Friday, April 27, 2012

አትንቀፍ እንዳትነቀፍ አትፍረድ እንዳ…”



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
19/08/2004
ቅዱስ ይስሐቅ ሰው በክፉም ይሁን በደግ ዐይኖቹ መታወራቸው አይቀርም ይለናል፡፡ በኃጢአት ውስጥ ያለ ሰው ዐይኖች ጽድቅን ማየት ይሳናቸዋል፡፡እንደነዚህ ዐይነት ወገኖች የሰዎች ኃጢአት እንጂ የጽድቅ ሥራቸው ወይም መልካም የሆነው ተፈጥሮአቸው አይታያቸውም፡፡ ነገር ግን የጻድቅ ሰው ዐይኖች የሰዎችን ድክመትም ሆነ ነውር ወይም ኃጢአት አይመለከቱም፡፡ሁሉም በእነርሱ ዘንድ ብሩካን ናቸው፡፡ እንዲህ ሲባል ግን ኃጥእ ጽድቅን አያቃትም ማለት ሳይሆን ወደ ኃጢአት ፈቃድ ያደላል ሲለን ነው፡፡ እንዲሁ ጻድቅ ሰውም የሰዎች ጉድለትና ድክመት ወይም ኃጢአት ሳይሆን አስቀድሞ የሚታየው የእነርሱ መልካምነት ነው፡፡
ጻድቅ ሰው የሰውን ደካማ ጎን ሳይሆን ጠንካራውን ይመለከታል፤ ስለዚህም በዐይኑ ውስጥ የገባውን ጉድፍ ለማውጣት በወንድሙ ዘንድ የታመነ ነው፡፡ በጽድቅም ምክንያት ዐይኖቹ ብሩሃን ናቸውና በወንድሙ ዐይን ውስጥ ያለውን ጉድፍ ዐይኑን ሳይጎዳው ጉድፉን ብቻ ለይቶ ያወጣለታል፡፡ ወንድሙም ከሕመምና ከስቃይ ጤናማ ስለሚሆን እርሱም እንደ ጻድቅ ወንድሙ አጥርቶ ማየት ይጀምራል፡፡ እንዲህ ነው መልካም ወዳጅ፡፡ ጻድቅ ሰው እንዲህ ነው፡፡ አይነቅፍም፤ አይቆጣም የወንድሙን ነውር ወይም ድክመት በአደባባይ አያወራም፤ በወንድሙ ላይ አይታበይም፤ ወንድሙ ከእርሱ እንደሚሻል ይቆጥራል፤ ስለወንድሙ መዳን በአምላክ ፊት ያነባል፤ ወንድሙን ከስህተት መንገድ ለመመለስ  ነገሮችን ሁሉ በጥንቃቄ ይከውናል፡፡

Thursday, April 19, 2012

እናት



በወንድም ሸዋዓለም ፈቃዱ
12/08/2004

መነሻ ዳርቻ ፍጻሜ የሌለው፤
ጥንቱን የማላውቀው ፍጹም የማለየው፤
አለ አንዳች ስበት ከስሜት የጸዳ፤
ከእናት ያጣበቀ ከእናት የተቀዳ፡፡
እማዬ ፡- ያኔ… ያ…ኔ ክፉውን ከደጉ ያለየሁኝ ለታ፤
በቅጽበት ዐይን ያልተለየኝ ላፍታ፤
ከጡቶችሽ ምጌ ከልቤ ያኖርኩት፤
አንዳች ምሥጢር አለ እኔ ያልገለጽኩት፡፡
ካንቺ የሰረፀ ያ  ኃያሉ ፍቅርሽ ፤
ከየት ቋንቋ ላምጣ እንደምን ልግለጽሽ፡፡
እማ… እማዬ… እኔ ብቻ ሳልሆን እኔን የሚመስሉ፤
ሰው ሁነው ተፈጥረው በዓለም ዙሪያ ያሉ ፤
ስለእናት አዚመው ስለእናት ቢቀኙ፤
ዓለምን ቢዞሩ ገላጭ ቃል ቢያገኙ፤
አልሆነላቸውም ምንም ቢባዝኑ ፤
ምንም ቢፈትሹ የትም ቢኳትኑ፡፡
ስለዚህም መግለጫ ቃል ቢያጡ፤
በአንደነት በጋራ ዓለሜ ናት ብለው ለአንቺ ስም አወጡ፡፡
እኔስ የእኔ እናት፣ ውዴ የእኔ ሕይወት፣ ስላንቺ ምንም አልልም፤
ከቶም አልጽፍልሽም፤ ዝምታ እንጂ አንቺን ቃላት አይገልጽሽም፤
ስለአንቺ አላወራም አልዘምርልሽም፤
ፈጣሪ ሲፈጥርሽ አልፈጠረልሽም፤
በምድር የሚገኝ ገላጭ ቃል የለሽም፡፡

