Thursday, May 24, 2012

ፍቅር (ፆታዊ ፍቅር)



ፍቅር ማለት ምን ማለት ነው?
በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
17/09/2004
ፍቅር ማለት እንዲህና እንዲህ ማለት ነው ብሎ ትርጉም ሰጥቶ መናገር እጅግ የሚከብድ ነገር ነው፡፡ ምክንያቱም የሰዎች ቋንቋ ስለ ፍቅር ትርጉም ለመስጠት አቅም የለውምና ነው፡፡ እንዲህ ሲባል የሰዎች አእምሮ አይረዳውም ማለት ግን አይደለም፡፡ ከመገለጫዎቹ ተነሥተን ስለፍቅር ትንታኔ መስጠት ይቻለናል፡፡ ይህ ማለት ግን ስለፍቅር የተሟላ ትርጉም አግኝተንለታል አያሰኘንም፡፡ የፍቅር ትርጉም እንደውቅያኖስ እጅግ ጥልቅና ሰፊ ነው፡፡ ጎርጎርዮስ ዘፓለማስ የሚባሉ አባት የእግዚአብሔር ባሕርያትን አይመረመሬነት ለማስረዳት ሲሉ ባሕርይውን በጨለማ ይመስለዋል፡፡ የእግዚአብሔር ባሕርይን መርምሮ ሊደርስበት የሚችል ከፍጡር ወገን የለም፡፡ ከእግዚአብሔር ባሕርያትም አንዱ ደግሞ ፍቅር ነው፡፡ “እግዚአብሔር ፍቅር ነው” እንዲል፡፡ (1ዮሐ 4.9) ፆታዊውም ፍቅር በእግዚአብሔር ባሕርይ ውስጥ ላለው ፍቅር ምሳሌ ነው፡፡


እግዚአብሔር ፍቅር ነው ስንል በእግዚአብሔር ሦስትነት ውስጥ ያለውን ፍጹም አንድነትና ሕብረትን መናገራችን ነው፡፡ በሥላሴ ባሕርይ ውስጥ ያለው ፍቅር ከሌላ የተገኘ ሳይሆን የራሱ የባሕርይ ገንዘቡ ነው፡፡ ስለዚህም ጌታችን ይህን ሲያስረዳ “አባት ሆይ ዓለም ሳይፈጠር በፊት ስለወደድኸኝ የሰጠኸኝንም ክብሬን እንዲያዩ እኔ ባለሁበት የሰጠኸኝ እነርሱ ደግሞ ከእኔ ጋር ይሆኑ ዘንድ እወዳለሁ” (ዮሐ 17.24) በሌላም ቦታ “አብ ወልድን ይወደዋልና የሚያደርገውንም ያሳየዋል”፡፡(ዮሐ 5.20) ብሏል፡፡
ነገር ግን የፍቅርን ምንነት ለመረዳት በምሳሌ ማሳየት ይቻላል፡፡ ፍቅር በነፍስ እንመስላታለን፡፡ ነፍስ ለሥጋችን ሕይወት እንደሆነች እንዲሁም ፍቅር ለበጎ ሥራዎቻችን ሁሉ ሕያውነትን የምትሰጥ  ናት፡፡ ያለ ፍቅር የሚከናወኑ ማናቸውም በጎ ምግባራት ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስረዳው የሞቱ ናቸው፡፡ ከእግዚአብሔር ዘንድ አንዳች ዋጋን አያሰጡንም፡፡ ፍቅር በውስጥዋ ሁሉንም ሥነ-ምግባራት አካታ ይዛለች፡፡ ሐዋርያው ፍቅርን የሕግ ፍጻሜ እንደሆነ ገልጾልናል፡፡ (ሮሜ. 13.10) ጌታም ሕግጋትን ሁሉ እግዚአብሔርን በመውደድና ባልንጀራን በመውደድ የታሰሩ መሆናቸውን ያስረዳናል(ማር 12.29)፡፡ 
ሰው በእግዚአብሔር አርዓያና አምሳል የተፈጠረ ፍጥረት ነው ሲባል ምን ማለት ነው?
አርዓያና አምሳል የሚሉት ቃላት ያለምክንያት የተነገሩ ቃላት አይደሉም፣ የየራሳቸው የጠለቀ ትርጉም አላቸው፡፡ ትርጉማቸውም፣ እንደሚከተለው ነው፡-
እግዚአብሔር እርሱን ይመስሉ ዘንድ ከፈጠራቸው ፍጥረታት ውስጥ ያኖረው አቅም አርዓያ (IMAGE) ይባላል፡፡
አምሳል የሚለው ደግሞ እርሱን እንድንመስል በውስጣችን ያኖረውን አቅም (Potential) ተጠቅመን እርሱን የምንመስልበት ነው፡፡ ይህ በምሳሌ ሲብራራ፡- አርዓያ (IMAGE) የምንለው በስንዴ ቅንጣት ውስጥ ያለው ተክል የመሆን አቅምን ሲሆን፤ አምሳል የምንለው ስንዴው በውስጡ ያለውን አቅም ተጠቅሞ ተክል የሚሆንበት ነው፡፡
ሰው በተፈጥሮ ውስጥ እግዚአብሔርን የሚመስልበት ባሕርያትን ገንዘቡ ያደረገ ፍጥረት ነው፡፡ ሰው እግዚአብሔርን የሚመስልበት አራት ባሕርያት አሉት፡፡ እነርሱም፡-

