Sunday, April 8, 2012

ሆሣዕና በሐዲስ ኪዳን



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
30/07/2004
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሕዝብና የአሕዛብ አባት ስለሆነው አብርሃም “አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤትን አደረገ አየም ደስም አለው”(ዮሐ.8፡56) ብሎ ተናገረለት፡፡ አብርሃም የጌታን የማዳን ቀን በእምነት የተረዳው እግዚአብሔር ዘርህን እንደ ሰማይ ከዋክብት አበዛልሃለሁ ብሎ በባረከው ጊዜ ነበር፡፡ ልጆቹ ቁጥራቸው ከሰማያውያን መላእክት ቁጥር እንደሚሆኑ ያለዘርዐ ብእሲ ከመንፈስና ከእሳት ተወልደው እሳታውያንና መንፈሳውያን መላእክትን እንዲመስሉ በመረዳቱ አብርሃም አባታችን ሐሤትን አደረገ፡፡ ስለዚህም አብርሃም “የሰሌን ጫፍ ለጋውን ያማረ የእንጨቱንም ፍሬ ይዞ በየቀኑ ዘንባባውን ይዞ ሰባት ቀን የመሠዊያውን ዙሪያ በመዞር አምላኩን አመሰገነ”(ኩፋሌ.13፡21-23) በዚህም “አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤትን አደረገ” የሚለው ቃል ተፈጸመ፡፡ ይህን ይዘው እስራኤላውያን በየዓመቱ የዳስ በዓልን የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ በቤተ መቅደስ ዙሪያ ሆነው በዓልን ያደርጉ ነበር፡፡(ዘዳ.16፡13) ነገር ግን እግዚአብሔር አምላክ ለወዳጁ ለአብርሃም እርሱንና በእምነት እርሱን የመሰሉትን እንዴት እንደሚያድናቸው ሊያሳየውና እግዚአብሔርን የሚፈሩ ዋጋቸው ምን እንደሆነ ሊያስተምርበት አባታችን አብርሃምን ልጁ ይስሐቅን እንዲሠዋለት አዘዘው፡፡




