Saturday, February 18, 2012

"በአረጀ አቁማዳ አዲስ የወይን ጠጅ የሚያኖር የለም"(ካለፈው የቀጠለ)


በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
10/06/2004
ይህ እንዲሆንም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ስለመንጎቹ በመስቀል ላይ ሠዋ፡፡ ሙሽሪት ምዕመናንንም በደሙ ገዛት፡፡ ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ አንጽቶ ከጎኑ በፈሰሰውም ደሙ ቀድሶ የራሱ አደረጋት፡፡ እንዲያም ስለሆነ ለሰማያዊው ንጉሥ ሰማያዊት ሙሽራው ሆነችው፡፡ ሙሽሪት የተባልነው እኛ ነን፡፡ አሁን እኛ በክርስቶስ አምላክነት አምነን በሥላሴ ስም የተጠመቅን ክርስቲያኖች በመንፈስ ቅዱስ የታደሰ ሰማያዊ ሰብእናን ገንዘባችን በማድረጋችን የእግዚአብሔር ልጆች ተሰኝተናል፡፡ስለዚህም የእግዚአብሔርን ጥልቅ የሆነ አሳብን እንኳ በመንፈስ ቅዱስ ታግዘን ለመረዳት እንችላለን፡፡ እንደ መንፈስ ቅዱስም ፈቃድ በመመላለስ ሰይጣንን ድል የምንነሣበትን የጽድቅ ጥሩርን ለብሰናል፡፡
አሁን አባታችን አዳም ሳይሆን እግዚአብሔር ሆኖአል፡፡ እንዲህም ስለተደረገልን አባ ብለን እርሱን ለመጥራት አናፍርም፡፡  ሆኖም የእግዚአብሔር ልጅነትን ሥልጣን በማግኘታችን ተረጋግተንና ተዛንተን መኖርን አግኝተናል ማለት ግን አንችልም፡፡ ምክንያቱም የአዳምን ንጽሐ ጠባይን ያልወደደውና ከክብሩ ያዋረደው ሰይጣን በቅናት ተነሣስቶ እኛን ለማሰናክል  መትጋቱ አይቀሬ ነውና፡፡ ይህም እንዲገለጥ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ በሰይጣን ይፈተን ዘንድ ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ሄደ፡፡ ይህ የሚስተምረን ነገር አለ፡፡ እርሱም እኛ በጥምቀት የእግዚአብሔር ልጅነት ሥልጣን በማግኘታችን ዲያብሎስ በጠላትነት እንደሚነሣብንና ከልጅነት ክብራችን ለማሳነስ እንደሚተጋ ነው፡፡ ስለዚህም አባ አባ የምንልበትን የልጅነት መንፈስ በጥምቀት በማግኘታችን እኛን ለማሰናከል በእጅጉ እንደሚተጋ አውቀን እኛም በጦምና በጸሎት ጌታችንን መስለን ሰይጣንን ድል ልንነሣው ይገባናል፡፡ ነገር ግን እንዳው በልማድ ለምን እንደምንጦም ሳንረዳ የምንጦም ከሆነ በአዲሱ አቁማዳ አሮጌውን የወይን ጠጅ እንደመጨመር ይቆጠርብናል፡፡ እነዚህ እርስ በእርሳቸው አይጠባበቁምና አቁማዳው ይፈነዳል ወይኑም ይፈሳል፡፡ ስለሆነም ከጦማችን አንዳች ጥቅም ሳናገኝ የሰይጣን መሳለቂያ ሆነን እንቀራለን፡፡ እንዲያ እንዳይሆን መጪው የጦም ወቅታችን ራስን መግዛት የምንለማመድበትና የእግዚአብሔርን አሳብና ፈቃድ የምናቅበት ጦም እንዲሆን እንትጋ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ መጪውን ጦም እንዳው በልማድ ሳይሆን ሰይጣንን እንዴት ድል መንሳት እንደምንችል የምንማርበት ጦም ያደርግልን ዘንድ ፈቃዱ ይሁን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡  

No comments:

Post a Comment