  1. ነፃነት (FREEDOM)
  2. ገዢነት (DOMINION)
  3. ሥሉስትነት (COMMUNION)
  4. ጥበብ (WISDOM) ናቸው፡፡

1.     ነፃነት
ሰው የፈቀደውን መርጦ ይፈጽም ዘንድ ነፃነት እንዲኖረው ሆኖ የተፈጠረ ፍጥረት ነው፡፡ ነፃነቱ ግን ተፈጥሮአዊ ሥርዓትን የማይጥስ ነፃነት ነው፡፡ ወይም ነፃነቱ በተፈጥሮአዊ ሥርዓት የተወሰነ ነው፡፡ ምክንያቱም ፍጡር እንጂ ፈጣሪ አይደለምና፡፡ በእግዚአብሔር ባሕርይ ውስጥ ያለው ነፃነት ግን ወሰን የለውም፤ ሁሉንም ያለማንም ከልካይነት ያከናውናል፡፡

2.    ጥበብ
ጥበብ (አእምሮ ጠባይ) ሰው የሚጠቅመውንና የሚጎዳውን ለይቶ ያውቅበት ዘንድ ከአምላኩ የተሰጠው አምላኩን የሚመስልበት ልዩ ሀብቱ ነው፡፡

3.    ገዢነት
እግዚአብሔር ሰውን በምድር ሁሉ ላይ እንዲሰለጥንባታ ገዢነትን ሰጥቶታል (ዘፍ 1.28)፡፡
4.    ሥሉስትነት
ሰው ሥሉስትነት የሚታይበት ነው፡፡ ሠሉስትነት ደግሞ በሥላሴ ውስጥ ያለ አንዱ ባሕርይ ነው፡፡ በሥላሴ ሦስትነት ውስጥ ፍጹም የሆነ አንድነት አለ፡፡ አንድነቱም በባሕርይው ውስጥ ባለው ፍቅር ነው፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥረው በሦስትነቱ ውስጥ ያለው ሕብረትና አንድነት በሰውም ዘንድ እንዲኖር አድርጎ ነው፡፡ የአንድነቱም ማሰሪያ ፍቅር እንዲሆን አድርጎታል ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው በሥላሴ ውስጥ ያለው አንድነት በሰዎችም ዘንድ አንዲኖር በማቀድ እግዚአብሔር በሰዎች ተፈጥሮ ውስጥ በተለያየ መንገድ ፍቅርን ተክሏታል ይለናል፡፡
እንደ ቅዱሱ ገለጻ እግዚአብሔር ስለ ፍቅር ሲል አንድ አዳምን አስቀድሞ ፈጠረው ምክንያቱም በእርሱ ራስነት አካላትን ሁሉ ለመጠቅለል፡፡ ይህ ቅዱስ ጥያቄ ይጠይቃል ስለምን እግዚአብሔር የሰውን ዘር ሁሉ ልክ እንደ አዳም ከምድር አፈር አላበጃቸውም? ስለምንስ እንደ አዳም የ30 ዓመት ጎልማሳ አድርጎ አልፈጠራቸውም? ስለምንስ ከእርሱ የሚገኙ ልጆችን በየጥቂቱ እንዲያድጉ አደረጋቸው? ለእነዚህ ጥያቄዎች ሁሉ ራሱ መልስ ይሰጥባቸዋል፡፡ እንዲህም ይላል፡- ስለፍቅር ሲል እንዲህ አደረገ፡፡ በመውለድና በመወለድ ሂደት ውስጥ በሚፈጠረው ጥብቅ የሆነ ቁርኝት ፍቅር ሥር ሰዳ ትመሠረታለች፡፡ ይህችም ፍቅር ሰዎች ሁሉ ፍጹም ወደሆነ አንድነት ታመጣቸዋለች፡፡
ይህ ቅዱስ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡ ስለምንስ እግዚአብሔር ሔዋንን ሲፈጥራት ልክ እንደ አዳም ከምድር አፈር አልፈጠራትም? ነገር ግን ከአካሉ አስገኛት? ብሎ ይጠይቃል፡፡ ይህም ስለ ፍቅር ብሎ ይህ አደረገ ይለናል፡፡
