Friday, April 27, 2012

አትንቀፍ እንዳትነቀፍ አትፍረድ እንዳ…”



በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
19/08/2004
ቅዱስ ይስሐቅ ሰው በክፉም ይሁን በደግ ዐይኖቹ መታወራቸው አይቀርም ይለናል፡፡ በኃጢአት ውስጥ ያለ ሰው ዐይኖች ጽድቅን ማየት ይሳናቸዋል፡፡እንደነዚህ ዐይነት ወገኖች የሰዎች ኃጢአት እንጂ የጽድቅ ሥራቸው ወይም መልካም የሆነው ተፈጥሮአቸው አይታያቸውም፡፡ ነገር ግን የጻድቅ ሰው ዐይኖች የሰዎችን ድክመትም ሆነ ነውር ወይም ኃጢአት አይመለከቱም፡፡ሁሉም በእነርሱ ዘንድ ብሩካን ናቸው፡፡ እንዲህ ሲባል ግን ኃጥእ ጽድቅን አያቃትም ማለት ሳይሆን ወደ ኃጢአት ፈቃድ ያደላል ሲለን ነው፡፡ እንዲሁ ጻድቅ ሰውም የሰዎች ጉድለትና ድክመት ወይም ኃጢአት ሳይሆን አስቀድሞ የሚታየው የእነርሱ መልካምነት ነው፡፡
ጻድቅ ሰው የሰውን ደካማ ጎን ሳይሆን ጠንካራውን ይመለከታል፤ ስለዚህም በዐይኑ ውስጥ የገባውን ጉድፍ ለማውጣት በወንድሙ ዘንድ የታመነ ነው፡፡ በጽድቅም ምክንያት ዐይኖቹ ብሩሃን ናቸውና በወንድሙ ዐይን ውስጥ ያለውን ጉድፍ ዐይኑን ሳይጎዳው ጉድፉን ብቻ ለይቶ ያወጣለታል፡፡ ወንድሙም ከሕመምና ከስቃይ ጤናማ ስለሚሆን እርሱም እንደ ጻድቅ ወንድሙ አጥርቶ ማየት ይጀምራል፡፡ እንዲህ ነው መልካም ወዳጅ፡፡ ጻድቅ ሰው እንዲህ ነው፡፡ አይነቅፍም፤ አይቆጣም የወንድሙን ነውር ወይም ድክመት በአደባባይ አያወራም፤ በወንድሙ ላይ አይታበይም፤ ወንድሙ ከእርሱ እንደሚሻል ይቆጥራል፤ ስለወንድሙ መዳን በአምላክ ፊት ያነባል፤ ወንድሙን ከስህተት መንገድ ለመመለስ  ነገሮችን ሁሉ በጥንቃቄ ይከውናል፡፡

በተቃራኒው ደግሞ ኃጥኡ አውቆም ቢሆን ሳያውቅ ስለሰው ድክመትና ነውር አውርቶ አይጠግብም፡፡ ያማል ያማል ያማል ያማል ሁሌም ያማል እንዴት አሰልቺ ነገር ነው?

