Friday, September 28, 2012

ስለንስሐ የተላከ መልእክት



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
18/01/2005
ውድ እና ከእግዚአብሔር ጋር ያለህን ሕብረት በእጅጉ የምናፍቅልህ ወገኔ ሆይ እንደምን አለህልኝ? ውድ ክርስቲያን ወገኔ ሆይ ንስሐ ማለት ሕመምን ለዶክተር እንደ መናገር ማለት ነው፡፡ አንድ ሰው ሕመሙን ቢደብቅ ሕመሙ ወደማይደን ደረጃ ይለወጥና ነፍሱንም ሥጋውንም ያጠፋል፡፡ እንዲሁ በንስሐ መድኀኒትነት ከኃጢአት ቁስል ራሱን የማይፈውስ ክርስቲያንም ነፍሱንና ሥጋውን በገሃነም እሳት ያጠፋል፡፡ ውድ ክርስቲያን ወገኔ ሆይ! በክርስቶስ አምላክነት አምነን በመጠመቃችን ክብር ይግባውና ሁላችንም የክርስቶስ ወታደሮች ሆነናል፡፡ ስለዚህም ከኃጢአት ጋር በምናደርገው ፍልሚያ ልንቆስል እንችላለን፡፡ አንድ ቁስለኛ ደግሞ የሐኪም እርዳታ በእጅጉ ያስፈልገዋል፤ ያለበለዚያ ሕመሙን ቢደብቅ ቁስሉ ወደ ጋንግሪንነት ተለውጦ የማይድን ይሆንና በሞት ይወሰዳል፡፡ እንዲህ ዓይነት ሰው አንዴ ሞቷልና ሊድን አይችልም፡፡ ክርስቲያን ወገኔ ሆይ! ኃጢአት ለነፍሳችን እንደ በሽታ ነው፡፡በሽታ ጋር ደግሞ እንዲኖር የሚፈቅድ ሰው የለም፡፡ ስለዚህ ወደ ነፍሳችን መድኃኒት ወደ ክርሰቶስ ቅረብ፡፡ እርሱ ሕመምተኞችን እንጂ ጤነኞችን ሊፈውስ አልመጣምና፡፡(ማቴ.912) 
ወገኔ ሆይ ንስሐ ለመግባት አትፍራ፡፡ ወደ ካህን ስትቀርብ ወደ ክርስቶስ እንደቀረብክ ተረዳ፤ በእነርሱ አድሮ ይቅር የሚለን እርሱ ነው፡፡ ይህንን በምን እናረጋግጣለን ካልከኝ? ከታች እንደሚከተለው በጥቅስ አስደግፌ አቅርቤልሃለሁ፡፡