 በአዳም ተፈጥሮ ውስጥም ፍቅር መተከሏን የምናስተውለው እግዚአብሔር ሔዋንን ከአዳም የጎን አጥንት ከፈጠራት በኋላ “ይህች አጥንት ከአጥንቴ ናት፤ ሥጋዋም ከሥጋዬ ናት” በማለት አዳም እርሷን ለሚስትነት መሻቱን በገለጸበት ኃይለ ቃሉ ነው፡፡ ይህ ቅዱስ ይህን ሲያስረዳ “For there is a certain love (sexual love) deeply seated in our nature, which imperceptibly to ourselves knits together this bodies of ours.” “አንድ በሰውነታችን ጥልቅ ውስጥ የታተመ እኛ የማንረዳው ነገር ግን ከእኛ ተፈጥሮ ጋር በጥብቅ የተቆራኘ ፍቅር አለ” ብሎታል፡፡ በሌላም ቦታ ስለዚህ ፍቅር ሲናገር “በእርግጥ በጣም በእርግጠኝነት ይህ የፍቅር ዓይነት አፍቃሪውን ከመግዛትም ባለፈ ገዢነቱ እጅግ ጽኑ ነው፡፡ ሌሎች የፍቅር ዓይነቶች በእርግጥ ጽኑዋን ቢሆኑም ይህ ፍቅር ግን ጽኑ ብቻ ሳይሆን ከተፈጥሮአችን ጋር በጥብቅ የተዋሐደና ፈጽሞ ከሕሊና የማይወጣ ጭምር ነው” ብሏል፡፡
 ከዚህ ተነሥተን የፆታዊ ፍቅርን በተፈጥሮአችን ውስጥ የተከለው እግዚአብሔር እንደሆነ እንረዳለን፡፡ ስለዚህም ፆታዊ ፍቅር ቅዱስ እና እግዚአብሔር የሰውን ዘር አንድ ቤተሰብ ለማድረግ የሠራው መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ እግዚብሔርም ይህን ባወቀ “ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል ከሚስቱ ጋር ይጣበቃል” አለ፡፡ ይህም የፆታዊ ፍቅር ውጤት ነው፡፡ከዚህ የምንረዳው እግዚአብሔር በእርሱ ባሕርይ ውስጥ ያለው ሥሉስትነት በሰዎች መካከልም መፍቀዱን ነው፡፡ ገና ከመጀመሪያው እግዚአብሔር ፍቅርን ጉልበተኛ አድርጓታል፡፡ (Yea, and for this cause he made it also stronger, that it might bow the superior parties to the absolute sway of this passion and might subjugate it to the weaker.) “አዎን! እግዚአብሔር ለዚህ ኣላማው ፍቅርን ብርቱ አደረጋት በዚህም ኃያላን ወገኖች ለዚህ እጅግ ጽኑ ለሆነ ፍቅር ወድቀውና ተንበርክከው ለደካሞች ይገዛሉ”፡፡ (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ) 
ማንኛውም ሰው ከጉልበተኛው ፍቅር ክንድ ሊያመልጥ አይቻለውም፡፡ እግዚአብሔር ስለ ፍቅር ማበብና መስፋፋት እንዲሁም የሰው ዘርን ሁሉ አንድ ቤተሰብ ለማድረግ ሲል የዘመድ ግቢን ከለከለ፡፡ (ዘሌዋ. 18.6) ገና ከሥነ ፍጥረት ጀምሮ አዳምንና ሔዋንን፣ ከውድቀትም በኋላ የሰው ልጆችን በአንድ ሥፍራ እንዲሰፍሩ ማድረጉም ስለፍቅር ነው፡፡ አንድ ቋንቋም እንዲኖራቸው ማድረጉም ስለፍቅር ነው፡፡ ነገር ግን የሰዎች ኃጢአት ፍቅርን የሚያጠፋ ሆኖ ሲያገኘው እንዲበታተኑ አደረጋቸው፤ ቋንቋቸውንም ደባለቀባቸው፡፡ አስቀድሞ ግን እንዲህ ይሆን ዘንድ የእግዚአብሔር ፈቃድ አልነበረም የሰዎች የአመፃ ውጤት እንጂ፡፡
