Friday, April 13, 2012

“ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ”?(በሳልማሱ ኤጲፋንዮስ)


ትርጉም በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
05/08/2004
በዛሬይቱ ቀን እንግዳ የሆነ ነገር ተከሰተ፡፡ እነሆ በዛሬይቱ ቀን ምድሪቱ በታላቅ ዝምታ ተዋጠች፡፡ ንጉሡዋ ክርስቶስ በውስጡዋ ተኝቶአልና በምድር ውስጥ ታላቅ ጸጥታ ሰፈነ፡፡ እንዲሁም በዛሬይቱ ቀን ምድር ከተፈጠረችበት ጊዜ ጀምሮ ሰምታ የማታውቀው ታላቅ የሆነ ንውጽውጽታ በውስጧ ተሰማ፡፡ ምክንያቱም በሥጋ በውስጡዋ ያደረው አምላክ በነፍሱ ወደ ሲኦል በመውረድ በሲኦል ያሉትን ነፍሳት በማስነሣት ወደ ገነት አፍልሶአቸዋልና፡፡ እግዚአብሔር በሥጋ በመሞቱ ሲኦል ታወከች፡፡ እርሱ በነፍሱ የጠፋውን የእግዚአብሔርን በግ አዳምን ሊፈልግ በዛሬይቱዋ ቀን ወደ ሲኦል ወርዶአልና፡፡
አምላክና የዳግማዊቱ ሔዋን ልጅ የሆነው ክርስቶስ አዳምንና ሔዋንን ከታላቅ ሃዘን ለማውጣት በዛሬይቱ ቀን በነፍሱ ወደ ሲኦል ወረደ፡፡ በዛሬይቱ ቀን ጠላቱን ድል የሚነሣበትን መስቀሉን ተሸከሞ ሞትን በሥጋው ተቀበለ፡፡ እርሱን የፈጠረው አምላክ በእርሱ አርአያ በሲኦል ተገኝቶአልና አዳም በፊቱ ክርስቶስ በነፍሱ ቆሞ ሲመለከተው በታላቅ ፍርሃትና መደነቅ ተሞልቶ በዙሪያው ላሉት ነፍሳት “የጌታችን ሰላም ከእናንተ ጋር ይሁን"ብሎ በታላቅ ድምፅ የምስራች አላቸው፡፡ ክርስቶስ ኢየሱስም “ከመንፈስህ ጋራ” ብሎ መለሰለት፡፡