“…በተቀደሰው ተራራህ ማን ይኖራል?”(በቅዱስ ጀሮም)



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
12/08/2004
መግቢያ
ቅዱስ ጀሮም የላቲን አባቶች ከሚባሉት ውስጥ አንዱ ሲሆን የታሪክ ጸሐፊ፤ የቅዱሳት መጻሕፍት ተርጓሚ፤ እና የቤተክርስቲያን ጠበቃዎች ከሚባሉት ውስጥ የሚመደብ ቅዱስ ነው፡፡ ለዛሬ ከእርሱ ሥራዎች ውስጥ የዳዊት መዝሙር 14ን ከሞላ ጎደል የተረጎመበትን ጽሑፍ ተርጉሜ አቅርቤላችኋለሁ፡፡
መዝሙር 14(15)
“የዳዊት መዝሙር”
1.      አቤቱ በድንኳንህ ውስጥ ማን ያድራል?
በተቀደሰውም ተራራህ ማን ይኖራል?
2.     በቅንነት የሚሄድ፣ ጽድቅንም የሚያደርግ፣
በልቡም እውነትን የሚናገር፡፡
3.     በአንደበቱ የማይሸነግል፣
በባልንጀራው ላይ ክፋትን የማያደርግ፣
ዘመዶቹንም የማይሰድብ፡፡
4.    ኃጢአተኛ በፊቱ የተናቀ፣
እግዚአብሔርንም የሚፈሩትን የሚያከብር፣
ለባልንጀራው የሚምል የማይከዳም፡፡
5.     ገንዘቡን በአራጣ የማያበድር፣
በንጹሑ ላይ መማለጃን የማይቀበል፡፡
እንዲህ የሚያደርግ ለዘለዓለም አይታወክም፡፡
 ጀሮም ትምህርቱን እንዲህ ይጀምራል፡- ከርእሱ እንደምንመለከተው “የዳዊት መዝሙር” ይላል፡፡ ዳዊት የክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡(ይህን አስመልክቶ የሰጠውን ትርጓሜ ወደፊት እጽፈዋለሁ) ከዚህ በተጨማሪ ግን ዘጸአትን ስናነብ እስራኤላውያን በዐሥራ ዐራተኛው ዕለት ከግብጽ ባርነት የተላቀቁበትን ዕለት ቀንዱ ያልከረከረ ጥፍሩ ያላረረ በግ እንዲሠው መታዘዛቸውን እናስታውሳለን፡፡(ዘጸአ.12፡6) በዐሥራ ዐራተኛው ቀን ጨረቃ ሙሉ በሆነችበት ዕለት ምድሪቱን በብርሃኑዋ በምታበራበት ጊዜ መሥዋዕቱን እንዲያቀርቡ እስራኤላውያን ታዘዋል፡፡ በዚህም በሙሉ ቅድስና ሕይወት ተገኝተን ከመሥዋዕቱ ልንቀበል እንዲገባን ያስተምረናል፡፡

Tuesday, April 17, 2012

“አብዝቶ የመመገብ ጣጣው” (በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)



ትርጉም ዲ/ንሽመልስ መርጊያ
09/08/2004
ከዚህ በፊት በማኅበረ ቅዱሳን ድኅረ ገጽ የተለቀቀ ጽሑፌ ቢሆንም ከጊዜው ጋር ተስማሚ ሆኖ ስላገኘሁት በድጋሚ አቅርቤዋለሁ