በተጨማሪም እግዚአብሔር አንድን ሰው ከሌላው የሚሻው ነገር እንዲኖረው አድርጎ መፍጠሩ በፍላጎታቸው ተስበው አንዱ ከአንዱ ጋር በመተሳሰብና በመፈቃቀድ እርስ በርሳቸው ግንኙነታቸውን በማጥበቅ በፍቅር ይመላለሱ ዘንድ ነው፡፡ እንደ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ማብራሪያ ከተሞች መቆርቆራቸው የሀብት መበላለጥ በሰዎች መካከል መኖር ስለፍቅር ሲባል ነው ይለናል፡፡
በእግዚአብሔር ዘንድ ከፍቅር የሚቀድም አንድም ነገር የለም በተፈጥሯችንም ውስጥና በዚህም ዓለም ውስጥ የሠራቸው ሥርዓቶች ሁሉ የሰውን ልጅ ወደ ፍቅር የሚያመጡ ናቸው፡፡ የእግዚብሔር ቀንደኛ ጠላት ማነው ቢባል ፍቅርን የማይሻ ሰው ነው፡፡ ፍቅርን የሚቃወም እግዚአብሔርን ብቻ ሳይሆን ፍጥረታትንም እራሱንም ይቃወማል፡፡
“ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል በሚስቱም ይጣበቃል” የሚለው ኃይለ ቃል የጾታዊ ፍቅርን ብርቱነት የሚገልጽ ኃይለ ቃል ነው፡፡ ከዚህ ዓይነት ፍቅር ብዙ ፍቅሮች ፈለቁ የአባት፣ የእናት፣ የወንድም፣ የእኅት እና የዘመድ ፍቅር ፈለቁ፡፡ እግዚአብሔር ፆታዊ ፍቅርን የፍቅሮች ሁለ ዘውድ አድርጎታል፡፡ ከሌሎችም የፍቅር ዓይነቶች ይልቅ ለፆታዊ ፍቅር ትልቅ ቦታን ይሰጣል፡፡ ምክንያቱም በዚህ ፍቅር የሰው ዘር አንድ ለማድረግ ፈቃዱ ነውና፡፡ የሰው ዘር ከአንድ ተፈጥሮ ወደአንድ ለመሰብሰብ ከፆታዊ ፍቅር የበለጠ ታላቅ ሚና የሚጫወት የፍቅር ዓይነት የለም፡፡
በምድር ላይ ከፆታዊ ፍቅር የበለጠ ፍቅር ስለሌለ እግዚአብሔር ለሕዝቡ ያለውን ፍቅር ለማስረዳት በፆታዊ ፍቅር መስሎ ያስተምር ነበር፡፡ አስተምሮአልም ሆሴ 3.1-5፡፡ “ሚስቶች ሆይ ለጌታ እንደምትገዙ ለባሎቻችሁ ተገዙ ክርስቶስ ደግሞ የቤተክርስቲያን ራስ እንደሆነ እርሱም አካሉን የሚያድን እንደሆነ ባል የሚስት ራስ ነው … ባሎች ሆይ ክርስቶስ ደግሞ ቤተክርስቲያንን እንደወደደ ሚስቶቻችሁን ውደዱ” ኤፌ 5.21-35 እንዲል፡፡
ሌሎች የፍቅር ትርጉሞች
“ፍቅር ማለት ራስን ስለሌላ አሳልፎ መስጠት ማለት ነው”፡፡ ወዳጄ የሥጋዬ ክፋይ ነው የሚል ሰው እርሱ እንዲህ በማለቱ መልካም ተናገረ /ቅዱስ ኦገስቲን/ well did one say to his friend thou half of my soul. “Love means finding one’s self in another” ፍቅር ማለት ራስን በሌላ ሰው ማንነት ውስጥ ማግኘት ማለት ነው፡፡
ፍቅር ከእምነት ከተስፋ በምን በለጠ?