አብርሃም አባታችንም በፍጹም መታዘዝ አንድያ ልጁን ሊሠዋ በአህያው ላይ ተቀምጦ፣ ሎሌዎቹን ለመሥዋዕት ማቅረቢያ የሚሆነውን እንጨቱን አስይዞ እግዚአብሔር ወዳሳየው ወደ ሞሪያ ተራራ አመራ፡፡(ዘፍ.22፡2) ወደ ሞሪያ ተራራ እንደቀረበ ልጁን ይስሐቅን እንጨቱን አስይዞ ሎሌዎቹን ደግሞ አህያውን እንዲጠብቁ በዚያው ትቶአቸው ቢላዋውንና እሳቱን ራሱ  በመያዝ ከልጁ ጋር በእግራቸው መሥዋዕቱ ወደሚቀርብበት ሥፍራ ደረሱ፡፡ አብርሃም እንጨቱን ረበረበ፤ ልጁን ይስሐቅን አጋድሞ ሊሠዋው ቢላዋውን እንዳነሣ የእግዚአብሔር መልአክ “አብርሃም አብርሃም ብሎ ተጣራ፤ አብርሃምም እነሆኝ ብሎ መለሰ፡፡ “በብላቴናው ላይ እጅህን አትዘርጋ አንዳችም አታድርግበት አንድ ልጅህን ለእኔ አልከለከልህምና እግዚአብሔርን የምትፈራ እንደሆነክ አሁን አውቂያለሁ”...እግዚአብሔር በራሴ ማልሁ ይላል ይህን አድርገሃልና አንድ ልጅህንም አልከለከልህምና በእውነት በረከትን እባርክሃለሁ ዘርህንም እንደ ሰማይ ከዋክብትና በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ አበዛዋለሁ" ብሎ ባረከው፡፡ እግዚአብሔርም ለአብርሃም በዕፀ ሳቤቅ ቀንዱ የተያዘ በግ አሳየው እርሱን መሥዋዕት አድርጎ ለእግዚአብሔር አቀረበ፡፡”(ዘፍ.22፡9-14)
በዚህ በሞሪያ ተራራ ላይ ነቢዩ ዳዊት ለአምላኩ መሥዋዐትን አቅርቦበት ነበር፡፡በጊዜውም የኦርና አውድማ ተብሎ ይታወቅ ነበር(2ሳሙ.24፡18-25)”ንጉሥ ሰሎሞን እግዚአብሔር ለአባቱ ለዳዊት በተገለጠበት በሞሪያ ተራራ ዳዊት ባዘጋጀው ስፍራ በኢያቡሳዊው በኦርና አውድማ በኢየሩሳሌም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ሠራ”(2ዜና.3፡1)
በዚህ ምንን እንረዳለን ወገኖቼ፡- አብርሃም የዘንባባን ዝንጣፊ ይዞ ሲዞረው የነበረው መሠዊያ ያለበት ሥፍራ፣ ልጁን ይስሐቅን ሊሠዋ ያቀረበበት ሥፍራ፤ ዳዊት እግዚአብሔር ካመጣበት ቸነፈር ይድን ዘንድ መሥዋዕት ያቀረበበት ሥፍራ እንዲሁም ንጉሥ ሰሎሞን ቤተመቅደሱን የሠራበት ሥፍራ የሞሪያ ተራራ መሆኑን ነው፡፡ በዚህም እግዚአብሔር ወልድ ለአብርሃም አባታችን በልጁ በይስሐቅ እና በዕፀ ሳቤቅ ቀንዱ በተያዘው በግ ምሳሌ ታየው፡፡ ስለዚህም “አየም ደስም አለው” የሚለው ቃል ተፈጸመ፡፡ ጌታችንም “አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤትን አደረገ አየም ደስም አለው”(ዮሐ.8፡56)ሲለን የእነዚህ ድምር ውጤት መሆኑን እንረዳለን፡፡
ነቢዩ ዳዊትም የአብርሃም ደስታ የሆነ ንጉሥ ክርስቶስ ከእርሱ ወገን ተወልዶ በሥጋ ለዓለም እንዲገለጥና መድኀኒት ሆኖ በኃጢአት ምክንያት ሰዎችን ከሚገዛ ከሰይጣን እጅ እንዲያድን በመንፈስ ተረድቶ በዳስ በዓላቸው ወቅት “እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህቺ ናት ሐሤትን እናድርግ በእርሱዋም ደስ ይበለን፡፡ አቤቱ እባክህ አሁን አድን አቤቱ አሁን አቅና በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ብሩክ ነው” እያለ እርሱና ሕዝቡ የአምላካቸውን ወደ ቤተመቅደስ መምጣት በናፍቆት ይጠባበቁ ነበር፡፡(መዝ.117፡25-27)  
እነሆ በዛሬዋ ቀን ለአብርሃም አባታችን በሞሪያ ተራራ ላይ በይስሐቅና በዕፀ ሳቤቅ በተያዘው በግ ተመስሎ የታየው ንጉሥ ክርስቶስ የሰው ልጆችን ሊያድን በነቢዩ ዘካርያስ “ለጽዮን ልጅ እነሆ ንጉሥሽ የዋህ ሆኖ በአህያ ላይና በአህያይቱ ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል በሉአት”(ዘካ.9፡9)እንደተባለው እንዲሁም ነቢዩ ዳዊት“አቤቱ ስምህ በምድር ሁሉ ተመሰገነ ምስጋናህ በሰማዮች ላይ ከፍ ከፍ ብሎአልና ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ”(መዝ.8፡2)ተብሎ እንደተነገረው ትንቢት በሞሪያ ተራራ ላይ ወደ ተሠራው ቤተመቅደስ በአህያይቱና በውርንጭላይቱ ላይ ተቀምጦ ገባ፡፡ 
በዚያም በመንፈስ ሕፃናት የሆኑት ሐዋርያት እንደ አባታቸው አብርሃም የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘው በመንገድ ላይም ልብሳቸውን በማንጠፍ፤ እንደ ንጉሣቸው ዳዊትም "ሆሣዕና በአርያም" እያሉ በዝማሬ ምስጋናን ለጌታችን አቀረቡለት፡፡ (ማቴ.11፡25) በአካል ሕፃናት የሆኑትም ከእናታቸው እቅፍ በመውረድ "ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረከ ነው" እያሉ በዝማሬ ተቀበሉት፡፡ 
አሁን አማናዊው ቤተመቅደስ ክርስቶስ ሆኖአል፡፡ ስለዚህም ጌታችን ለአይሁድ "ይህን ቤተመቅደስ አፍርሱት በሦስት ቀን አነሣዋለሁ"ብሎ ተናገራቸው፡፡(ዮሐ.2፡19) እርሱ በሰውነቱ ቤተመቅደስ ራሱ መሥዋዕት፤ መስቀሉን መሠዊያ፤ ራሱን መሥዋዕት አቅራቢ፤ ራሱ መሥዋዕት ተቀባይ ሆኖ እኛን ከኃጢአትና ከሞት ባርነት ነጻ አወጣን፡፡
ስለዚህም በእርሱ መዳንን ያገኘን እኛ ክርስቲያኖች ሆሣዕናን ስናከብር በእኩል ደስታና በእኩል ኀዘን ሆነን ነው፡፡ እኩል በደስታ ሆነን ስንል እርሱ ስለእኛ በተቀበለው ሕማምና ሞት በመዳናችን ነው፡፡ ይህ የእኛ ብቻ ሳይሆን የጌታም ደስታ እንደሆነ በነቢዩ “እግዚአብሔር በደዌ ያደቅቀው ዘንድ ፈቀደ ነፍሱን ስለ ኃጢአት መሥዋዕት ካደረገ በኋላ ዘሩን ያያል … ከነፍሱም ድካም ብርሃንን ያያል ደስም ይለዋል”(ኢሳ.53፡10-11)ብሎ ገልጾልናል፡፡
በአንጻሩ ደግሞ ስለእኛ የተቀበለውን ጽኑ ሕማምን ባሰብን ቁጥር ልባችን በኀዘን ይሰበራል፡፡ ምክንያቱም እንዲህ ዓይነት ጽኑ መከራን መቀበሉ በእኛ መተላለፍ ምክንያት ነውና፡፡ ስለዚህም ስለእኛ የተቀበለውን ጭንቅ የሆነ መከራ ስናስብ ልባችን በኀዘን ይሞላል፡፡ ነገር ግን ሕማሙንና ሞቱን ማሰባችን በሰሙነ ሕማማት ብቻ እንዲሆን የእግዚአብሔር ፈቃዱ አይደለም፤ በሕይወት ዘመናችን ሁሉ እንጂ፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን እንድንቀበል  ማዘዙ አንድም ሕማሙንና ሞቱን ዘወትር እንድናስበው በመሻቱ ነው፡፡ እንዲህም እንደሆነ ቅዱስ ጳውሎስ ሲያስረዳ፡-“ይህን እንጀራ በበላችሁ ጊዜ ሁሉ ይህንም ጽዋ በጠጣችሁ ጊዜ ሁሉ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ሞቱን ትናገራላችሁ”(1ቆሮ.11፡26) ብሎ ጽፎልናል፡፡ ስለዚህም እኛም ልክ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ “የኢየሱስ ሕይወት በሥጋችን ይገለጥ ዘንድ የኢየሱስን መሞት በሥጋችን ተሸክመን እንዞራለን፤” ይህ ስንቆርብ ይፈጸማል፡፡(2ቆሮ..4፡10) በመሆኑም ስለእኛ የተቀበለውን ጽኑ ሕማምና ሞት ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን በተቀበልን ጊዜ ሁሉ እናስባለን፡፡ እንዲሁም በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ ባገኘነው ሕይወት በመንፈስ ቅዱስ ደስ ይለናል፡፡ ይህንን ነው እኩል ደስታ እኩል ኀዘን ማለቴ፡፡ ስለዚህም ለእኛ ለክርስቲያኖች የሆሣዕና በዓል ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን በተቀበልን ጊዜ ሁሉ ነው ማለት ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ሆይ ለዚህ ድንቅ ለሆነው ፍቅርህ ምን እንከፍልሃለን? አምላካችን ሆይ ሁሌም አንተን ማሰብንና በፍቅርህ መኖርን ስጠን ለዘለዓለሙ አሜን!!!
በዚህ አጋጣሚ ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን ሰሙነ ሕማማቱ መልካም የተመስጦ ጊዜ እንዲሆንላችሁ እመኝላችኋለሁ፡፡      

