Wednesday, August 2, 2017

የነፍስ ወግ አምስተኛ ክፍል ስለ ሥነ ተፈጥሮዬ


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
27/11/2009

እግዚአብሔር እኔ ነፍስን ልክ እንደ አዳምና ሔዋን ከእኔ ጋር አንድ አድርጎ የፈጠራትን ግዙፏን ሥጋዬን እንድረዳት አድርጎ ፈጠረኝ። ስለዚህ አምላኬ እርሷን እንደሚያውቃት መጠን አይሁን እንጂ ሥጋዬን አውቃታለሁ፡፡ ምድርን በእርሷ ላይና ውስጥ ያሉትን እንደማጥናት እንዲሁ ግዙፋን ሥጋዬን በማጥናት ሁል ጊዜ አዳዲስ የሆኑ ነገሮችን ከእርሷ እያወቅሁ እኖራለው፡፡ ለዕውቀቱ ፍጻሜ የለውም፤ ብቻ እርሷን ለማወቅ ተሰጥቶኛልና ስለእርሷ ማንነት መናገር ብዙም አይቸግረኝም፡፡ የሚደንቀኝ ግን ስለ ራሴን መርምሬ ለማወቅ አለመቻሌ ነው፡፡ ረቂቅ መንፈስ መሆኔን አውቃለሁ ነገር ግን አይቼ ዳስሼ አረጋግጬ አይደለም፡፡ መዓዛዬን፣ ቁመቴን፣ ውፍረቴን፣ ቅጥነቴን ገጽታዬን ጭምር አላውቀውም፡፡ በአጠቃላይ መንፈስ መሆኔን እንጂ ለሌላው ማንነቴ ባይተዋር ነኝ፡፡ የሚደንቀው ግን መላእክት እርሷን ማወቃቸው ነው፡፡