትምህርት እነዚህን ማዕከል ያደረገ መሆን አለበት፡፡ከእነዚህ ዐራት መሠረታዊ የሕግ ምንጮች ጋር የተጣጣመ ሊሆን ይገባዋል፡፡ የእነዚህም አቀራረባቸው:- በእምነት(በቀጥታ በመቀበል፡፡ ይህ ከአእምሮ መረዳት በላይ የሆኑ እግዚአብሔር የገለጣቸውን እውነታዎችን ይመለከታል፡፡ ለምሳሌ የእግዚአብሔር ወልድን ከአብ መወለድን በተመለከተ፤የሥጋና የመለኮት ተዋሕዶን በተመለከተ፣ የሥላሴን አንድነትና ሦስትነት፣ ወይኑ ወደ ደመ መለኮት የሕብስቱም ወደ ሥጋ መለኮት የመለወጥን ምሥጢርና ሌሎቹም ይገኙበታል) እና በምክንያት (logic or reason) ላይ የተመሠረቱ መሆን አለባቸው፡፡ ይህ በተፈጥሮአችንና በሕሊናችን ለተሠሩት ሕግጋት ትንታኔ የምንሠጥበት መንገድ ነው፤እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ እንድንረዳቸው የሆኑትንም ያካትታል፡፡

"መዝጊያውን አንኳኩ ይከፈትላችኋል" (የኅዳር ወር ምንባብ)



ትርጉም ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
(ቅዱስ ዮሐንስ ዘደማስቆ)
30/02/2005
ቅዱስ ዮሐንስ ዘደማስቆ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብን በተመለከተ እንዲህ ብሎ ጽፎልናል፡፡ “ከመንፈሳዊ እውቀት በላይ እጅግ አስደሳችና ጠቃሚ የሆነ እውቀት ምን አለ? እውቀት ለአንድ ለባዊት ነፍስ ብርሃኑዋ ነው፡፡ የእውቀት ተቃራኒ የሆነው አላዋቂነት ደግሞ በጨለማ ይመሰላል፡፡ የብርሃን አለመኖር ጨለማን እንዲያመጣ እንዲሁ የእውቀት ጉድለት ድንቁርናን ያመጣል፡፡ ስለዚህም አላዋቂነት ለእንስሳት እንጂ ለሰው ልጅ አይደለም፡፡ አንድ በተፈጥሮ የማወቅና የማገናዘብ ችሎታ የተሰጠው ፍጥረት ከእውቀት የራቀ ከሆነ ቁጥሩ ከእንስሳት ይሆናል፡፡ እውቀት ስል ግን እውነተኛውን እውቀት ማለቴ ነው፡፡ እውነተኛ እውቀትን የምናገኘው ከራሱ ከእግዚአብሔር ወይም እርሱ ካለመኖር ወደመኖር ካመጣቸው ፍጥረታት ነው፡፡ ሀሰተኛ እውቀት የሚባለው ግን በሥነፍጥረቱ ለእኛ ያልተሰጠ ወይም ጨርሶ ካልተፈጠረ ነገር የሚመነጨውን እውቀት ነው፡፡ እርሱ ሐሰተኛ እውቀት ይባላል፡፡

Wednesday, November 7, 2012

ቅድስት ኤልሳቤጥና ቅድስት ድንግል ማርያም በንጽጽር(ቅዱስ ኤፍሬም)