በጽድቅ ሕይወት ያለ ሰው ግን ሁሌም በንግግሩ ሰውን እንዳይጎዳ እግዚአብሔር ንግግሩን እንደሚሰማው ተረድቶ በማስተዋል ይናገራል፡፡ ዐይኖቹ የአምላኩን ፊት ስለሚመለከቱ የሰውን ድክመት በጥበብና በፍቅር አጋጣሚን ተጠቅሞ ለማረም ይደክማል እንጂ በመንቀፍና በማንኳሰስ ኃጥእ ወንድሙን አይናገረውም፡፡ ጻድቅ በእርሱ ሊሆን የማይፈልገውን በሰው ላይ ሊያደርግ አይፈቅድም፡፡ ኃጢእ ግን እንዲህ አይደለም፡፡ ዐይኖቹ በትዕቢት ወይም በከንቱ ውዳሴ ወይም በገንዘብ ፍቅር ወይም በዝሙት የታወሩ ናቸውና ወንድሙን በመጉዳት፣ በመንቀፍ፣ በማሳነስ በራሱ ላይ ጉድጓድ ይምሳል፤ ጉድጓዱም እጅግ ጥልቅ ነው፤ እርሱም ገሃነም ነው፡፡ ጌታችን ስለዚህ ሲያስተምር “በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ሁሉ ፍርድ ይገባዋል፤ ወንድሙንም ጨርቃም የሚለው ሁሉ የሸንጎ ፍርድ ይገባዋል፤ ደንቆሮ የሚለውም ሁሉ የገሃነም እሳት ፍርድ ይገባዋል” ብሎአል፡፡(ማቴ.5፡21-23) 
ኦ አምላክ ሆይ ኃጥኡ በራሱ እጅ የቆፈረው ጉድጓድ እንዴት ጥልቅ ነው! በዚያ ውስጥ ለዘለዓለም የሚቀበለውስ ስቃይና ሰቆቃ እንዴት ጭንቅ ነው! ስለዚህም ይሆን ጠቢቡ ሰሎሞን “ሰነፍ ዝም ቢል ጠቢብ ሆኖ ይቆጠራል” ያለው?(ምሳ.17፡28) ሰነፍ ሰው ልቡ ስለሰው ድክመትና ኃጢአት እንዲሁም ነውር አውራ አውራ ሲለው ወይም በውስጡ ያደረው ሰይጣን ክፉ እንዲያወራ ሲጎተጉተው ልቡ አንካሳ ቢሆንም ዝምታን ቢመርጥ ጭንቅ ከሆነ ጥፋት ያመልጣል፡፡ 
ቅዱስ ኤፍሬም “እሳት ከእርሱ የወጣበትን እንጨት እንዲያጠፋ ኃጥእም ከእርሱ የመነጨው ክፉ ንግግሩ እርሱን መልሶ ያጠፋዋል” ይለናል፡፡ ስለዚህ ወገኔ ሆይ በማንም ሰው ላይ ቢሆን ራሳችንን በእግዚአብሔር ፍርድ ወንበር ላይ አስቀምጠን አንፍረድ፡፡ ማንም በሌላው ባሪያ ላይ ፈራጅ ተደርጎ አልተሾመምና፡፡ ይልቁኑ በቅንነትና በፍቅር እንዲሁም በትሕትና ወንድማችንን ከጥፋት ለመቤዠት እንድከም፡፡ የሚነቅፍ ይነቀፋል፤ የሚፈርድም ይፈረድበታል፡፡ 
አባታችን ሆይ የምትወዳቸውን የሰውን ልጆች ከኃጢአት ሕይወት እንድናወጣቸው ዐይኖቻችንን በፍቅር አብራ፡፡ በወንድማችን ጉድለትና ነውር ላይ እንዳንሳለቅና በእነርሱ ላይ እንዳንታበይ የራሳችንን ኃጢአት እንድንመለከት እርዳን፡፡ ወገኖቻችንን ከውድቀታቸው እንድናነሣቸው እኛን ከወደቅንበት ከዚህ ኃጢአት አንሥተህ ኃይልህን አስታጥቀን፡፡ ሁሌም በሰው ሁሉ ላይ ያንተን መልክና ምሳሌ ማየትን እንድናስቀድምም ጌታ ሆይ እርዳን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

  

1 comment:

  1. አባታችን ሆይ የምትወዳቸውን የሰውን ልጆች ከኃጢአት ሕይወት እንድናወጣቸው ዐይኖቻችንን በፍቅር አብራ፡፡ በወንድማችን ጉድለትና ነውር ላይ እንዳንሳለቅና በእነርሱ ላይ እንዳንታበይ የራሳችንን ኃጢአት እንድንመለከት እርዳን፡፡ ወገኖቻችንን ከውድቀታቸው እንድናነሣቸው እኛን ከወደቅንበት ከዚህ ኃጢአት አንሥተህ ኃይልህን አስታጥቀን፡፡ ሁሌም በሰው ሁሉ ላይ ያንተን መልክና ምሳሌ ማየትን እንድናስቀድምም ጌታ ሆይ እርዳን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

    ReplyDelete