ጌታችን እጆቹን ይዞ አዳምን ከሲኦል በማውጣት “አንተ ያንቀላፋህ ንቃ፤ የሞተክውም ተነሥ እኔ ያበራልሃል” ብሎ ከተናገረው በኋላ "ስለአንተ መዳን ስል የአንተ ልጅ የሆንኩት አምላክህ እኔ ነኝ፡፡ ላንተና ለልጆችህ ካለኝ ጥልቅ ፍቅር የተነሣ በራሴ ሥልጣን በሲኦል ያሉትን ነፍሳት ከእስራታቸው ልፈታ፤ በጨለማ ያሉትን ብርሃን ልሰጣቸው፤ ያንቀላፉትን ላስነሣ   ፈቃዴ ሆኖአልና፡፡ በገዛ ሥልጣኔ በሞት እንቅልፍ አንቀላፍታቸሁ ያላችሁትን ሁሉ ተነሡ ብዬ አዛችኋለሁ፤ እናንተም ትነሣላችሁ፡፡ እኔ እናንተን መፍጠሬ በሲኦል ትጋዙ ዘንድ አይደለም፡፡ ሙታን ሆይ ከሞት ተነሡ እኔ ለሙታን ሕይወትን የምሰጥ ሕይወት ነኝና፡፡ በእኔ መልክና ምሳሌ በእጆቼ የፈጠርኩዋችሁ ሆይ ተነሡ፡፡ ከዚህ ቦታ እንውጣ እናንተ በእኔ ናችሁ እኔም በእናንተ ነኝ፡፡ እኔና እናንተ አንድ አካል ከሆንን ፈጽሞ ለሊለየነን የሚቻለው ኀይል የለም፡፡
በእናንተ ምክንያት እኔ እግዚአብሔር ቃል የእናንተ ልጅ ሆንኩ፡፡ እኔ እግዚአብሔር የባሪያዬን አርአያ ገንዘቤ አደረግሁ፡፡ መኖሪያዬ ከሰማያት በላይ እጅግ ከፍ ከፍ ያለ ቢሆንም ስለፍቅር ራሴን ዝቅ በማድረግ ማደሪያዬ በምድሪቱና በመቃብር ውስጥ አደረግሁ፡፡ እናንተን አዎ እናንተን ያለማንም እርዳታና ድጋፍ ከሞት ባርነት ነጻ ላወጣ የሰውን አርአያ ይዜ ተገኘሁ፡፡ ከአትክልት ስፍራው ስለተባረራችሁት ስለእናንተ መዳን ይሁዳ እኔን በአትክልቱ ስፍራ መርቶ ለካህናቱ ጭፍሮች አሲያዘኝ፡፡  ወደቀደመው ክብራችሁ እመልሳችሁ ዘንድ በአትክልቱም ሥፍራ ተሰቀልኩ፡፡
 አስቀድሜ በንፋሐት እፍ ብዬ በእናንተ ውስጥ ያሳደርኩትን መንፈስ ቅዱስን እመልስላችሁ ዘንድ ፊቴ ላይ ርኩስ የሆነው ምራቃቸው እንደተተፋብኝ ልብ በሉ፡፡ እኔን ወደሚመስል የቀድሞው ውበታችሁ እመልሳችሁ ዘንድ ፊቴን በመጸፋቴ ምክንያት በፊቴ ላይ የተሰማመረውን የጣታቸው አሻራ ተመልከቱ፡፡ በእናንተ ላይ የተጫነውን የኃጢአትን ሸክም ለማስወገድ ስል በጀርባዬ የተቀበልኩትን የግርፋቱን ሰንበር ተመልከቱ፡፡ እናንተ ወደ አልተፈቀደላችሁ ዕፅ እጃችሁን በመዘርጋታችሁ ምክንያት የእኔ እጆች በዕፀ መስቀሉ ላይ መቸንከራቸውን አስተውሉ፡፡ አዳም ሆይ በገነት አንቀላፍተህ ሳለህ ሔዋን ከጎንህ አጥንት እንደተገኘች እንዲሁ እኔ በመስቀል የሞትን እንቅልፍ አንቀላፍቼ ሳለሁ በጦር በመወጋቴ ቤተክርስቲያን እንደተመሠረተች ልብ በል፡፡ የእኔ ሞት በሲኦል አንቀላፍተህ ያለኸውን አንተን አስነሣ፡፡ ጎኔን የወጋው ጦር በአንተ ላይ የተቃጣውን ሰይፍ ወደሰገባው እንዲመለስ አደረገው፡፡ አዳም ሆይ ኑ ከዚህ ቦታ እንውጣ፡፡ 
አዳም ሆይ እኔ እናንተን ጠላት ዲያብሎስ ካስወጣችሁ ከገነት የማገባችሁ አይደለም፤ ነገር ግን በሰማያት ከአባቴ ቀኝ አቆማችኋለሁ፡፡ እኔ አስቀድሜ የሕይወት ዛፍ ምሳሌ ከሆነው ፍሬ እንዳትበሉ ከለከልኳችሁ፤ አሁን ግን ሕይወት የሆንኹትን እኔን ለእናንተ ሕይወት አድጌ ሰጠሁ፡፡ አስቀድሜ ባሪያን እንደሚጠብቁ ጠባቂዎች ኪሩቤልን በእናንተ ላይ ሾምኳቸው፡፡ አሁን ግን የእኔን የእግዚአብሔርን መልክና ምሳሌ ይዛችኋልና እናንተን ያከብሯችኋል፤ በፍቅርም ያገለግሏችኋል፡፡ አሁን ከእርሱ ጋር የምትነግሡ ናችሁና ኪሩቤል የሚሸከሙት ዙፋን እናንተን ይጠባበቃል፡፡ ዙፋኑን የሚሸከሙት ኪሩቤል እጅግ ፈጣኖች ናቸው፤  እናንተንም ለማገልገል እጅግ ናፍቀዋል፡፡ ስለእናንተ የሰርግ ቤቱ አጊጦአል፡፡ ድግሱም ተሰናድቶአል፡፡ ዘለዓለማዊው ማደሪያችሁም ተዘጋጅቶአል፡፡ መልካም መዛግብቶችን የያዙት ቤቶችም ለእናንተ የተከፈቱ ሆነዋል፡፡ የእግዚአብሔር መንግሥት ዘለዓለማዊያን የምትሆኑትን ለመቀበል ትጠባበቃችኋለች፡፡ በሞቱ ሕያዋን የሆናችሁ ክርስቲያኖች  ኑ እርሱ ያለበሳችሁን  የጸጋ ልብሳችሁን በንጽሕና በመጠበቅ ወደ ጌታ ደስታ ግቡ፡፡ እናም በአንድነት “ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ? ሲኦል ሆይ ድል መንሣትህ የት አለ?”በሉት፡፡ ክርስቶስ አምላክነ መጽአ ወሐመ ወሞተ ወበሕማማቲሁ አድኀነነ፡፡

1 comment:

  1. min ale huligiza zewitir enidi sikileteu eyasebin bininor fitachin bisal ewneti kehatiyati betebekin neber

    ReplyDelete