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
29/02/2005
አረጋዊቱ ኤልሳቤጥ የነቢያት ፍጻሜ የሆነውን ዮሐንስ መጥምቅን በእርጅናዋ ወለደች፤ ታናሽዋ ብላቴና ቅድስት ድንግል ማርያም ግን የመላእክትን ጌታ ወለደች፡፡ ከአሮን ወገን የሆነችው ኤልሳቤጥ በምድረ በዳ የሚጮኸውን የሰው ደምፅ ወለደች፤ የዳዊት ልጅ የሆነች ቅድስት ድንግል ማርያም ግን ለሰማያዊው ንጉሥ ቃሉ የሆነውን ክርስቶስን ወለደችው፡፡ የካህኑ ዘካርያስ ሚስት የሆነችው ቅድስት ኤልሳቤጥ በጌታ ፊት የሚሄድ መልእክተኛውን ወለደች፤  የዳዊት ልጅ የሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ግን ምድሪቱን የሚገዛት እግዚአብሔርን በሥጋ ወለደች፡፡  መካን የሆነች መኅፀን ሰዎችን ለንስሐ የሚያዘጋጅ ልጅን ወለደች፡፡ ድንግል የሆነች ማኅፀን ግን የሰው ልጆችን ኃጢአት የሚያስወግድ ልጅን ወለደች፡፡ ኤልሳቤጥ ሰዎችን ከእግዚአብሔር ጋር የሚያስታርቅ ልጅን ወለደች፡፡ ድንግል ማርያም ግን በኃጢአት ያደፈችውን ምድር በደሙ የሚነጻ ልጅን ወለደችልን፡፡ በፅንሰት ታላቁ የሆነው ዮሐንስ ለያዕቆብ ቤት ብርሃን ሆናቸው፡፡ በፅነሰት ታናሹ የሆነው የድንግሊቱ ልጅ ክርስቶስ ግን ለዓለም ሁሉ የጽድቅ ፀሐይ ሆነ፡፡

Saturday, November 3, 2012

ድንቅ ግን እውነት



ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
23/02/2005
ክብር ይግባውና ስለ ድንቅ እምነቱ እግዚአብሔር አብርሃምን ለአሕዛብ አባት አደረግሁ አለው፡፡(ዘፍ.17፡7-8፤ሮሜ.4፡12) ድንቅ ስለሆነውም በእምነት መታዘዟ እግዚአብሔር ሣራን የአሕዛብ እናት አደረጋት፡፡ ስለእርሱዋ እግዚአብሔር “እባርካታለሁ ደግሞም ከእርሱዋ ልጅ እሰጥሃለሁ እባርካታለሁ የአሕዛብም እናት ትሆናለች፡፡”(ዘፍ.17፡16)ብሎ ተናገረላት፡፡
ንጉሥ ዳዊትም እንዲሁ ከልጅነቱ ጀምሮ ልቡን የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ፣ አንደበቱን የመንፈሱ አገልጋይ በማድረጉ እንደ ልቤ ተባለ፡፡ ከእርሱም ዘር ክርስቶስ እንዲወለድ “ዘርህን ለዘለዓለም አዘጋጃለሁ፤ ዙፋንህንም ለልጅ ልጅ እመሠርታለሁ፡፡”(መዝ.88፡4) እንዲሁም “ከወገብህ የሚወጣውን ዘርህን ከአንተ በኋላ አስነሣለሁ መንግሥቱንም አጸናለሁ፡፡ እርሱ ለስሜ ቤትን ይሠራል የመንግሥቱም ዙፋን ለዘለዓለም አጸናለሁ” አለው፡፡ ይህን ቅዱስ ዳዊት በመንፈስ አስተውሎ “ጌታዬ ሆይ! እግዚአብሔር ሆይ ! እስከዚህ ያደረስኸኝ እኔ ማን ነኝ? ቤቴስ ምንድን ነው? ጌታዬ እግዚአብሔር ሆይ! ይህ በፊትህ ጥቂት ነበረ፤ ስለባሪያህም ቤት ደግሞ ለሩቅ ዘመን ተናገርህ፤ ጌታዬ እግዚአብሔር ሆይ! ይህ የሰው ሕግ ነው፡፡(2ሳሙ.7፡12-4፤ 18-19) ብሎ ጌታውን አመሰገነ፡፡ በዚህ ቦታ ይህ “የሰው ሕግ ነው” ያለው “ክርስቶስን መምሰል” ነው፡፡  ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ለማስረዳት "የሚያምኑ ሁሉ ይጸድቁ ዘንድ ክርስቶስ የሕግ ፍጻሜ ነውና” ብሎ ጽፎልናል፡፡(ሮሜ.10፡4)