መግቢያ
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የዮሐንስን ወንጌል በተረጎመበት በ፳፩ ኛው ድርሳኑ “ ጌታችን በእናታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ጥያቄ በቃና ሰርግ ላይ ስለምን ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት እንደቀየረው  ከአብራራ በኋላ ከዛሬ 1500 ዓመት በፊት በአሁኑ ጊዜ እንደ አዲስ ግኝት ተደርገው የሚታዩትን አብዝቶ በመመገብ የሚመጡትን የጤና ጉድለቶች ጽፎልን እናገኛለን ፡፡ ጽሑፉ ተተርጉሞ እንዲህ ቀርቦአል

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት ያኔ እንደቀየረ ዛሬም እኛን ድካማችንንና እንደ ወራጅ ውሃ በአንድ ቦታ ጸንቶ መቆየት የተሣነውን የሥጋ ፈቃዳችንን ከመቀየር አልተቆጠበም ፡፡ ዛሬም አዎን ዛሬም ልክ እንደውሃ ቀዝቃዛ ፣ደካማና ፣ ያልተረጋጋ ጠባይ ያለቸው ሰዎች አሉ ፡፡ እነዚህን ፈቃዶቻችንን ወደ ጌታችን አናምጣቸው ፤ እርሱ ወደ ወይንነት ይቀይራቸዋል  ፡፡  ከዚያም በኋላ ውኃ ሆነው ከእንግዲህ አይቀጥሉም ፡፡ ነገር ግን ለራሳቸውና ለሌሎች ደስታን የሚሰጡ አካላት ይሆናሉ ፡፡
በውሃ የተመሰሉት እነማን ናቸው ? ለዚህ ከንቱ ዓለም ሕሊናቸውን ያስገዙ ወገኖች ፣ የዚህን ዓለምን ቅምጥልነት ፣ አለቅነትንና ክብርን የሚሹ አይደሉምን ? እነዚህ ፍቃዶቻችን እንደውኃ የሚፈሱ ፣ ፈጽሞ ያልተረጋጉ ፣ ለአመፃ የሚፋጠኑ ቁልቁል የሚምዘገዘጉ ውኆች ናቸው ፡፡

የትንሣኤው መልእክት



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
09/08/2004
ቅዱስ ጳውሎስ “ፋሲካችሁ ክርስቶስ ታርዶአልና ስለዚህ በቅንነትና በእውነት በዓልን እናድርግ እንጂ በአሮጌ እርሾ በክፋትና በግፍ እርሾ አይደለም”(1ቆሮ.5፡8)አለን፡፡ በዚህ ቦታ በክርስቶስ የተሰበከችውን ወንጌል በእርሾ መስሎ ማስተማሩን እናስተውላለን፡፡ ስለዚህም ለእኛ ክርስቲያኖች የሕይወት ዘመናችን በሙሉ የበዓል ቀን ነው፡፡(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ) ቅዱስ ጳውሎስ “በዓል እናድርግ” ሲለን ግን እንደ አይሁድ የዳስ በዓልን ወይም ከግብጽ ባርነት ነጻ የወጡበትን ፋሲካቸውን ማለቱ እንዳልሆነ ሁላችንም መረዳቱ አለን፤ አስቀድሜ እንደ ተናገረኩት እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ለሚነሡ ሁሉ የሚበቃ የእግዚአብሔር በግ ክርስቶስ ታርዶአልና በዓልን አድርጉ ሲለን ነው፡፡
 ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ካለው ጥልቅ ፍቅር የተነሣ ራሱን አንድ ጊዜ መሥዋዕት አድርጎ በማቅረቡ ከጨለማ ወደሚደንቅ ብርሃን፣ ከባርነት ወደ ነጻነት፣ ከድሮው አዳማዊው ተፈጥሮ ክርስቶስን ለብሰን ወደምንገኝበት ሰብዕና አሸጋግሮናል፡፡ እነሆ በእርሱ የድኅነት ሥራ ሀገራችን በሰማይ ሆኗል፡፡ ስለዚህም አነጋገራችን፣ አመጋገባችን፤ አለባበሳችን፤አኗኗራችን ሁሉ ተለውጦአል፡፡ ከእንግዲህ ደስታችን በምድራዊው ምግብና መጠጥ አይደለም፡፡ ነገር ግን ልክ እንደ ቅዱሳን መላእክት መንፈስ ቅዱስ በሚሰጠን መጽናናት ሆኖአል፡፡ ጌታችን ለእኛ ካደረገው ከዚህ ታላቅ ቸርነት በላይ ሌላ ቸርነት አለን? ስለእኛ መዳን ሲል እግዚአብሔር ቃል ሰው ሆነ፤ስለእኛ ጭንቅ የሆነ ሕማምን ተቀበለ፣ በሞቱ ሞትን አጥፍቶ እኛን ከሰይጣን ባርነት ነጻ አውጥቶ አዲስ ሕይወትን ሰጠን፡፡ ሰውነታችን ማደሪያው ቤተመንግሥቱ ሆነ፡፡