3 comments:

  1. እነሆ ጌታችን ምስጋናን በመንፈስ ሕፃናት ከሆኑ ከሐዋርያትና(ማቴ.11፡25) በአካል ሕፃናት ከሆኑት በዛሬዋ ቀን ምስጋናን ተቀበለ፡፡ አሁን አማናዊው ቤተመቅደስ ክርስቶስ ነው፡፡ ራሱን መሠዋዕት፤ መስቀሉን መሠዊያ፤ ራሱን መሥዋዕት አቅራቢ፤ ራሱ መሥዋዕት ተቀባይ፤ ሆኖ ዓለምን ያዳነ እርሱ ነው፡፡ ስለዚህ እኛ በእርሱ መዳንን ያገኘነው ክርስቲያኖች ሆሳዕናን ስናከብር በእኩል ደስታና በእኩል ኀዘን ሆነን ነው፡፡ እኩል በደስታ ሆነን ስንል እርሱ ስለእኛ በተቀበለ ሕማምና ሞት በመዳናችን ነው፡፡ ይህ የእኛ ብቻ ሳይሆን የጌታም ደስታ እንደሆነ በነቢዩ “እግዚአብሔር በደዌ ያደቅቀው ዘንድ ፈቀደ ነፍሱን ስለ ኃጢአት መሥዋዕት ካደረገ በኋላ ዘሩን ያያል … ከነፍሱም ድካም ብርሃንን ያያል ደስም ይለዋል”(ኢሳ.53፡10-11)ብሎ አሳውቆናል፡፡

    ReplyDelete
  2. Amen amen amen kale heyweten yasemalen

    ReplyDelete
  3. Kaleheywet yasemalen

    ReplyDelete