Tuesday, April 10, 2012

የንስሐ ጸሎት (በቅዱስ ኤፍሬም)


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
03/08/2004
ጌታዬ ሆይ! ይቅር በለኝ፤ ወደ አንተ በንስሐ እመለስ ዘንድም ብርታትን ስጠኝ፡፡ እንደ ቅዱስ ፈቃድህ በቅድስና እመላለስ ዘንድ ወደ አንተ መልሰኝ፡፡ የአጋንንት መኖሪያና ጎሬ የሆነውን ልቡናዬን እባክህ ቀድሰው፡፡
ጌታዬ ሆይ! እኔ ከአንተ ዘንድ ለራሴ ይቅርታን እጠይቅ ዘንድ የማይገባኝ ጎስቋላ ሰው ነኝ፡፡ በተደጋጋሚ ንስሐ ለመግባት ቃል እገባና ለራሴ የገባሁትን ቃል መጠበቅ ተስኖኝ ዋሾ ሆኜ እገኛለሁ፡፡ አንተ ከወደቅሁበት የኃጢአት አዘቅት በተደጋጋሚ ብታወጣኝም እኔ ግን በገዛ ፈቃዴ በደጋጋሚ በኃጢአት ተሰነካክዬ እወድቃለሁ፡፡ ስለዚህም ጌታዬ ሆይ! በራሴ ላይ እፈርዳለሁ፤ በመተላለፌ ከአንተ ዘንድ የሚመጣብኝን ቅጣት ሁሉ በጸጋ እቀበላለሁ፡፡ አምላኬ ሆይ! ስንቴ ጨለማ የወረሰውን ልቡናዬን በጸጋህ ብርሃንህ አበራኸው? እኔ ግን ተመልሼ ወደ ተናቀውና ከንቱ ወደሆነው አስተሳሰብ ተመለስሁ፡፡ ይህን ባሰብኩ ቁጥር ሰውነቴ በፍርሃት ይርዳል፡፡ ነገር ግን የኃጢአት ፈቃዴ አይሎ በኃጢአት አዘቅት ውስጥ በተደጋጋሚ እወድቃለሁ፡፡

ጌታ ሆይ ለእኔ ያሳየኸኝን የቸርነትህን ብዛት ዘርዝሬ ልጨርሰው እንዴት ይቻለኛል? እነዚህ ጸጋዎችህን ለእኔ ለማይገባኝ ሰው ሰጠሃቸው፤ ነገር ግን በስንፍናዬ በከንቱ አጠፋዋቸው፡፡ አንዳች ፍሬ ሳላፈራም ዘመኔን ጨረስኩት፡፡ አንተ በበረከቶችህ ሞላኸኝ እኔ ግን ለቸርነትህ አመፃን በብድራት መለስኩብህ ፡፡  
ነገር ግን ጌታ ሆይ! እንደ ታጋሽነትህና እንደርኅራኄህ መጠን ፍሬ አፍርታ እንዳልተገኘችው የበለስ ዛፍ ለዘለዓለም ነቅለህ እንዳትጥለኝ እለምንሃለሁ፡፡ ለዘለዓለም ሕይወት የሚያበቃ ፍሬን ሳላፈራ በዘለዓለማዊ እሳት እንዳታጠፋኝ እማጸንሃለሁ፡፡ ጌታዬ ሆይ! ለፍርድ በመጣህ ጊዜ አንተን ለመቀበል ሳልዘጋጅ እንዳልገኝ ጠብቀኝ፡፡ ድንገት በመጣህ ጊዜ የዘይት ማሰሮዬ ሞልቶ መብራቴን ከዘይቴ ጋር ይዤ እገኝ ዘንድ እርዳኝ፡፡ የሰርግ ልብሴን ሳልለብስ በመገኘቴ ከሰርግህ ቤትህ ወደ ውጭ እንዳልጣል አድነኝ፡፡ አንተ ርኅሩኅ ጌታና ሰውን የምትወድድ ነህና ምህረትህ በእኔ ላይ ትብዛ፡፡ ጌታ ሆይ!  ለፍርድ በመጣህ ጊዜ ነፍሴ በኃጢአት ተዳድፋና ከጸጋህ ተራቁታ እንዳትገኝ የንስሐ እድሜን ስጠኝ፡፡
ጌታ ሆይ! ጻድቅ በጭንቅ የሚድን ከሆነ የእኔ ከንቱና ኃጢአተኛ ሰው መጨረሻ ምን ይሆን? ወደ ሕይወት የምታደርሰው መንገድ ቀጭንና ጠባብ ከሆነች በቅምጥልነት የምኖረውና ለዓለማዊ ደስታ የምተጋው ሰው እጣ ፈንታዬ ምን ይሆን? ነገር ግን ጌታዬና መድኀኒቴ እንዲሁም ለእውነተኛ አምላክ እውነተኛው ልጁ የሆንክ ጌታዬ ክርስቶስ ሆይ! እንደ ፈቃድህና አንተ ለእኔ እንደምትመኛት ምኞት እንድኖር አብቃኝ፡፡ በአንተ ጸጋ ብቻ እንዳው በከንቱ በሰውነቴ ውስጥ ያደረውን የኃጢአት ፈቃድ አውጥተህ ጣልልኝ፡፡ ጌታዬ ሆይ እኔን ታድነኝ ዘንድ ፈቀድ፡፡ እጅግ ርኅሩኅና መሐሪ ለሆንከው ጌታ ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን!


4 comments:

  1. ወንድሜ ሽመልስ በመጀመርያ በእግዚያብሄር ስም እንደት ዋልክ ፡፡ ወንድሜ በጽፍችህ ውስጥ ጥቅሞች አሉ ጥቅምም ብቻ ሳይሁን ህይወት አለ ባልሳሳት ፡፡ ያላወቅነውን ማወቃችን ከሜጣሉት የቃላት ስልቶች እንዴሆም በቅዱስ ኤፍሬም ስልት የሁነውን ስርአት ማወቃችን እውነት ምንኛ መልካም ነው ወንድሜ እውነት ቃለ ህይወት ያስማልን ያገልግሉት ዘመንሀን ይባርክልህ እመብርህን ወላዴተ አምላክ ካንተ ጋራ ትሁን በርታ ....

    ReplyDelete
  2. ቃለ ህይወት ያስማልን ያገልግሉት ዘመንሀን ይባርክልህ .....

    ReplyDelete
  3. Awo Wendime Hiwet Ale altesasatikim " ወንድሜ በጽፍችህ ውስጥ ጥቅሞች አሉ ጥቅምም ብቻ ሳይሁን ህይወት አለ ባልሳሳት ፡፡ Wendime Shemelis Ebakih tsafilin teribenal tetemtenal....Ye Abatochachin tsega yederibin

    ReplyDelete
  4. አሜን ቃለ ህይወት ያስማልን ያገልግሉት ዘመንህን ይባርክልህ

    ReplyDelete