Friday, April 13, 2012

“ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ”?(በሳልማሱ ኤጲፋንዮስ)


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/08/2004
በዛሬይቱ ቀን እንግዳ የሆነ ነገር ተከሰተ፡፡ እነሆ በዛሬይቱ ቀን ምድሪቱ በታላቅ ዝምታ ተዋጠች፡፡ ንጉሡዋ ክርስቶስ በውስጡዋ ተኝቶአልና በምድር ውስጥ ታላቅ ጸጥታ ሰፈነ፡፡ እንዲሁም በዛሬይቱ ቀን ምድር ከተፈጠረችበት ጊዜ ጀምሮ ሰምታ የማታውቀው ታላቅ የሆነ ንውጽውጽታ በውስጧ ተሰማ፡፡ ምክንያቱም በሥጋ በውስጡዋ ያደረው አምላክ በነፍሱ ወደ ሲኦል በመውረድ በሲኦል ያሉትን ነፍሳት በማስነሣት ወደ ገነት አፍልሶአቸዋልና፡፡ እግዚአብሔር በሥጋ በመሞቱ ሲኦል ታወከች፡፡ እርሱ በነፍሱ የጠፋውን የእግዚአብሔርን በግ አዳምን ሊፈልግ በዛሬይቱዋ ቀን ወደ ሲኦል ወርዶአልና፡፡
አምላክና የዳግማዊቱ ሔዋን ልጅ የሆነው ክርስቶስ አዳምንና ሔዋንን ከታላቅ ሃዘን ለማውጣት በዛሬይቱ ቀን በነፍሱ ወደ ሲኦል ወረደ፡፡ በዛሬይቱ ቀን ጠላቱን ድል የሚነሣበትን መስቀሉን ተሸከሞ ሞትን በሥጋው ተቀበለ፡፡ እርሱን የፈጠረው አምላክ በእርሱ አርአያ በሲኦል ተገኝቶአልና አዳም በፊቱ ክርስቶስ በነፍሱ ቆሞ ሲመለከተው በታላቅ ፍርሃትና መደነቅ ተሞልቶ በዙሪያው ላሉት ነፍሳት “የጌታችን ሰላም ከእናንተ ጋር ይሁን"ብሎ በታላቅ ድምፅ የምስራች አላቸው፡፡ ክርስቶስ ኢየሱስም “ከመንፈስህ ጋራ” ብሎ መለሰለት፡፡

Tuesday, April 10, 2012

የንስሐ ጸሎት (በቅዱስ ኤፍሬም)