እምነት ተስፋ መቀበል ናቸው፡፡ ፍቅር ግን መስጠት ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከመቀበል መስጠት እንደሚበልጥ “ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብጹእ ነው” ብሏል፡፡ እምነትና በጎ ምግባራት ዋጋ ሊያሰጡ የሚችሉት በፍቅር የሆኑ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ “በክርስቶስ ኢየሱስ ሆኖ በፍቅር የሚሠራ እምነት እንጂ መገረዝ ቢሆን አለመገረዝ አይጠቅምም” እንዲል (ገላ 5.6)፡፡
ፆታዊ ፍቅር መች ይጀምራል?
ፆታዊ ፍቅር በራስ ግፊት ወይም ፈቃድ የሚመጣ ፍቅር አይደለም፡፡ በራሳችን ፈቃድ ለማምጣት የፈለግን እንደሆነ ፍቅራችን የተሟላ ሊሆን አይችልም፡፡ ፍቅር የእግዚብሔር ስጦታ ነው፡፡ “ከላይ ከእግዚአብሔር በሚገኘው ፍቅር ካልሆነ በቀር ሰዎችን ወደ ፍጹም ስምምነት ማምጣት እጅግ አስቸጋሪና የማይሞከር ነው፡፡ እንዲል (ቅ/ዮሐንስ አፈወርቅ) ይህ ነፍስንም ሥጋንም ሰቅዞ የሚይዝ ፍቅር በእርጋታና በማስተዋል ላይ የተመሠረተ ይሆንና ተጀምሮ የሚፈጸም እንጂ ወዲያው የሚፈርስ እንዳይሆን ለወንድ በአብዛኛው ከ25 እድሜው በላይ ለሴት ደግሞ ከ18 ዓመት ዕድሜ በላይ በሆኑ ሰዓት ይህን ፍቅር በተለያየ ጊዜያት እግዚአብሔር ሊያሳድርባቸው ይችላል፡፡ ቢሆንም ፆታዊ ፍቅርና የተቃራኒ የፆታ ግፊት የሚከሰቱባቸው ወቅቶች በአብዛኛው በዚህ በወጣትነው እድሜ ክልል ውስጥ ስለሆኑ ሁለቱ ክስተቶች ወጣቱን ሲያምታቱ ይታያል፡፡ በተለይ ከወንዱ ፆታ ላይ ጎልቶ ይታያል፡፡ በፆታዊ ፍቅርና በተቃራኒ ፆታ ግፊት መካከል ሰፊ ልዩነት አለ፡፡
ፆታዊ ፍቅር
v በፆታዊ ፍቅር ውስጥ ያለ ሰው ራሱን ላፈቀረው ሰው ያስገዛል፣ ያሳድራልም
v በፆታዊ ፍቅር ላፈቀረው ሰው ፈቃድና ጥቅም ያድራል
v የግል እርካታውን አይሻም ላፈቀረው ሰው በጎ ነገሮች አድርጎ አይጠግብም
v ነፍሱን ስላፈቀረው አሳልፎ ይሰጣል፡፡
በተቃራኒ ፆታ ግፊት የሚመላለስ ሰው
v  ለራሱ እርካታ ብቻ ይተጋል
v ርኅራሄ አክብሮት ለፆታዊ ግንኙነት ላሰበው አካል የለውም፤ ጨካኝ ነው፡፡
v በአንድ ረግቶ አይኖርም ካገኘው ጋር ይዳራል
v አስገድዶ ለመድፈርም አጋጣሚዎች ከተመቻቹለት አይመለስም
v በአጠቃላይ እውር ድንበሩን የሚጓዝ ሰው ነው፡፡ ነገር ግን የተቃራኒ ፆታ ግፊት በራሱ ጤናማ ነው፡፡ ነገር ግን ፆታዊ ግፊት በማስተዋልና በፍቅር በእምነት ሊመራ ይገባዋል፡፡ ያለበለዚያ ሊወጡት የማይችሉትን ጸጸትና ቅጣት ያመጣል፡፡
 ፆታዊ ፍቅር በራሱ ሙሉ ነው ወይ?
ፆታዊ ፍቅር በራሱ ሙሉ ነው ብሎ ለመናገር ከውድቀት በፊት ወደነበረው ተፈጥሮአችን ልንመለስ ይጠበቅብናል፡፡ አዎን! በዛን ጊዜ /ከውድቀት በፊት ፆታዊ ፍቅር በራሱ አንዳቸው ጉድለት የሌለበት ሙሉ ነበር፡፡ ምክንያቱም በዛን ጊዜ ፆታዊ ፍቅር እግዚአብሔርን በማወቅና በእርሱ ፈቃድ ላይ የተመሠረተ ነበርና ነው፡፡ ፆታዊ ፍቅር እግዚብሔርን ማወቅና መፍራት የሚቀድመው ከሆነ እጅግ ጣፋጭና የሰመረ ፍቅር ሊሆን ይችላል፡፡ ጠቢቡም “አንድ ብቻ ከመሆን ሁለት መሆን ይሻላልና ቢወድቁ አንዱ ሁለተኛውን ያነሳዋል” ካለ በኋላ “አንዱም አንዱን ቢያሸንፍ ሁለቱ በፊቱ ይቆማሉ በሦስትም የተገመደ ገመድ አይበጠስም” መክ 4.8-12 ማለቱ ለዚህ ነው፡፡
ትዳር ማለት መስቀልን መሸከም ማለት ነው፡፡ መስቀልን መሸከም ደግሞ ያለፍቅር አይሆንም፡፡ በትዳር ውስጥ የሚመጡ ፈተናዎችን በጽናት ማሳለፍ የሚቻለው በፍቅር ነው፡፡ “The mother of long suffering is love” የትዕግሥት እናቱ ፍቅር ናት” ዮሐንስ አፈወርቅ” እንዲያም ሆኖ ግን በተደጋጋሚ በሚገጥሙ መከራዎች ሰይጣን አላዋቂነትታችንን ተጠቅሞ በመካከላችን በሚዘራው ተንኮል የተነሣ ምንም ብንዋደድ ትዳራችንን ሊያፈርሰው ይችላል፡፡ ይህንን ለማቆም ታዲያ እግዚአብሔርን ማወቅና ለፍቃዱ መገዛት ቅድሚያ ልንሰጠው ይገባል፡፡ ይህም አማኞችን የሰይጣንን ተንኮል አጥርተው እንዲመለከቱ ስለሚያደርጋቸው በቀላሉ የክፋት መረቡን መበጣጠስ ያስችላቸዋል፡፡ ፍቅር እግዚአብሔርን ከማወቅ ጋር ከሆነ መከራም ቢመጣብን በእግዚአብሔር ተደግፈን እናልፈዋለን፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔርን ማወቅ ያላስቀደምን ከሆነ ዓለም በፍቅራችን መሐል ጣልቃ ገብታ በድህነት፣ በዘረኝነት፣ በክብር፣ በገንዘብ ወዘተ ልትለያየን ትችላለች፡፡ በእግዚአብሔር የተደገፈ ግን እነዚህን ነገሮች ከንቱ ያደርጋቸዋል፡፡
ክርስቶስ ቤተክርስቲያንን እንደወደዳት እንዲሁም ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ፍቅሩን ያለስስት ላፈቀረው አካል የሚለግስ ሰው እርሱ ብጹእ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም “ብታገቡ ግን ኃጢአት አትሠሩም ነገር ግን እንዲህ በሚያደርጉ በሥጋቸው ላይ መከራ ይሆንባቸዋል” 1ቆሮ 7.28 ማለቱ ስለዚህ ነው፡፡
ነገር ግን እግዚአብሔርን በማወቅና ፈቃዱንም በመፈጸም ላይ የተመሰረተ ጾታዊ ፍቅር ቅ/ዮሐንስ አፈወርቅ እንደተናገረው እጅግ የከበረ ነው፡፡ ምሳሌ የሚሆኑን ቅዱሳንን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ለምሳሌ አብርሃምና ሣራ፣ ይስሐቅና ርብቃ፣ አቂላና ጵርስቅላ ሐዋ 18.2-24፡፡
“ከምንጭ ውሃ እንዲፈልቅ መልካም በረከቶች ሁሉ እግዚአብሔርን ከመፍራት ይፈልቃሉ፡፡ እናም ቤቱ የእልፍ እልፍ በሆኑ በረከቶች ይሞላል የማያልፈውን በሻትን ጊዜ የሚያልፉትን ምድራዊ በረከቶችን ጨምረን እናገኛለን … እንዲህ ከመሰሉ ቤተሰቦች የሚገኙ ልጆች ምን ሊመስሉ እንደሚችሉ እንገምታለን … ፍቅርን የተማሩ አንድ ዓይነት ቋንቋ ይናገራሉ ፍቅርን አስተምረዋቸዋልና የእነርሱን ፈለግ ይከተላሉ፡፡ (ቅ/ዮሐንስ አፈወርቅ)