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
03/08/2004
ጌታዬ ሆይ! ይቅር በለኝ፤ ወደ አንተ በንስሐ እመለስ ዘንድም ብርታትን ስጠኝ፡፡ እንደ ቅዱስ ፈቃድህ በቅድስና እመላለስ ዘንድ ወደ አንተ መልሰኝ፡፡ የአጋንንት መኖሪያና ጎሬ የሆነውን ልቡናዬን እባክህ ቀድሰው፡፡
ጌታዬ ሆይ! እኔ ከአንተ ዘንድ ለራሴ ይቅርታን እጠይቅ ዘንድ የማይገባኝ ጎስቋላ ሰው ነኝ፡፡ በተደጋጋሚ ንስሐ ለመግባት ቃል እገባና ለራሴ የገባሁትን ቃል መጠበቅ ተስኖኝ ዋሾ ሆኜ እገኛለሁ፡፡ አንተ ከወደቅሁበት የኃጢአት አዘቅት በተደጋጋሚ ብታወጣኝም እኔ ግን በገዛ ፈቃዴ በደጋጋሚ በኃጢአት ተሰነካክዬ እወድቃለሁ፡፡ ስለዚህም ጌታዬ ሆይ! በራሴ ላይ እፈርዳለሁ፤ በመተላለፌ ከአንተ ዘንድ የሚመጣብኝን ቅጣት ሁሉ በጸጋ እቀበላለሁ፡፡ አምላኬ ሆይ! ስንቴ ጨለማ የወረሰውን ልቡናዬን በጸጋህ ብርሃንህ አበራኸው? እኔ ግን ተመልሼ ወደ ተናቀውና ከንቱ ወደሆነው አስተሳሰብ ተመለስሁ፡፡ ይህን ባሰብኩ ቁጥር ሰውነቴ በፍርሃት ይርዳል፡፡ ነገር ግን የኃጢአት ፈቃዴ አይሎ በኃጢአት አዘቅት ውስጥ በተደጋጋሚ እወድቃለሁ፡፡

ክርስቶስ በዮሴፍ(በቅዱስ ኤፍሬም)



ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
2/08/2004
የአብርሃም አምላክ፣ የይስሐቅ አምላክ፣ የያዕቆብ አምላክ ሆይ አንተን ከሚያፈቅሩህ አገልጋዮችህ ንጹሕ ዘርን የመረጥህ፤ አባታችንን ያዕቆብን በእርጅናው ደስ ስላሰኘው ስለዮሴፍ የቅድስና ሕይወት እሰብክ ዘንድ ታላቅ ከሆነው ቸርነትህ የጸጋ ስጦታህን አብዝተህ ያፈሰስክልኝ አምላኬ ሆይ ስምህ ቡሩክ ይሁን፡፡
በዚህ ጻድቅ ወጣት ሕይወት ውስጥ የክርስቶስን ሁለቱን ምጽአቶች በምሳሌ እናገኛቸዋለን፡፡ የመጀመሪያው ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ወደዚህ ዓለም የመምጣቱን ሲሆን ሁለተኛው ግን በሚያስፈራ ግርማ ሆኖ ዓለምን ለማሳለፍ የሚመጣውን ምጽአትን ነው፡፡

Sunday, April 8, 2012

ሆሣዕና በሐዲስ ኪዳን



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
30/07/2004
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሕዝብና የአሕዛብ አባት ስለሆነው አብርሃም “አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤትን አደረገ አየም ደስም አለው”(ዮሐ.8፡56) ብሎ ተናገረለት፡፡ አብርሃም የጌታን የማዳን ቀን በእምነት የተረዳው እግዚአብሔር ዘርህን እንደ ሰማይ ከዋክብት አበዛልሃለሁ ብሎ በባረከው ጊዜ ነበር፡፡ ልጆቹ ቁጥራቸው ከሰማያውያን መላእክት ቁጥር እንደሚሆኑ ያለዘርዐ ብእሲ ከመንፈስና ከእሳት ተወልደው እሳታውያንና መንፈሳውያን መላእክትን እንዲመስሉ በመረዳቱ አብርሃም አባታችን ሐሤትን አደረገ፡፡ ስለዚህም አብርሃም “የሰሌን ጫፍ ለጋውን ያማረ የእንጨቱንም ፍሬ ይዞ በየቀኑ ዘንባባውን ይዞ ሰባት ቀን የመሠዊያውን ዙሪያ በመዞር አምላኩን አመሰገነ”(ኩፋሌ.13፡21-23) በዚህም “አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤትን አደረገ” የሚለው ቃል ተፈጸመ፡፡ ይህን ይዘው እስራኤላውያን በየዓመቱ የዳስ በዓልን የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ በቤተ መቅደስ ዙሪያ ሆነው በዓልን ያደርጉ ነበር፡፡(ዘዳ.16፡13) ነገር ግን እግዚአብሔር አምላክ ለወዳጁ ለአብርሃም እርሱንና በእምነት እርሱን የመሰሉትን እንዴት እንደሚያድናቸው ሊያሳየውና እግዚአብሔርን የሚፈሩ ዋጋቸው ምን እንደሆነ ሊያስተምርበት አባታችን አብርሃምን ልጁ ይስሐቅን እንዲሠዋለት አዘዘው፡፡




Friday, April 6, 2012

How shall it be?