ለፍቅር መስፈርት አለው ወይ?
ፆታዊ ፍቅር የሚከሰተው እድሜአችን ለአቅመ አዳምና ሔዋን ከደረሰ በኋላ ነው፡፡ ነገር ግን ፆታዊ ፍቅር ለተፈጥሮአዊ ሕግና ለእግዚአብሔር ፈቃድ ይገዛል፡፡ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ ልብ ሊለው የሚገባ ጉዳይ ቢኖር ሰዋዊውን ባሕርይውን ነው፡፡ ቀደም ብለን እንደተመለከትነው ሰው አምላኩን የሚመስለው አንድም በተሰጠው ነፃነት ነው፡፡ እግዚአብሔር በሰዎች ነፃነት ውስጥ ጣልቃ አይገባም፡፡ እንግዲህ እኛ በፈቃደኝነት ነፃነታችንን ለእርሱ እስካላስረከብነው በቀር እግዚአብሔር በሰዎች ነጻነት ውስጥ ጣልቃ የሚገባ ካልሆነ ይልቁኑ ሰዎች በሰዎች ነፃነት ውስጥ ጣልቃ የመግባት መብት እንዴት ሊኖራቸው ይችላል? አዎን የአንድን ሰው ተፈጥሮአዊ መብቱን በግዴታ የጣስን እንደሆነ በደላችን በእግዚአብሔር ላይ ነው፡፡ ስለዚህ በፍቅር አሳበን የተፈቃሪን መብት መጣስ ከአንድ ክርስቲያን የሚጠበቅ አይደለም፡፡ ማንኛውም ድርጊቶቻችን ከተፈጥሮአዊ ሥርዓቶቻችን ጋር የሚስማሙ ሊሆኑ ይገባቸዋል፡፡ አባትም፣ እናትም፣ ጓደኛም፣ ሌላውም ወገን ለወዳጁ የሚበጀውን ከመምከር፣ የሚሻለውን ከመጠቆም፣ በቀር ነፃነቱን የመንጠቅ መብት የለውም፡፡
ፍቅር በተፈቃሪዎች ነጻ ምርጫ ላይ የሚመሠረት ነው፡፡ አንዱ ወገን ያላፈቀረ ከሆነ ፍቅርን ለማግኘት ሲባል መማለጃ መስጠት፣ ማስፈራራት፣ ማስገደድ፣ ሌሎችን ነገሮች ማድረግ በእግዚአብሔር ላይ እንደመዝመት ይቆጠራል፡፡ ጠለፋ፣ ያለ እድሜ ጋብቻ፣ የቤተሰብ ጋብቻ፣ በቤተሰብ በኩል የሚመጣ ጋብቻ ባጠቃላይ ኢክርስቲናዊ ተግባራት ናቸው፡፡
አንዳንድ ጠቃሚ አባባሎች
v For the woman has beauty, and the man desire, shows nothing else that for the sake of love it hath been made so. ለሴት ልጅ ውበትን ለወንድ ልጅ መሻትን መሥራቱ ስለፍቅር እንጂ ሌላ ምንም ምክንያት የለውም፡፡ 
v Do not therefore, because thy wife is subject to thee, act the despot, nor because thy husband loves thee, be thou puffed up. ሚስትህ ስለታዘዘችህ አታቃላት አንቺም ባልሽ ስላፈቀረሽ አትታበይ፡፡
v For this cause has He subjected her to thee, that she may be loved the more. For this cause He hath made thou to be loved, wife’s that you may easily bear thy subjection. በዚህ ምክንያት እርሱ (እግዚአብሔር) ሚስትህ ለአንተ እንድትታዘዝ ማድረጉ ይበልጥ ታፈቅራት ዘንድ ነው፡፡ አንተም እርሱዋን ታፈቅራት ዘንድ ሥርዐት አድርጎ መሥራቱ ሚስትህ ለአንተ መገዛቱዋ እንዳይከብዳት ነው፡፡
v Fear not in being a subject for the subjection to one that love thee hath not hard ship. ለሚያፈቅርሽ ሰው መታዘዝ የሚከብድ አይደለምና መታዘዝን ለአንቺ እንደ ሕግ መስጠቱ አያስፈራሽ፡፡  
v Fear not in loving for you has her yielding. In no other way then could a bond have been.ለአንተ ማፍቀርን ለእርሱዋ መታዘዝን መሠራቱ አያስፈራህ ከእነዚህ ውጭ አንድነትን የሚያመጡ ነገሮች የሉምና፡፡ 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

11 comments:

  1. ፆታዊ ፍቅር በራሱ ሙሉ ነው ብሎ ለመናገር ከውድቀት በፊት ወደነበረው ተፈጥሮአችን ልንመለስ ይጠበቅብናል፡፡ አዎን! በዛን ጊዜ /ከውድቀት በፊት ፆታዊ ፍቅር በራሱ አንዳቸው ጉድለት የሌለበት ሙሉ ነበር፡፡ ምክንያቱም በዛን ጊዜ ፆታዊ ፍቅር እግዚአብሔርን በማወቅና በእርሱ ፈቃድ ላይ የተመሠረተ ነበርና ነው፡፡ ፆታዊ ፍቅር እግዚብሔርን ማወቅና መፍራት የሚቀድመው ከሆነ እጅግ ጣፋጭና የሰመረ ፍቅር ሊሆን ይችላል፡፡ ጠቢቡም “አንድ ብቻ ከመሆን ሁለት መሆን ይሻላልና ቢወድቁ አንዱ ሁለተኛውን ያነሳዋል” ካለ በኋላ “አንዱም አንዱን ቢያሸንፍ ሁለቱ በፊቱ ይቆማሉ በሦስትም የተገመደ ገመድ አይበጠስም” መክ 4.8-12 ማለቱ ለዚህ ነው፡፡

    ReplyDelete
  2. Kale hiwot yasemaln tsegaw yabzalh amleke kudusan anten emimesel twled endtteka Egziabhir yibarkh edmina tina yisth wendmachi...

    ReplyDelete
  3. Thank you.continue....go forward. ቃለህይወት ያሰማልን

    ReplyDelete
  4. ፍቅር ምንድን ነው Hi. Sir.. You really are a genius, I feel blessed to be a regular reader of such a blog Thanks so much.. -online kaj💕💋 font copy and paste what is love?

    ReplyDelete
  5. መምህር ቃለህይወት ያሰማልን የውስጤን ጥያቄ ነው የመለሱልኝ

    ReplyDelete
  6. በፍቅር መካከል ሊኖር ስለሚገባው ጤናማ ግንኙነት ትንሽ ምክር አዘል ሃሳብ ቢስጥ መልካም ነው

    ReplyDelete