By Shimelis Margia
29/07/2004
“For if the word spoken by angel was steadfast, and every transgression and disobedience received a jest recompense of reward, how shall escape” (Heb.2:2-3)
When St. Virgin Mary heard the greeting of that angel she disturbed, and didn’t understand the accidental revelation and unfamiliar speech of the angle. But she didn’t try to flee from hearing the word of the angel. Instead of this, in order to understand the message of the good tiding, she asked, “How this shall be, seeing I know not man?
St. Mary knows that to obey the word of Holy angel brings to her the grace of God; however, the message was contrasted with her vow that she vowed to God to live as Virgin. Therefore she asked the angel “seeing I know not a man” that means I vowed to God to continue as virgin, so how can it be?
The question of St. Mary is indeed correct. Because cancelling the vow to God is great sin. What says the bible in Ecclesiastes “better is it that you should not vow, that you should vow and not pay, suffer not your mouth to cause your flesh to sin.(Ecc.5:4-5)

Thursday, April 5, 2012

Christocentric asceticism



by D/n Shimelis Mergia
(one part of my SENIOR ESSAY)
28/07/2004
Any Christian teaching must be Christ centered. When I say Christ centered teachings, I mean that which follows the teaching and doing of Christ. Our Lord Jesus Christ taught about Asceticism practically, when he went to wilderness after His baptism. After He passed there with fasting and praying for forty days, He went back to the people and preached the Gospel to them.
 After He finished His preaching He usually went to the wilderness and led the solitary life by spending his time on prayer (Luke, 6:13). He was not restricted himself in wilderness or lived within the people. He has a time to be alone and to spend with his sheep. This is practical teaching of Jesus Christ about Asceticism.

Wednesday, April 4, 2012

በመስቀሉ የተፈጸመው ጋብቻ (በቅዱስ ያዕቆብ ዘስሩግ)



 ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
27/07/2004
ከእኛ ጌታ በቀር ለእጮኛው ራሱን አሳልፎ የሰጠ ሰው ማን ነው? ከቤተ ክርስቲያንስ በቀር የሞተ ሰው ለእርሱዋ ባልዋ ይሆን ዘንድ የምትሻ ሴትስ ማን ናት? ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ደሙን የጥሎሽ ስጦታ አድርጎ ያቀረበ ሰው ማን ነው? በመስቀል ላይ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ካቀረበ  ከአንድዬ በቀር ጋብቻውን በሕማሙ ያተመ ሰው ማን ነው ? ከሞተ አካል መጽናናት ታገኝ ዘንድ በእቅፎቹዋ ይዛ በሰርግዋ በዓል ላይ የተገኘች ሙሽራ ከዚህ በፊት ታይታ አትታወቅም ? በየትኛውስ የሰርግ በዓል ላይ ነው ሙሽራውን ሥጋ በመቁረስ በሰርጉ ለታደሙት እንግዶች መብል ይሆን ዘንድ የተሰጠው?
ሚስት በባሏ ሞት ምክንያት ፍቺን ትፈጽማለች ፡፡ ይቺ ሚስት ግን በውድ ባሏ ሞት ምክንያት ከእርሱ ጋር ፍጹም ተዋሕዶን አደረገች፡፡ እርሱ በመስቀል ላይ ራሱን በመሠዋት ቅዱስ የሆነውን ሥጋውን ሁሌም ትመገበው ዘንድ  ክብርት ለሆነችው ሙሽራው መብል አድርጎ አቀረበላት ፡፡ ጉኑንም በመወጋት ቅዱስ ደሙን በጽዋው ሞልቶ ሰጣት ፡፡ በዚህም ምክንያት በልቡዋ ያኖረቻቸው ጣዖታት ሁሉ ተወገዱላት ፡፡ በእርሱም ቅዱስ ቅባት ከበረች ፤ እርሱንም በጥምቀት ውኃ ለበሰችው ፤ በሕብስት መልክ ተመገበችው ፤ እንደ ወይንም ጠጣችው ፡፡ በዚህም ምክንያት ሁለቱ በፍጹም ተዋሐዱ  አንድ እንደሆኑ ዓለም ሁሉ አወቀ ፡፡

Tuesday, April 3, 2012

ማርታና ሞቤድ


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
26/07/2004
ሞቤድ ፋርሶች ሶርያን በተቆጣጠሩበት በ4ተኛው ክፍለ ዘመን የነበረ የዞሮአስትራኒዚም እምነት ተከታይና ፈራጅ ዳኛ ነው፡፡ ማርታ ደግሞ እርሱ በዳኝነት በተሰየመባት ከተማ ትኖር የነበረች በጥንታዊያን የሶርያ ክርስቲያኖች ዘንድ “የቃል ኪዳን ልጆች” ተብለው ከሚጠሩት ወገን ነበረች፡፡ ከዕለታት በአንዱ ቀን ለእርሱዋም እንደ ሌሎቹ ክርስቲያኖች ሁሉ ሰማዕትነት የምትቀበልበት ጊዜው ደርሶ ኖሮ ይህ የከተማዋ ዳኛ ወደ እርሱ አስጠርቶ እንዲህ ብሎ አስጠቅቆ ተናገራት፡-
 “አንቺ ሴት እኔ የምልሽን ብቻ ልብ ብለሽ አድምጪ፤ ምኞትሽን ተከትለሽ እኔ የምልሽን ከመፈጸም እንዳትዘገዪ ተጠንቀቂ፡፡ በእምነትሽ ትኖሪ ዘንድ አልከለክልሽም፤ እምነትሽን በተመለከተ እንደ ፈቃድሽ ማድረግ ትችያለሽ፡፡  ነገር ግን እኔ የማዝሽን ብቻ ፈጽሚ፤ እኔ የምልሽን የፈጸምሽ እንደሆነ ከሞት ቅጣት ትድኛለሽ፡፡ ማርታ ሆይ ይህ “ቃል ኪዳን” የምትይውን የማይረባ ነገርሽን ትተሽ ገና ወጣትና መልከ መልካም ሴት ነሽና ባል ፈልገሽ አግቢ፤ ሴቶች ልጆችንና ወንዶች ልጆችን ወልደሽ ኑሪ” ብሎ አዘዛት፡፡

Monday, April 2, 2012

ጦምን እንዲህ ብንረዳውስ?


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
25/07/2004
ምግብ ለሰው ልጆች በሕይወት መቆየት መሠረታዊ ነገር ሆኖ መቆጠር የጀመረው ከውድቀት በኋላ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ግን እንዲያ  አልነበረም፡፡ የቀደመው የአዳምና የሔዋን ሕይወት ምን ይመስል እንደነበር በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መረዳት እንችላለን፡፡ እርሱ ምንም እንኳ የእኛን ተፈጥሮ ገንዘቡ ያደረገ ቢሆንም እንዲያ በመሆኑ ምክንያት ልክ እንደ እኛ በሕይወት ለመቆየት ምግብ አላስፈለገውም፡፡ እንዲህ ስል ግን የእርሱን አምላክነት ዘንግቼው ሳይሆን የአዳምና የሔዋን በገነት የነበራቸውን ሕይወት ለማስረዳት ከእርሱ የተሻለ ማሳያ ስለሌለ ነው፡፡
አዳምና ሔዋን ከውድቀት በፊት በገነት ሳሉ በገነት ካሉ ፍራፍሬዎች ይመገቡ ነበር እንጂ በሕይወት መቆየታቸው በእነርሱ ላይ የተመሠረተ አልነበረም፡፡ ነገር ግን ከውድቀት በኋላ ሕይወታችን ከሆነው በአፍንጫችን እፍ ተብሎ ከተሰጠን መንፈስ ቅዱስ ስለተለየን መጽናናታችንና በሕይወት መቆየታችን በምግብ ላይ ተመሠረተ ሆነ፡፡